2022-07-05 16:15:22
በላይ በቀለ ወያ በመፈታቱ (እንደ ሰው) ደስ ብሎናል፤ ይኹንና የ“ቶ” መስቀልን በስፋት ከሚጠቀሙ አንዱ ነው፤ እንደዚያውም ደግሞ “ኦርቶዶክሳዊ ክርስቲያን” ነኝ ሲል እንመለከተዋለን፤ ነገር ግን “ክርስቲያናዊ ምልክት” አለመኾኑን ከዚህ በታች አቋሜ አመለክታለሁ! ...
“ቶ”
ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ፣ በአንገታቸው የመስቀል ምልክትን የሚያስሩ ብዙዎች፣ “ቶ” ምልክት ያለውን በአንገታቸው ማሰርን በአደባባይ እየተመለከትን ነው። “ቶ” ምልክት ያለው ብቻ ሳይኾን፣ ሌሎችም እንግዳ ድርጊቶች ሲከሰት፣ በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶና በሌሎችም አድባራትና አብያተ ክርስቲያናት ሲከናወን ዝም ማለት አልያም አንዳችም ምላሽ ከመስጠት ተቆጥቦ፤ ነገሩ ከእንቁላል ወደ ጫጩት እስኪያድግና ብሎም እስኪጐለምስ ችላ ማለት እንግዳ ተግባርም አይደለም።
የመጽሐፍ ቅዱሱ ክርስትና፣ መስቀል ሲል ዋናውን ትርጕም በመከተል፣ የክርስቶስን የማዳን ኹለንተናዊ ተግባርን በመወከል ይሰብካል። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መሰቀሉ፣ የክርስትና ዋና ማዕከልና የመዳናችን ቱንቢ ነው። እግዚአብሔር ለወደቀው ዓለም ርኅራኄውን የገለጠው አንድያ ልጁን በመስቀል ላይ አሳልፎ በመስጠት ነው። አንድያ ልጁም “ስለ እኛ ነፍሱን የሰጠው” (ዮሐ. 10፥11፤ ቲቶ 2፥14) እጅግ ኃጢአተኞች፣ ደካሞች፣ ጠላቶች፣ በበደላችንና በኃጢአታችን ሙታን፣ ዐመጸኞችም ሳለን ነው፤ (ሮሜ 5፥6፡ 8፡ 10፤ ኤፌ. 2፥1፤ 1ጴጥ. 3፥18)።
ለዚህ ነው አራቱም ወንጌላውያን በአንድነት ተባብረው ስቅለቱንና ሞቱን በታላቅ ርዕስነት የሚያነሡት። አዎን፤ የመሲሑን ልደት፣ የልጅነቱን ሕይወት ኹሉም ወንጌላውያን አልተረኩትም፤ መስቀሉን ግን ተባብረው በአንድ ቃል አጽንዖት ሰጥተው ተርከውታል። ምክንያቱም መስቀሉ[መሥዋዕታዊ ሞቱ] የክርስትና ዋና ጭብጥና ትምህርት፤ ፍጥረተ ዓለሙ የተዋጀበት እንከንና ነቅ አልባ ቤዛና ዋጆ ስለ ኾነ። የክርስቶስ መስቀል የሌለበት ክርስትና፣ እርሱ ክርስቶስ ያስተማረንና ተሰቅሎ ያሳየን ክርስትና አይደለም። መጽሐፍ በግልጥ ቃል ልዩ ወንጌልና ልዩ ኢየሱስ እንዳለ ሲነግረን፣ “ … የሚመጣውም ያልሰበክነውን ሌላ ኢየሱስ ቢሰብክ፥ ወይም ያላገኛችሁትን ልዩ መንፈስ ወይም ያልተቀበላችሁትን ልዩ ወንጌል ብታገኙ፥” (2ቆሮ. 11፥4) በማለት ያሳስበናል፤ ልዩ ኢየሱስና ልዩ መንፈስ ካለ፣ ልዩ መስቀልም ሊኖር እንደሚችልም መዘንጋት አይገባም።
