Get Mystery Box with random crypto!

በኩር ጋዜጣ Bekur Newspaper

የቴሌግራም ቻናል አርማ bekurnewspaper — በኩር ጋዜጣ Bekur Newspaper
የቴሌግራም ቻናል አርማ bekurnewspaper — በኩር ጋዜጣ Bekur Newspaper
የሰርጥ አድራሻ: @bekurnewspaper
ምድቦች: ያልተመደበ
ቋንቋ: አማርኛ
ተመዝጋቢዎች: 8.53K
የሰርጥ መግለጫ

የሰኞ ጋዜጣዎ

Ratings & Reviews

3.50

2 reviews

Reviews can be left only by registered users. All reviews are moderated by admins.

5 stars

0

4 stars

1

3 stars

1

2 stars

0

1 stars

0


የቅርብ ጊዜ መልዕክቶች 2

2022-08-26 06:09:41 አክሳሪዎቹ ጅምር ህንጻዎች ምን ይሁኑ?

ነሐሴ 16 ቀን 2014 ዓ.ም
ሕንጻዎች ከተማ ወካይ ናቸው:: ከተሞች የሚይዟቸው ህንጻዎች የወደፊት መዳረሻዎቻቸውን የሚጠቁሙ ናቸው:: በተለይም ጎብኝዎች መዳረሻቸውን ሲያስቡ መነሻ የሚያደርጉት ከተሞች ያሏቸውን ህንጻዎች ታሳቢ አድርገው ነው:: ይሁን እንጂ በተለያዩ ከተሞች የሚስተዋለው የግንባታ መጓተት ገጽታን በማደብዘዝ፣ የሥራ ዕድል ፈጠራን በመገደብ እና የተቀዛቀዘ ኢኮኖሚን በመፍጠር የሚያስከትሉት አሉታዊ ጫና ከፍተኛ እንደሚሆን ብዙኃኑን የሚያስማማ ሀቅ ነው::

ለአብነት በባሕር ዳር ከተማ በኖርኩባቸው አራት ዓመታት ውስጥ ግንባታቸው ያልተጨረሱ ግን ሙሉ ለሙሉ በሥራ እንቅስቃሴ ውስጥ ያልሆኑ ህንጻዎችን ተመልክቻለሁ:: ሕንጻዎች የብዙኃኑ የቡና ሰዓት መነጋገሪያ ናቸው::

የመነጋገሪያው ዋናው ጉዳይ ደግሞ የባለቤትነት ጥያቄ ሲሆን ተጨባጭ መልስ ግን የሚሰጥባቸው አይገኝም:: አንዳንዶች ሕንጻዎቹ የቆሙበት ቦታ የቀድሞ ባለቤት በአነስተኛ ካሳ እንዲነሳ ተደርጎ ዛሬ ላይ በከፋ ችግር ውስጥ ሊሆን ይችላል የሚል ሐሳብም ያነሳሉ::

አቶ ክንዱ ወለላው የባሕር ዳር ከተማ ነዋሪ ናቸው:: በከተማዋ በርካታ በጅምር የቀሩ ከ15 እና 20 ዓመታትን የተሻገሩ ህንጻዎችን ተመልክተዋል:: የግንባታ ባለቤቶች እነማን ናቸው? ክትትል የሚደረግባቸውስ በእነማን ነው? ለሚሉት ጥያቄዎች መልስ እንዳጡ ተናግረዋል::

‘ባለሀብቶች’ ቦታ የማግኘት ሽሚያ ውስጥ ገብተዋል:: ባለሀብቶች ለከተማዋ በሚያስፈልጉ ዘርፎች ለመሠማራት ፍላጎት ሲያቀርቡ የባለሀብቶችን የኋላ ታሪክ ማወቅ ተገቢ እንደሆነ አቶ ክንዱ ጠቁመዋል::

በተለይም የእነዚህ ባለሀብቶች የግንባታ ማጠናቀቅ ተሞክሮን መቃኘት፣ ሌላ ግንባታ ኖሯቸው ያንም አጠናቀው ወደ ሥራ በማስገባት የታለመለትን ግብ ማሳካታቸውን ማረጋገጥ ከተቻለ የግንባታ መጓተትን ለማስቀረት እንደሚያስችል ገልጸዋል::

