2022-07-04 18:36:28
የወጠረኝ ደም ሲበርድ የምፀፀት ነበር የመሰለኝ። በምትኩ የሆነ መገላገል አይነት ስሜት ተሰማኝ። የሚራወጥ ጭንቅላቴ እርግት እንደማለት።
«ቀንተሃል! ተናደሃል! በራስህ በሽቀሃል! ያን ግን እየተወጣኸው ያለኸው ትክክለኛ ቦታ አይደለም! በፊት እንደምታደርገው በመፅሃፎችህ ወይም በስራህ ራስህን ልትሸውደው ሞክረህ ሀሳብህ አልሰበሰብ ብሎሃል! ያን በወሲብ እየተካኸው ነው! የቀኑን ውጥረትህን ትቀንስበታለህ እንጂ ቋሚ መፍትሄ አይሆንህም! አንተ ራስህን ልትረዳው ካልፈለግክ እኔ ምንም ላደርግ አልችልም አዲስ መፍትሄው አንተጋ ነው!! ። ራስህን በጊዜያዊ እፎይታ ልትሸውደው አትሞክር! ውጥረት በተሰማህ ቁጥር ያን እፎይታ ፍለጋ በወሲብ ልትወጣው ትሞክራለህ! ስትደጋግመው ልክ እንደማንኛውም ድራግ ነው። የሚሰጥህ እፎይታ መጠን እየቀነሰ ይመጣና ዜሮ ይሆናል። ይሄኔ ውጥረቱ ብቻ ሳይሆን አንተ ባልሆነው ማነነትህ ብስጭትህና ፀፀት ይጨመሩበታል። ወይ ሌላ የምትተነፍስበት ሱስ ትፈልጋለህ ወይም ወደምትሸሸው ጨለማህ ትመለሳለህ!!» አለኝ ዶክተር የሆነ ቀን በሀኪም ለዛ ሳይሆን በአባት ቁጣ!!
በትክክል ሂደቱን ጠብቆ የተከሰተው ያ ነው። ደጋገምኩት! በደጋገምኩት ቁጥር እርካታን ሳይሆን የባሰ ጭንቀትን እያስታቀፈኝ መጣ!! እዚህጋ እሷንም ዘነጋኋት ራሴንም እንደዛው። ከወራት በኋላ ዶክተርጋ ሄጄ
«አሁን ዝግጁ ነኝ የሆንኩትን ሆኜ መዳን እፈልጋለሁ።» አልኩት። ደስ ብሎት ትከሻዬን እየመታ ተቀመጠ። ማውራት የጀመርኩኝ ቀን አስመለሰኝ ሁላ! የእናቴን አልፌ የመጀመሪያ የማዕረግ ክህደቷን አልፌ ሶስተኛው ጋር ስደርስ ተሰምቶኝ የነበረውን ዲቴል ማውራት ያቅተኛል። በየቀኑ ከመጀመሪያው እጀምራለሁ። በየቀኑ ትንሽ እየገፋሁ አቆማለሁ። በዚህ መሃል ለስራ ከከተማ ወጥቼ ስመለስ ነው መኪናዬ የተገለበጠው። እያሰብኩ እንደነበር አስታውሳለሁ ምን እንደሆነ ግን አላውቅም! ከፊቴ የሚመጣ መኪና ጡሩንባውን ሲያስጮኸው ነው እንደመባነን አድርጎኝ መሪዬን ያጠመዘዝኩት።»
«ለእኔኮ ግን እስከመጨረሻው ነገርከኝ አይደል? ያ ማለት?» አልኩት ካለፈው ስቃዩ የመዳን ምክንያት ሆኖት ከሆነ በሚል
«እናያለና!» አለኝ
«እሺ ቆይ በቃ? ከዛ በኋላ ያለውስ?» አልኩት ኮንፒውተሩን እያስቀመጥኩት።
«ከዛ በኋላ ያለውን አንቺ የማታውቂው የለም ራስሽ ትፅፊዋለሽ!» አለኝ በእርግጠኝነት
«እህ! ያንተን ስሜት ግን በትክክል ላሰፍረው አልችልም!»