ክብር ይግባውና፣ የተሰቀለው ጌታችን ኢየሱስ ለእኛ ሕይወታችን ነው፤ በእርሱ በስቁሉ ተወዳጅ መሲሕ መሰቀልም ተነግሮ፤ ተሰፍሮ የማያልቁ በረከቶችና ጸጋዎችን ማግኘታችንን መዘንጋት የለብንም፤ ጥቂቱን ብንጠቅስ፦
· በደላችንና ኃጢአታችን በእርሱ መሰቀል ተሰረየ፤
“ስለ ብዙዎች ለኀጢአት ይቅርታ የሚፈስ የአዲስ ኪዳን ደሜ ይህ ነው።” (ማቴ. 26፥28)
“እርሱንም [ክርስቶስ ኢየሱስንም] እግዚአብሔር በእምነት የሚገኝ በደሙም የሆነ ማስተስሪያ አድርጎ አቆመው” (ሮሜ 3፥25)
“መጽሐፍ እንደሚል ክርስቶስ ስለ ኀጢአታችን ሞተ …” (1ቆሮ. 15፥3)
“በውድ ልጁም እንደ ጸጋው ባለ ጠግነት መጠን በደሙ የተረገ ቤዛነታችንን አገኘን፤ እርሱም የበደላችን ስርየት” (ኤፌ. 1፥7)
“ክርስቶስ ደግሞ፣ የብዙዎችን ኀጢአት ሊሸከም አንድ ጊዜ ከተሠዋ በኋላ …” (ዕብ. 9፥28)
“ለወደደን ከኀጢአታችንም በደሙ ላጠበን …” (ራእ. 1፥6)
· ተቃዋሚያችን ከመንገድ ተወግዶበታል፤
“በእኛ ላይ የነበረውን የሚቃወመንንም በትእዛዛት የተጻፈውን የዕዳ ጽሕፈት ደመሰሰው፤ እርሱንም በመስቀል ጠርቆ ከመንገድ አስወግዶታል፤” (ቈላ. 2፥14)
· ዱካውን እንድንከተል በመሰቀሉ አሳይቶናል፤
ጌታችን ኢየሱስ ሲያስተምር በግልጥ ቃል እንዲህ አለ፤ “መስቀሉንም የማይዝ በኋላዬም የማይከተለኝ ለእኔ ሊሆን አይገባውም።” (ማቴ. 10፥38)። ልክ እርሱ እስከ ሞት ባለፈበት መንገድ አማኞችም ሕይወታቸውን እስከ ሞት ድረስ ጭምር ስለ ኢየሱስ በመስጠት ሊያልፉበት እንዳላቸው ተናገረ። ቅዱስ ጳውሎስም እንደ መሰከረው፤
“የእምነታችንንም ራስና ፈጻሚውን ኢየሱስን ተመልክተን፣ በፊታችን ያለውን ሩጫ በትዕግሥት እንሩጥ፤ እርሱ ነውርን ንቆ በፊቱም ስለ አለው ደስታ በመስቀል ታግሦ በእግዚአብሔር ዙፋን ቀኝ ተቀምጦአልና።” (ዕብ. 12፥2)
እኒህና ሌሎችንም አያሌ በረከቶችን የሰጠን የመሲሑ መስቀል(መሲሐዊ የሥጋ ሞት)፣ ተዘንግቶና ተረስቶ ዛሬ ላይ “እንጨቱን መስቀል” ማለትም፣ የተሰቀለበት እንጨት ዋና ትኵረት አጊኝቶ ስናይ እጅግ እናዝናለን። ክርስቶስ መሰቀሉና የዘመናትን ቀንበር ማንከባለሉና ፍጹም ነጻነትን በመሥዋዕታዊ ሞቱ መስጠቱ፣ እንደ ዋዛ ቀልሎና ታልፎ፣ እንጨቱን አልቀው ሰዎች ማየታቸው እጅግ ያስደንቃል። በርግጥ መስቀሉን ምልክት ማድረግ፣ አሉታዊ በኾነ መንገድ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ውስጥ ቢታወቅም፣ በተለይም ከመስቀሉ ጦረኞች ጋር በተያያዘ አብያተ ክርስቲያናት አርማውን መጠቀማቸው የተለመደ ነው። ነገር ግን የውርደትንና የመከራውን ዓርማ መጠቀም ዋናውን ጥሎና ዘንግቶ መኾን አልነበረበትም።