በሌላ በኩል ደግሞ ባለሀብቶች በተለያዩ የኢንቨስትመንት ዘርፎች የሚሠማሩት ከፍተኛ ብድር ከመንግሥት በመውሰድ ነው:: ይህ ገንዘብ ቦታ ከተወሰደበት ከተማ ውጭ ለሌላ ዓላማ ውሎ በሚያመጣው ትርፍ ግንባታውን ለማጠናቀቅ ታሳቢ እየተደረገ ሊሆን እንደሚችልም አቶ ክንዱ ያምናሉ::በመሆኑም የተወሰደው ብድር የታለመለትን ግብ በማሳካት በሥራ ዕድል ፈጠራ ኢኮኖሚን ማሳደግ ካልቻለ ትርፉ ኪሳራ ነው የሚል ሐሳብም አላቸው::

የግንባታዎች መጓተትም ከግንባታ እስከ ማምረት ባሉት ሂደቶች መፍጠር የነበረበትን የሥራ ዕድል በማሳጣት ለሥርዓት አልበኝነት መንገስ ትልቅ አበርክቶ እንደሚኖረው ይረዳሉ:: ለይስሙላ ግንባታ ጀምሮ ብድር መውሰድ እና አለማጠናቀቅ ተገቢ ባለመሆኑ የሚመለከተው አካል በመገንዘብ ጠንካራ ክትትል እና ቁጥጥር ሊያደርግ እንደሚገባ አስገንዝበዋል::

በባሕር ዳር ከተማ ለረጅም ዓመታት በጅምር ላይ የሚገኙ ህንጻዎች አለመጠናቀቃቸው ጎብኝዎች የሚያድሩበት፣ የሚተኙበት…አማራጭ የመዝናኛና የማረፊያ ቦታ በማሳጣት ፍሰቱን በመገደብ፣ የተረጋጋ የገበያ ሥርዓት ለመፍጠር እክል በመሆን፣ የሥራ ተነሳሽነትን በመንቀፍ እና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴውን በማቀዝቀዝ የሚያሳድሩት ጫና ከፍተኛ እንደሚሆን የምጣኔ ሐብት ምሁሩ ውዱ ወርቁ ተናግረዋል::

እንደ ምሁሩ ገለጻ የሕንጻዎች በወቅቱ አለመጠናቀቅ ተገንብተው አገልግሎት ላይ የሚገኙ ድርጅቶች በውድ እንዲከራዩ በማድረግ ነዋሪው ለኑሮ ውድነት እንዲጋለጥ ያደርጋሉ:: ተከራይተው የሚያከራዩት ደግሞ ትርፋማነትን ታሳቢ አድርገው የሚሠሩ በመሆናቸው የሚሰጡትን አገልግሎት በማናር ብዙኃኑ ለከፋ የኑሮ ጫና እንዲዳረግ ምክንያት ይሆናሉ::

እንደ ምሁሩ ገለጻ የሰው ልጅ ትልቅ ትርፍ ማግኘትን ታሳቢ አድርጎ ወደ ሥራ ይገባል:: ወደ ግንባታ የመግቢያ እና የማጠናቀቂያ ጊዜን ታሳቢ አድርጎ መፈጸም ካልቻለ በመመሪያው መሠረት ተጠያቂ ማድረግ ይገባል። ካልሆነ ግን ቦታዎች እንዲሸጡ እና እንዲለወጡ ዕድል ይፈጥራል::

ባዶ ቦታዎች በህገወጥ መንገድ/በአየር ላይ /በመሸጣቸው እና ገንዘቡም በተመሳሳይ በአየር ላይ በመረጨቱ በገበያው ላይ ያልተገባ የዋጋ ንረት እንዲከሰት ምክንያት እንደሆነም አቶ ውዱ ጠቁመዋል:: እነዚህ አይነት አሠራሮች በየጊዜው እየጨመረ ላለው የቤት ኪራይ ምላሽ መስጠት እንዳይቻል እና በትንሽ ካፒታል ወደ ሥራ መግባትንም የሚገድቡ እንደሚሆኑ ገልጸዋል::
“ጅምር ህንጻዎችን በወቅቱ ማጠናቀቅ ቢቻል ኖሮ ዛሬ ላይ ተጨማሪ ሥራ መሥራት የሚያስችል ሀብት ለብክነት አይዳረግም ነበር” ይላሉ::
አቶ ውዱ አክለው እንደተናገሩት የቤት ኪራይ ዋጋ የግንባታ ወጪን መሠረት ያደርጋል::