«come on! ካንቺ በላይ የሚያውቀኝ ሰው የለም። በስሜት ደረጃ ከማንም ጋር መቆራኘት የማልፈልግ ሰው ዊልቸር ላይ ተቀምጬ በአካልም የሰው እርዳታ የምፈልግ ጥገኛ መሆኔ ምን እንዲሰማኝ እንደሚያደርገኝ ካንቺ በላይ የሚረዳ ሰው አለ? »
«የሰውን ድጋፍ ማግኘትኮ ሁሉም ሰው በሆነኛው የህይወቱ ጊዜ የሚገጥመው ነው! አንተ ሰዎችን ትረዳ የለ? ሰዎች ሲረዱህ ውድቀት የሚሆንብህ ለምንድነው?»
«በቃ እኔ ነኛ! (ትከሻውን ምን ላድርግ አይነት እየሰበቀ) በሰው ድጋፍ የምንቀሳቀስ ሰው መሆን ሞቴ ነው! ያን ታውቂያለሽ!! ለዘመናት የለፋሁትኮ በስሜትም በአካልም በገንዘብም ማንንም ያልተደገፍኩ ነፃ ለመሆን ነው» አለኝ የእርሱ ባልሆነ ማባበል ድምፅ! አላውቅም ምን እንዳሰብኩ ማጅራቴ ላይ ያለ እጁን ስቤ ሳምኩት። ሲጠብቀው የነበረ እርምጃ ይመስል አስከትሎ ከንፈሬን ሳመኝ። እየሳመኝ ያወራ ጀመር እንደበፊቱ ወሬው ግን የቀን ውሎአችንን አይነት አይደለም። ጆሮዬን ማመን እስኪያቅተኝ አዲስ በፍቅር ቁልምጫ ስም እየጠራኝ ነው። ደንግጬ ለሰከንድ በርግጌያለሁ ሁላ! ረዥም ሰዓት ከተሳሳምን በኋላ አቁሞ እንደመሳቅ ነገር እያለ
«ንግስቴ እንደምታደርጊኝ ካላደረግሽኝኮ እግሬን አላዘውም!» አለኝ አባባሉ ውስጥ <አየሽ ለዚህ እንኳን ያንቺን እርዳታ መጠየቅ ግድ ሲለኝ?> አይነት የመሰበር ድምፀት አለው። ሶፋው ስላልተመቸን ምንጣፉ ላይ ወርደን ማላብ ጀመርን! ከላይ ሆኜ እያየሁት እሱ በሚጠራኝ የፍቅር ቁልምጫ ሁሉ ልጠራው እፈልጋለሁኮ! ግን ከአፌ አይወጣም! አንዴ ቢለኝ ብዬ አምላኬን የለመንኩትን ቃል አለኝ። «ልትገምቺው ከምትችዪው በላይ እወድሻለሁ!» አለኝ። ስሰማው እፈነጥዛለሁ ብዬ ያሰብኩትን ያህል አላስፈነጠዘኝም! ንግስቴ ፣ ፍቅሬ ፣ ልዕልቴ ……….. ያላለኝ የለውም። ለዓመታት ያላለውን ማካካስ የሚመስል ፍቅር ……. ስንጨርስ አጠገብ ላጠገብ ተኝተን ዝም ተባባልን። ከሴክስ ስሜት ውጪ ያ የተስገበገብኩለት ፍቅር ስጨብጠው ምንም አልመስልሽ አለኝ ብዬ እውነቱን ነው የምነግረው ወይስ እንደዚሁ እንቀጥላለን ? በተጎዳው ላይ ጉዳት መጨመር መሰለኝ! ምናልባት ሽባ ስለሆንኩ ነው የጠላችኝ ይለኛል እያልኩ ሳስብ
«ይሰማኛል ብለሽ ያሰብሽውን ስሜት ውስጥሽ አጣሽው?» አለኝ
«ለምን እንደእሱ አልክ?»
