2022-09-28 09:20:32
ለውብ ቀን!
የኦሽዊትዙ ሰው..
በጦር ወንጀለኝነት፣ በሰው ልጅ ላይ አሰቃቂ ሳይንሳዊ ሙከራዎችን በማድረግ፣ ጤነኛ ሰዎችን ለምርምር ሲባል በበሽታ አምጪ ባክቴሪያዎች በመበከል፣ የሚገደሉና ለምርምር የሚውሉ ሰዎችን በመለየት ሂደት ውስጥ በመሣተፍ፣ ወዘተ የሚሉ መዓት ዓይነት አሳቃቂ ክሶች የቀረበባቸው 40 ሰዎች ነበሩ።
ሰዎቹ የሰው ግዞት፣ ጉልበት ሥራና የሰው ምርምር በተካሄደበት በአሰቃቂው የኦሽዊትዝ የሞት ካምፕ ያገለገሉ የናዚ አባላትና ቅጥረኞች ናቸው። ናዚ ሲገረሰስ በአሜሪካኖቹ እጅ ወደቁ።
አሜሪካኖቹ ደሞ የሚመርጡትን መርጠው፣ የሚፈልጉትን ምርመራ አድርገው፣ 40ዎቹን የኦሽዊትዝ የሞት ባልደረቦች ለፖላንዶች አሳልፈው ሰጧቸው።
የፖላንድ ቤተእስራኤሎች ደሞ ዋነኛዎቹ የናዚ አራዊት ተጨፍጫፊዎች ናቸው። ከጦርነቱ በፊት በፖላንድ ከ4 ሚሊየን በላይ ትውልደ-እስራኤል ዜጎች ነበሩ። ጦርነቱ ሲጠናቀቅ በህይወት የተረፉት 350 ሺህ አይሞሉም።
ከ3.5 ሚሊየን በላይ አይሁዶች በ5 የተለያዩ የመግደያ የግዞት ካምፖች እየተወሰዱ ነው የተጨፈጨፉት። ይህ ማለት ከመቶው 98 ፐርሰንቱ እስራኤላዊ ከምድረ-ገፅ እንዲጠፋ ተደርጓል። (በዘመናዊዋ ዓለም እንደ ናዚ ዘረኛ ምሁራን በንፁሃን ደም የተጨማለቀ አረመኔ ኡመክ ታይቶም ተሰምቶም አያውቅም።)
ለፖላንዶች ተላልፈው የተሰጡትና በዋና ከተማዋ (ከዋርሶ በፊት) በክራኮ ክሳቸው የተደመጠው እነዚያ 40ዎቹ ናዚዎች ዶክተሮች አሉባቸው። ሳይንቲስቶች። የተማሩ የተመራመሩ ኡመክ የሚለውጨቃል የማይገልፃቸው አረመኔ ምሁሮች ናቸው።
ሁሉም ሞት ተፈረደባቸው። ከአንዱ በስተቀር። በናዚ የፍርድ ሂደት ታሪክ ውስጥ፣ በሰው ዘር ማጥፋትና በሰው እንደ አይጥ በመጫወት ተከስሶ፣ በነፃ የተሰናበተ ብቸኛው ሰውም ሳይሆን አይቀርም ይሄ ሰው።
የህክምና ዶክተር ነው። ዶክተር መንች ይባላል። የወጣለት ባክቴሪዎሎጂስትም ነው። ገና በኮሌጅ ተማሪ እያለ ነው የናዚ አባል የሆነው። ጦርነቱ ሲጀመር ካላዘመታችሁኝ ሞቼ እገኛለሁ ብሎ፣ ግን ዕውቀትህ እጅግ ጠቃሚ ስለሆነ አትዘምትም ተብሎ ነው ወደ ኦሽዊትዝ፣ በሳይንቲስትነት ማዕረግ ተመደበ።
(የኦሽዊትዝ ምሥጢር የሚል መፅሐፍ ከፃፈውና በመንታ ህፃናት ላይ የላብራቶሪ ምርምር ያካሂድ ከነበረው ከዶክተር ሜንጌሌ ጋር በባልደረባነት አብሮ ሠርቷል)።
ብዙዎች የናዚ ወንጀለኞች ክስና ፍርድ ተራ በቀል ነው፣ አይሁዶች ተጨፈጨፈፉ የሚባለውም ውሸት ነው ሲሉ ይደመጣሉ። ...