በመጓተት ዛሬ ላይ የደረሱ ሕንጻዎች በወቅቱ የግንባታ ግብዓት ወጪ ቢጠናቀቁ ኖሮ የቤት ኪራይ የማኅበረሰቡን ገቢ ሊገዳደር ባልቻለ ነበር:: በተጨማሪም ዛሬ ላይ የሚገነቡ ሰዎችን የግብዓት እና የሰው ኃይል ሽሚያን ያስቀር እንደነበር እምነታቸው ነው::

እንደ ምጣኔ ሀብት ምሁሩ ትልቁ ክፍተት የሕዝብን ተጠቃሚነት ቀዳሚ ዓላማ በማድረግ ለባለሐብቶች ቦታ ያስተላለፈው የመንግሥት አካል ነው:: በመሆኑም ቦታን ከማስተላለፍ ባሻገር በተያዘላቸው ጊዜ ተጠናቀው ወደ ሥራ ግባቸውን መከታተል እና እስከ መንጠቅ የሚደርስ እርምጃ የመውሰድ ኃላፊነቱን መወጣት እንዳለበት አሳስበዋል::

የባሕር ዳር ከተማ አስተዳድር ኢንዱስትሪ እና ኢንቨስትመንት መምሪያ ኃላፊ ወ/ሮ ብርሃን ንጉሴ እንደገለጹት ቦታ ታጥሮ የሚቀመጥ እና ህንጻዎች ተጀምረው የማይጠናቀቁ ከሆነ ባሕር ዳርን የቱሪዝም፣ የኢንዱስትሪ እና ኢንቨስትመንት ከተማ ማድረግ አይቻልም:: በአሁኑ ወቅት ከከፍተኛ የትምሕርት ተቋማት እየተመረቀ የሚወጣውን ከፍተኛ ሥራ ፈላጊ መሸከም የሚችለው የግሉ ዘርፍ በመሆኑ ዘርፉን ማነቃቃት እና ችግሮችን ለይቶ መደገፍ እንደሚገባ ታምኖ ወደ እንቅስቃሴ መገባቱን አስታውቀዋል::

በከተማ አስተዳድሩ ግንባታቸው የተቋረጡ እና ታጥረው የተያዙ 73 ቦታዎች መለየታቸውንም ጠቁመዋል:: ሕንጻዎቹ በጅምር ለምን ረዥም ዓመታትን ዘለቁ? ባለቤታቸው ማነው? በሚሉት ጉዳዮች ዙሪያ ከባለሐብቶች ጋር ውይይት መደረጉንም አስታውቀዋል::

የኑሮ ውድነት እና ሀገሪቱ የቆየችበት ወቅታዊ ሁኔታ በባለሐብቶች በኩል ለግንባታ መጓተቶች በምክንያትነት የተነሱ ናቸው:: ነገር ግን እነዚህ ምክንያቶች ተቀባይነት እንደሌላቸው የገለጹት ወ/ሮ ብርሃን፣ ጥናት ተደርጎ ዝቅተኛው የግንባታ መጓተት የታየበት ህንጻ ሦስት ዓመት መሆኑን ጠቁመዋል:: ሌላው አንዱን ሳያጠናቅቁ ወደ ሌላ የኢንቨስትመንት ዘርፍ መሠማራት ለግንባታዎች መጓተት ዋናው ምክንያት መሆኑንም አንስተዋል::

