2021-08-24 20:08:19
የምርጫ ሥርዓት፣ መርሆች እና ዓይነቶች
=========================
#የምርጫ ሥርዓት
በፌደራል ህገ መንግሥት መሠረት ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ለሚደረግ ምርጫ በአንድ የምርጫ ክልል ውስጥ ከሚወዳደሩት ዕጩዎች መካከል አብላጫ ድምጽ ያገኘው አሸናፊ ይሆናል። በክልል ህገ መንግሥታት መሠረት ለክልል ምክር ቤቶች የሚመረጡት ተወካዮች ከአንድ በላይ ሲሆኑ ከተወዳዳሪዎቹ መካከል በቅደም ተከተል አብላጫ ድምጽ ያገኙ ዕጩዎች አሸናፊ ይሆናሉ፡፡
የክልል ምክር ቤት አባላት ምርጫን የሚመለከቱ የክልል ህጎች በህገ መንግሥቱና በዚህ አዋጅ ከተቀመጡ ምርጫን የተመለከቱ ድንጋጌዎች ጋር የተጣጣሙ መሆን ይኖርባቸዋል፡፡
#የምርጫ መርሆዎች
ማንኛውም ምርጫ ሁሉን አቀፍ፣ ቀጥተኛ፣ በምስጢር ድምፅ አሰጣጥ መራጩ ፈቃዱን በነፃነት የሚገልጽበት እና ያለ ምንም ልዩነት በሚደረግ ህዝባዊ ተሳትፎ ላይ የተመሰረተ ይሆናል፡፡
የመምረጥ ወይም የመመረጥ መብቱ በህግ ወይም በፍርድ ቤት ውሳኔ ያልተገደበ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ መምረጥ ወይም መመረጥ ይችላል፣ ሆኖም ለመምረጥም ሆነ ለመመረጥ አይገደድም፡፡
እያንዳንዱ መራጭ የሚሰጠው ድምፅ እኩል ነው፡፡
እያንዳንዱ መራጭ ድምጽ መስጠት የሚችለው በአካል በመገኘት ነው፡፡
#የምርጫ ዓይነቶች
በኢትዮጵያ የሚካሄዱ የምርጫ ዓይነቶች የሚከተሉት ናቸው፣
1. ጠቅላላ ምርጫ፣
2. የአካባቢ ምርጫ፣
3. ማሟያ ምርጫ፣
4. ድጋሚ ምርጫ፣
5. ህዝበ ውሳኔ፡፡
1. #ጠቅላላ ምርጫ
ጠቅላላ ምርጫ በየአምስት ዓመቱ የሚካሄድ የህዝብ ተወካዮች እና የክልል ምክር ቤቶች አባላት ምርጫ ነው፡፡
ጠቅላላ ምርጫ በመላ ሀገሪቱ በተመሳሳይ ጊዜ ይካሄዳል፡፡ ሆኖም ቦርዱ አስፈላጊ ሆኖ ሲያገኘው እና ጉዳዩ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀርቦ ውሳኔ ሲያገኝ በተለያየ ጊዜ እንዲካሄድ ሊያደርግ ይችላል፡፡
ለኢ.ፌ.ዴ.ሪ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከአንድ የምርጫ ክልል አንድ ተወካይ ብቻ ይመረጣል፡፡
የክልል ምክር ቤቶች አባላት ቁጥር በየክልሉ ህግ መሠረት የሚወሰን ሆኖ ከአንድ የምርጫ ክልል ከአንድ ተወካይ በላይ ለክልል ምክር ቤቶች አባልነት ሊመረጥ ይችላል፡፡ ክልሎች የምክር ቤቶቻቸውን አባላት ቁጥር ለመቀየር የሚሰጡት ውሳኔ ከእጩዎች የምዝገባ የጊዜ ሰሌዳ ስድስት ወር አስቀድሞ መሆን ይኖርበታል፡፡
በህገ መንግሥቱ አንቀጽ 61(3) መሠረት አንድ የክልል ምክር ቤት የፌዴሬሽን ምክር ቤት አባላት በቀጥታ በህዝብ እንዲመረጡ ሲወስን ምርጫው ከጠቅላላ ምርጫ ጋር አንድ ላይ የሚካሄድ ይሆናል፡፡ ይህ ሲሆን የክልል ምክር ቤቱ ቀጣዩ ምርጫ ከመደረጉ ስድስት ወራት አስቀድሞ ውሳኔውን ለቦርዱ ማሳወቅ አለበት።
2. #የአካባቢ ምርጫ
የአካባቢ ምርጫ በህግ በተደነገገው መሠረት በየደረጃው የሚካሄድ የብሔረሰብ ዞን፣ የዞን፣ የወረዳ፣ የከተማ፣ የክፍለ ከተማ ወይም የቀበሌ ምክር ቤቶች አባላት ምርጫ ነው፡፡
የአካባቢ ምርጫ ከአንድ ምርጫ ክልል በየደረጃው ለምክር ቤቶቹ የሚመረጡት ተወካዮች ቁጥር እያንዳንዱ ክልል በሚያወጣው ሕግ ይወሰናል፡፡
በዚህ አንቀጽ ንዑስ አንቀጽ (2) የተጠቀሰው እንደተጠበቀ ሆኖ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ህገ መንግሥት አንቀጽ 55 (2) (መ) እና አንቀጽ 51(15) መሠረት የአካባቢ ምርጫዎችን በተመለከተ ሁሉም ሊያደርጋቸው የሚገቡ መለኪያዎችን የሚያስቀምጥ ህግ ሊያወጣ ይችላል።