ሌሎች ብዙዎች ግን የህግን ልፍስፍስነት ሲረግሙ ነው የሚገኙት። ያንን ሁሉ ግፍ ለፈፀሙ የሰው ሥጋ ለብሰው የዲያቢሎስን ሥራ በፍቅር ሲከውኑ ለነበሩ እነዚያ የናዚ አውሬዎች የሚገባቸው ቅጣት ሞት ብቻ ነው ወይ? ህግ የሚባለው ነገር ከቅፅበት ሞት የበለጠ (የከፋ) ቅጣት የለውም ወይ? ብለው። መፈክር ሁሉ ይዘው ወጥተው ህጉን ረግመዋል።
ሁሉም ናዚ የዲያብሎስ ደቀመዝሙር ነው ባይባልም፣ የኦሽዊትዞቹን የኤስ ኤስ የናዚ መኮንኖችና ቅጥረኞች ግን ዲያብሎስ ራሱ የሚቀናባቸው ከሠይጣንም የባሱ አረመኔ ኡመኮች ናቸው።
ይሄ ዶክተር ግን ከኡመኮቹ ተለይቶ ተገኘ። ትንሽ ሰብዓዊ ህሊና ተገኘበት። ከናዚ ፓርቲ ቃልኪዳኑ ይልቅ ቃል ለገባለት ለሂፖክራቲክ ቃለኪዳን አድልቶ ተገኘ።
በኦሽዊትዝ አዲስ ከሚራገፉ አይሁዶች መሐል ለጉልበት ሥራ የሚሆኑትን፣ ለህክምና ምርምር የሚሆኑትንና በእርጅናቸው ወይ በህፃን ዕድሜያቸው የተነሳ ወይ ደግሞ በአቅመ-ቢስነታቸው ተስፋ የሌላቸውንና ወዲያው ወደ መርዝ ጋዝ መገደያ የሚላኩትን እንዲለይ ተመደበ።
ይሄ ዶክተር ግን ትዕዛዝ ባለመቀበሉ የሚደርስበትን ለመቀበል ቆርጦ (ህይወቱን ሸጦ) የተሰጠውን ግዳጅ አልቀበልም ብሎ ፀና። እና ታሪኩና የናዚ ፍቅሩ ተጠንቶ ተረፈ።
እና ከኦሽዊትዝ አጠገብ የሚገኘው የበሽታ አምጪ ሚክሮብስን ለማጥናትና ለመጠቀም በሰው ልጆች ላይ ምርምር የሚያደርገው ኢንስቲትዩት ሀላፊ ተደርጎ ከኦሽዊትዝ ዘወር ተደረገ።
በዚያ ላብራቶሩ ውስጥ ሆኖ ብዙ ትውልደ-እስራኤሎችን ለምርምር ይላኩልኝ እያለ ከኦሽዊትዝ የሞት ካምፕ በብዛት እያስመጣ ከጋዝና ከምድጃ አፍ አትርፏቸዋል። የታመሙትን በምሥጢር እያከመ አድኗል። ብዙዎች እንዲያመልጡ ረድቷል።
ብዙዎች መሠከሩለት። ታሳሪዎች፣ ተጋዦች፣ ከሞት ያስመለጣቸው። እና እርሱም በፀፀት ያደረገውን አመነ፦
"ብዙዎችን ለማዳን፣ ሌሎች ጥቂቶችን
መግደል ነበረብኝ፣ ጥቂቶችን ለሞት
ዳርጌ ብዙዎችን አትርፌያለሁ፣ ማድረግ
የምችለው ያ ነበር፣ አለበለዚያ ሁላችንም
ያልቅልን ነበር።"
ታማኝነቱን ለማረጋገጥ ዓይኑ እያየ በሰዎች ላይ ዘግናኝ የአይጥና የዝንጀሮ ምርምር ሲካሄድ መተባበር ነበረበት። ግን ህሊና አለውና ብዙዎችን አዳነ። እና ብቸኛ ባለ ህሊናነቱ፣ ብቸኛው ነፃ ሰው አደረገው። ክሶቹ ውድቅ ተደርገውለት፣ በነፃ ተለቀቀ።