ግንባታዎች በተያዘላቸው ጊዜ አለመጠናቀቃቸው በከተማዋ ገጽታ፣ በሥራ ዕድል ፈጠራ እና በኢኮኖሚ እንቅስቃሴው ላይ ከፍተኛ ጫና ማሳደሩንም መምሪያ ኃላፊዋ ገልጸዋል:: ከዚህ አንጻር ከተማ አስተዳድሩ ጅምር ሕንጻዎች እንዲጠናቀቁ እና ወደ ግንባታ መግባት ያለባቸው እንዲገቡ የሚያስችል መፍትሄ አስቀምጧል:: ይህም ባለሀብቶች ግንባታ እንዲያቋርጡ ያስገደዷቸውን ምክንያቶች እንዲያሳውቁ፣ ከመቼ ጀምሮ ወደ ግንባታ እንደሚገቡ እና መቼስ ያጠናቅቃሉ? የሚሉትን ጉዳዮችን የሚያሳውቁበት የአንድ ሳምንት ጊዜ ሰጥቷቸዋል። በመመሪያ መሰረት እርምጃ መውሰድ ካልተቻለ የተጠናቀቁ ሕጻዎችን በባሕር ዳር ማየት እንደሚናፍቅም ገልጸዋል::
1.8K views03:09
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-08-26 06:08:44
1.1K views03:08
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-08-26 06:08:17 አብዲሳ አጋ፣ አሉላ አባ ነጋ፣ ዐፄ ዮሐንስ፣ ዐፄ ቴዎድሮስ፣ ንጉሥ ጦና ወይም ሌሎች ጀግኖች ኢትዮጵያውያን ጀግንነታቸውን ለእናት ሀገራቸው ኢትዮጵያ እንጂ ለሰፈር በዳይነት አላዋሉትም:: ትልቁን የኢትዮጵያን ሥዕል ማየት የተሳነን ሰዎች ቢያንስ ሰብዓዊነትን እንኳን ብናስቀድም ጥሩ ነው:: ዘረኝነታችን እንደ ዓባይ ይገደብ ስልም ከግድቡ ብዙ እንደምናተርፍ በመተማመን ነው::

(እሱባለው ይርጋ)
በኲር ነሐሴ 16 ቀን 2014 ዓ.ም ዕትም
በአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን ዘወትር ሰኞ የምትታተመውን የበኲር ጋዜጣን ሙሉ ፒዲኤፍ
በhttp://www.amharaweb.com/Bekur ላይ ማግኘት ይችላሉ።
1.1K views03:08
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-08-26 06:08:17 ዘረኝነትም ይገደብ!

ነሐሴ 16 ቀን 2014 ዓ.ም
ከሰሞኑ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የሦስተኛ ዙር የውኃ ሙሌት እና የሁለተኛው የኃይል ማመንጫ (ተርባይን) ሥራ መጀመር ብዙዎቻችንን አስደስቶናል:: የሚገርመው ነገር ግን ኢትዮጵያዊ ሆነው “የዓባይ መገደብ ምናችን ነው?” ሲሉ የሚደመጡ ሰዎች መፈጠራቸዉ ነው:: የዓባይ ግድብ ሁሉንም ኢትዮጵያውያን በአንድነት ያስተሳሰረ ገመድ ሆኖ ሳለ እንዴት ስለ ዓባይ እና ስለ ግድቡ አይገደንም ይባላል?

የዓባይ ግድብ ኢትዮጵያውያን ህፃናት ከደብተር እና እርሳስ መግዣቸው ላይ የለገሱበት፣ ደሃ እናቶች መቀነታቸውን ፈትተው የደገፉት፣ የመንግሥት ሠራተኛው ከሌለ ጥሪቱ ግድቡን ያስቀደመበት፣ ጫማ አሳማሪዎች፣ የአካል ጉዳተኞች፣ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች እና ሌሎችም “የኔ” ብለው የገነቡት የኢትዮጵያውያን ወዝ እና ደም ያረፈበት ትልቅ ፕሮጀከት ነው::

የዚህ ዘመን ትውልድ ለሀገርህ ምን ሠራህ? ተብሎ ቢጠየቅ በአንድ ድምፅ ሊመልሰዉ የሚችለው ነገር የዓባይን ግድብ ብቻ ነው:: የዓባይ ግድብ ኢትዮጵያውያን በጋራ “የኛ” የሚሉት ያለማንም እርዳታ የገነባነው አንጡራ ሀብታችን ነው:: በዓባይ ግድብ ዙሪያ ልናመሰግናቸው እንጂ ልንወቅሳቸው የምንችል የቀደሙ መሪዎችም የሉንም::