የአካባቢ ምርጫን የሚመለከቱ የክልል ህጎች በህገ መንግሥቱ እና በዚህ አዋጅ ከተቀመጡ ምርጫን የተመለከቱ ድንጋጌዎች ጋር የተጣጣሙ መሆን ይኖርባቸዋል፡፡
በዚህ አዋጅ ለጠቅላላ ምርጫ የተደነገገው እንደ አግባብነቱ በአካባቢ ምርጫ ላይም የሚፈጸም ሆኖ ቦርዱ በየደረጃው የምርጫ ክልሎች ወይም ጣቢያዎች አደረጃጀት፣ የምርጫ አስፈጻሚዎችና ታዛቢዎች አመዳደብ፣ የመራጭ እና የእጩዎችን ምዝገባ ቦታና ሂደት፣ የግል እጩ ተወዳዳሪዎች የድጋፍ ፊርማ ብዛት እና ሌሎች ጉዳዮችን ይህን አዋጅ መሠረት በማድረግ በሚያወጣው መመሪያ ይወስናል፡፡
3. #የማሟያ ምርጫ
የማሟያ ምርጫ የሚካሄደው:-
በየደረጃው ያሉ ምክር ቤቶች በተለያየ ምክንያት የተጓደሉባቸው አባላት እንዲሟሉላቸው ለቦርዱ ጥያቄ ሲያቀርቡ፣ ወይም
ተፈጻሚነት ባለው ህግ መሠረት የቀረበ የይውረድልን ጥያቄ ተቀባይነት ሲያገኝ ነው፡፡
ቦርዱ ጥያቄው በደረሰው ስድስት ወር ባልበለጠ ጊዜ ውስጥ የማሟያ ምርጫ ያካሂዳል፡፡
በዚህ አንቀጽ ንዑስ አንቀጽ (1) እና (2) የተደነገገው ቢኖርም አንድ ምክር ቤት የሥራ ዘመኑ ሊጠናቀቅ የቀረው ጊዜ ስድስት ወርና ከዚያ በታች ከሆነ የማሟያ ምርጫ አይካሄድም፡፡
4. #ድጋሚ ምርጫ
ድጋሚ ምርጫ ከሚከተሉት ምክንያቶች በአንዱ ሊካሄድ ይችላል፣
በአዋጅ ቁጥር 1133/2011 እና በዚህ አዋጅ በተሰጠው ስልጣን መሠረት ቦርዱ የምርጫ ውጤት እንዲሰረዝና ድጋሚ ምርጫ እንዲካሄድ ሲወስን ወይም የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት በቀረበለት አቤቱታ ላይ ተመስርቶ የምርጫ መደገም ውጤትን የሚያስከትል ውሳኔ ሲወስን፣
በዚህ አዋጅ አንቀጽ 61(3) መሠረት እጩ ተወዳዳሪዎች እኩል ድምፅ በማግኘታቸው ምክንያት አሸናፊውን መለየት ያልተቻለ እንደሆነ፡፡
ድጋሚ ምርጫ ሲካሄድ:-
ሌላ አዲስ የመራጮች ምዝገባ ሳያስፈልግ በምርጫ ክልሉ ወይም ችግሩ በተከሰተባቸው የምርጫ ጣቢያዎች ተመዝግበው በነበሩ መራጮች እንደገና ይካሄዳል፣
በዚህ አንቀጽ ንዑስ አንቀጽ (1) (ሀ) መሠረት ምርጫ እንዲካሄድ ሲወሰን አዲስ የእጩዎች ምዝገባ ሳያስፈልግ ቀድሞ በተመዘገቡ እጩዎች መካከል ብቻ ይደረጋል፣
ለድጋሚ ምርጫ የምርጫ ቅስቀሳ ማድረግ የተከለከለ ነው፡፡
የድጋሚ ምርጫ ዝርዝር አፈፃፀም ቦርዱ በሚያወጣው መመሪያ ይወሰናል፡፡
5. #ህዝበ ውሳኔ
ቦርዱ በህገ መንግሥቱ ወይም በሌሎች ህጎች መሠረት አግባብ ባለው አካል ሲወሰን የህዝብን ፍላጎት ለመለካት ወይም ለመወሰን ድምጽ እንዲሰጥ ህዝበ ውሳኔ የሚሰጥበትን ምርጫ ያዘጋጃል፡፡
ህዝበ ውሳኔው እንዲካሄድ ከወሰነው አካል ጋር በመመካከር ቦርዱ ህዝበ ውሳኔ ያስፈለገበትን ጉዳይ ለመለየት በሚያስችለው መልኩ የድምጽ መስጫ ጣቢያዎችን በማደራጀት ህዝበ ውሳኔውን ያከናውናል፡፡
ቦርዱ በህገ መንግሥቱ ስልጣን ከተሰጠው አካል ጋር በመመካከር ድምጽ የሚሰጥበትን ቀን፥ በህዝበ ውሳኔው በድምጽ ሰጪነት ለመሳተፍ ማሟላት የሚገባቸውን መስፈርቶች በድምጽ መስጫ ወረቀቱ ላይ የሚሠፍረው ለውሳኔ የቀረበው አማራጭ አጻጻፍ እና የህዝበ ውሳኔውን አስመልክተው የሚደረጉ የቅስቀሳ ዓይነቶችን ይዘት ይወስናል። ዝርዝር አፈፃፀሙ ቦርዱ በሚያወጣው መመሪያ ይወሰናል፡፡ ይህም በኢትዮጵያ የምርጫ፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባና የምርጫ ሥነምግባር አዋጅ ቁጥር 1162/2011 አንቀጽ 4-7 ድረስ ተደንግጓል።
℗
#Join_our_telegram_channel
https://t.me/Consultancy2012
Call us for #Legal_Service
Tsegaye Demeke - Lawyer
7.2K views17:08