የ“ተ” ምልክት መስቀሉ፣ የክርስቶስን መሥዋዕታዊ ሞት ቦታን ተክቶ መውረሱ ሲደንቀን፣ ከዚህ የከፋውና እንግዳው ነገር ደግሞ፣ የ“ቶ” ምልክት እንግዳ የአንገት ጌጥ መምጣቱ ነው።
የ“ቶ” ምልክት “መስቀል” ምንነት
የ“ቶ” ምልክት ምንነት አያሌ ትርክቶች አሉት፤ ጥቂቶቹን ብናነሳ ከዚህ በታች እንዲህ ማስቀመጥ እንችላለን።
1. በጥንት ግብጽ ውስጥ “ራ” የፀሐይ አምላክ ነው፤[1] ይህን አምላክ ስሙን ጠርቶ ለሚለምነው፣ በእጆቹ በ“ቶ” ምልክት ከያዘው “መስቀል” በጨረር ፍንጣቂ፣ ሕይወት፣ ጥበብና ኃይልን ለአማኞቹ ኹሉ ያድላል፤ ይሰጣል ተብሎ ይታመናል። የዚህ ፀሐይ አምላክ አገልጋይ ካህናት የ“ቶ” ምልክትን በእጆቻቸው ይዘው ጣዖቱን ለማገልገል ይገደዳሉ። “ራ” በአምላካዊ ማንነቱ በፀሐይ ውስጥ ኾኖ “ቶ”ን ይይዛል። “ቶ” ደግሞ ዘወትር ሃይልን፣ ዕውቀትንና ጥበብ የተመላ ነው። ስለዚህም የ“ቶ” ምልክት በቀጥታ ከአማልክቱ አምልኮ ጋር የሚገናኝ መኾኑ አያሌ ማስረጃዎች አሉ።
እንግዲህ ይህን ምልክት እንደ መስቀል በአንገታቸው የሚያስሩ ራሳቸውን እንዲመረምሩ ብንልስ?
2. የጥቅምቱ ድርሳነ ዑራኤል፣ ፍካሬ ኢየሱስ፣ ገድለ ሲኖዳ፣ መጽሐፈ ምስጢርና ገድለ ፊቅጦር የሚተርኩት እጅግ እንግዳ ትርክት ደግሞ አለ። በተለይም ከ“ኢትዮጵያ ትንሣኤ” ጋር በማያያዝ። በገድለ ፊቅጦር ስለሚፈርሰው መቅደስና በኢትዮጵያ ስለሚነግሠው ቴዎድሮስ ስለሚባለው ንጉሥ የተገለጠ ራእይ እንዳለ ይናገራል። በድርሳነ ዑራኤል ደግሞ የቴዎድሮስን መንገሥ የሰማው የኤርምያስ ረድእ የነበረው ባሮክ ነው ይላል። እርሱም 40 ቀንና ሌሊት ጾሞ እንደ ተነገረውም ጭምር ይናገራል።
ይህ በ“ቶ” ምልክት የሚነግሠውና የስሙ መጀመሪያ በ“ቴ” ስም የሚጀምረው ንጉሥ በመንገሡ፣ ኢትዮጵያና ግብጽ ያልፍላቸዋል፤ እርሱም የአሕዛብን ነገሥታት ኹሉ ይደመስሳል። የመከራውን ዘመን ኹሉ ያሳልፋል ይላል እጅግ ሰፊው የመጻሕፍቱ ትርክት። ይህ ንጉሥ በሚነግሥበት ዘመን እንኳን ሰውና፣ ጠማማ እንጨት እንኳ አይኖርም በማለት ጭምር የንጉሡን ዘመን ፍጹም ያደርጉታል።
397 views"ውሰድና ብላት" (ራእ. 10፥9), 13:15