«አውቅሻለሁ እኮ! በደንብ።»
«ታዲያ ካወቅክ?» ብዬ እንዴት መጠየቅ እንዳለብኝ ግራ ሲገባኝ
«ፍቅርሽን ከጨረሽ እንደቆየሽ አውቃለሁ። ከዛ ሁሉ በደል በኋላ ያ ስሜት ሊኖር አይችልም!»
«የበደልከኝንኮ ግን ትቼልሃለሁ!»
«አውቃለሁ! ይቅር ስትዪኝ ላለፍኩት መንገድ አዘንሽልኝ። ፍቅርን እና ሀዘኔታን ነው ያልለየሽው!»
«እሺ ካወቅክ ለምን?»
«ምንም እንዳልቀረብሽ እንድታውቂ!! ከተመኘሽው ምንም እንዳይጎድልብሽ!» አለኝ።
መኝታ ቤታችን ገብተን አቅፌው ተኛሁ። ነጋችንን እንዴት እንደምንኖረው እያሰብኩ እንቅልፍ ወሰደኝ። አይኖቼን ስገልጥ አንዳች ሸክም ከላዬ እንደተነሳ ቅልል ብሎኝ ነበር። አይኖቹን እንደጨፈነ ነው። ተገላብጬ ደረቱ ላይ ተጠግቼ ተኛሁ።
«አዲስዬ ! አዲስዬ!» ልቀሰቅሰው ሞከርኩ «ዛሬ እኔ ስራ ቦታ ደርሼ ልምጣ?» አይመልስልኝም። ቀና ብዬ አየሁት! «አታደርገውም አዲስዬ!!» ራስጌውጋ ያለውን መጠቀም ያቆመውን ያኔ ከባድ ህመም ሲሰማው ይወስድ የነበረውን ከባድ ፔንኪለር እቃ አየሁት!! «አታደርገውም! አዲስ አታደርገውም!» እቃው ባዶ ነው! ተነስቼ ይሰማኝ ይመስል ደረቱን እየደበደብኩ ማልቀስ ጀመርኩ።
መጠርጠር አልነበረብኝም ሲሸነፍልኝ? ያቺን ከዲያቢሎስ ጋር ሲማከር የሚያመጣትን ፈገግታ ፈገግ ካለ በኋላ ድንገት ቅይር ስል መጠርጠር አልነበረብኝም? አውቀው አልነበር ክፉ ሲያስብ? ከምንም ተነስቶ እንደዛ ቅይር እንደማይል እንዴት ጠፋኝ? ይሄን አስቦት ነው ማታ የሆነውን ሁሉ የሆነው! መጠርጠር አልነበረብኝም ፍቅሩን ሲያምንልኝ? መጠርጠር አልነበረብኝም በደሉን ሲያምንልኝ?? እስከሞት ራሴን የምወደው ራሴን ነው ሲለኝ መጠርጠር አልነበረብኝም? ሁሌም አፍቃሪ ሰውነቱ በተገለጠ ማግስት መዘዝ ተከትሎት እንደሚመጣ እንዴት ዘነጋሁት? ከመሸነፍ ሞትን እንደሚመርጥ አውቀው አልነበር? ድምፅ የወጣው ለቅሶ ማልቀስ አቃተኝ። እንባዬ ጉንጬ ላይ እየተንዠቀዠቀ አገላብጬ ሳምኩት። እያለቀስኩ ወደሳሎን ሄጄ ፀሃይን ጎረቤታችንን እንድትጠራ ስነግራት
«ምነው እናቴ? ምን ሆንሽ?» ስትለኝ
«አዲስ አዲስ » ብዬ መጨረስ አቃተኝ።
«በጠዋት ስትነሳ ስጫት ብሎ ይሄን ወረቀት ሰጥቶኝ ነበር ትናንት! ምነው አመመው እንዴ?» አለችኝ ወረቀቱን እያቀበለችኝ።
210 viewsBetslot markos, 15:36