በነፃ መለቀቀ ብቻ አይደለም። የህክምና ፈቃዱም ተመለሰለት። መፅሐፎችና ፊልሞችም ተሠርተውለታል። "The Good Man of Auschwitz" (የኦሽዊትዙ መልካም ሰው) የሚል መጠሪያ ስምም ወጥቶለታል። በብዙ ችሎቶችና ሕዝብ አዳራሾች እየተገኘ "ያለፈው እንዳይደገም" ምስክርነቱን ሰጥቷል።
አንዳንዴ የፈለገው መጥፎ ሥራና መጥሰዎች ቢከብቡህ፣ ህሊና እስካለህ ድረስ፣ ከመጥፎዎች መሐል ሆነህ ጥሩ መሥራት እንደምትችል፣ ከዚህ ሰው ህይወት መማር ይቻላል።
ሰሞኑን ያየሁትና የመሰጠኝ አንድ አባባል ነበር፦ "መርከቡ የሚሰምጠው በውሃ በመከበቡ የተነሳ አይደለም፣ ውሃው ወደ መርከቡ ውስጥ ሲዘልቅ ነው የሚሰምጠው" የሚል አባባል።
ታዲያ ይህ እውነት ለሰውም የሚሠራ ይመስለኛል። የፈለገውን ያህል በመዓት እርጉሞች ተከብበህ የምትንቀሳቀስ ሰው ብትሆን፣ ክፋታቸውን ወደ ውስጥህ እስካላስገባኸው ድረስ በእርጉምነታቸው አትለከፍም። ውስጣቸው ሆነህ፣ ክፋታቸውን መታገል ትችላለህ። ክፋታቸው ንፁህ ህሊናህን እንዳያጨቀየው፣ ሌላውን ባትችል ራስህን ማዳን ትችላለህ። ለዛሬው ታሳሪህ ብትራራለት፣ የዛሬ ታሳሪህ የነገ አስፈቺህ ይሆናል።
በዘመነ ኢህአዴግ ባለፍንበት የልዩ አቃቤ ህግ የዘር ጭፍጨፋ ክስ አሳዛኝ ድራማ መሐል፣ አንድ እየተማረረ በልዩ አቃቤ ህግነት ይሠራ የነበረ አቃቤ ህግ ወዳጄ ያጫወተኝ አሁን ትዝ አለኝ።
ከተከሰሱት የደርግ (ወታደራዊው) መንግሥት ባለሥልጣናት የአንዱ ክስ ሂደት እየተደመጠ በነበረበት ወቅት፣ ወሬውን የሰማ አንድ ምስክር ማንም ሳይጠራው በራሱ ተነሳሽነት ከእንግሊዝ ሀገር ድረስ በርሮ አዲሳባ ልዩ አቃቤህግ ቢሮ መጣ። ምን ሊመሠክር?
ይሄ ባለሥልጣን በቀይሽብር ወቅት የእስርቤት ውሳኔ አስፈፃሚ ሆኖ በኃላፈፊነት ሲሠራ፣ እኔ ተወስኖብኝ ልረሸን በጭለማ ወደ እንጦጦ ተወሰድኩ። ነገር ግን ይህ ሰው ጥይቱን ወደ ድንጋዩ አከታትሎ ከተኮሰ በኋላ፣ ደርቄ በቀረሁበት ወደ ጆሮዬ ጠጋ ብሎ፣
"በል ሳትገላመጥ ሸምጥጠህ ሩጥ።
ለዛሬ አትርፌሀለሁ። ተመልሰህ ብትያዝ፣
እኔንም ጭምር ነው የምታስገድለኝ። አሁን
ጥፋ ከፊቴ!"
"ብሎ ከሞት አትርፎ አባረረኝ። አያውቀኝ። አላውቀው። ወጣትነቴ አሳዝኖት ብቻ ነው። በተሠጠው ትዕዛዝ አላመነበትም። በዚያው ካገር ኮበለልኩ። ሱዳን ስደተኛ ካምፕ ሆነን ከዚህ ካመለጡ ኢትዮጵያውያን ጋር ስናወራ፣ ይህ ሰው በዚህ መልክ ከሞት አፋፍ ያስመለጠን ሶስት ሰዎች ነበርን። ስሙን ያወቅኩትም እዚያ ነው።...
1.4K views06:20