ለሀገራችን ብቻ ሳይሆን ለአፍሪካ ብርሃን ይሆናል የምንለዉ ግድባችን ብዙ ጠላቶችን ያፈራንበት ብቻ ሳይሆን የተፈራንበት ግዙፍ መሣሪያችንም ጭምር ነው:: የዓባይ ግድብ ጉባ ላይም ተገነባ ሰከላ ላይ ጥቅሙ የሁሉም ኢትዮጵያውያን ስለሆነ ነው ሁላችንም ኢትዮጵያውያኖች በወዝ፣ በደማችን እና በፅናታችን እየገነባነው የምንገኘው:: ይሄንን የደስታችንን ምንጭ የሆነ ግዙፍ ፕሮጀክት በማሳነስ ወይም ጥላሸት በመቀባት የሚገኝ አንዳችም ትርፍ የለም:: ለምን? ቢሉ፣ ዓባይ ለሁሉም ኢትዮጵያውያን መብራትም እራትም መሆኑ አይቀርምና ነው::

ይልቁንም ዘረኝነታችንንም እንደ ዓባይ ብንገድበዉ ትልቅ የነበረችው ሀገራችን ዳግም ወደ ትልቅነቷ መመለሷ ባልቀረ ነበር:: አክሱምን የትግራይ፣ ላልይበላን የአማራ፣ ሶፍኡመርን የኦሮሞ፣ ጀጎል ግንብን የሀረር፣ የጥያ ትክል ድንጋይን የደቡብ ከማድረግ ይልቅ የቀደሙ አያቶቻችን ለኛ ለልጆቻቸው ያወረሱን ኢትዮጵያዊ ሀብቶች እንደሆኑ አድርገን ብናስብ መዳረሻችን ሩቅ በሆነ ነበር::

ጀግኖች አትሌቶቻችን በተለያዩ የዓለም አደባባዮች የኢትዮጵያን ሰንደቅ ዓላማ ከፍ አድርገው በማውለብለብ ታላቅ ሀገር እንዳለን ሲያበስሩ እኛ ግን በጎጥ እና በመንደር እሳቤ ስንውተፈተፍ እንገኛለን:: የጀግኖቹ አትሌቶቻችን ገድል በአበበ ቢቂላም፣ በምሩፅ ይፍጠርም፣ በማሞ ወልዴም፣ በደራርቱ ቱሉም፣ በኃይሌ ገብረ ስላሴም፣ በጥሩነሽ ዲባባም፣ በመሠረት ደፋርም፣ በቀነኒሳ በቀለም፣ በለተሰንበት ግደይም፣ በሠለሞን ባረጋም ሆነ በሌሎች አትሌቶቻችን ይጻፍ ስሟ የሚነግሠው እና ሰንደቅ ዓላማዋ ከፍ ብሎ የሚውለበለበው የእናት ሀገራችን የኢትዮጵያ ነው::

ኢትዮጵያውያን ሁለት ዓይነት ዜግነት ያለን ይመስል የአንዱ ብሔር ተወላጅ በሌላው ክልል እንዳይኖር መሳደዱ እና መገደሉ ለ21ኛው ክፍለ ዘመን ፈፅሞ የማይመጥን እሳቤ ነው:: በዓድዋ ጦርነት ጠላታችንን በጋራ የመከትን፣ በአትሌቶቻችን ድል በጋራ የተደሰትን እና በዓባይ ግድብ የጋራ ስኬትን እያስመዘገብን የምንገኝ ሕዝብ ስለምን በዘረኝነት ሰይፍ እንተራረዳለን? ለዚህም ነው ዘረኝነትንም እንደ ዓባይ እንገድበዉ ማለቴ::

ከትንሽነት የሚገኘው ጥቅም ባይገባኝም ታላቋን ኢትዮጵያ ወደ ትናንሽ ኢትዮጵያዎች ለመከፋፈል የሚደረገው ጥረት ግን አደገኛነቱ አያጠራጥርም:: የቀድሞዋ ሶቪየት ሕብረት በመፈራረሷ ተጠቀመች ወይስ ተጎዳች? የሚል ጥያቄ ማንሳት አልፈልግም:: የኢትዮጵያውያንን ኃይል ለመበታተን የሰሞነኛዉ ነጠላ ዜማ “ክልል እንሁን” የሚል መሆኑ በእጅጉ ያስፈራኛል::

የአማራን ክልል ጎንደሬ፣ ጎጃሜ፣ ወሎዬ፣ ሽዋ፣ አገው፣ ቅማንት ብሎ ለመከፋፈል የሚደረገው ጥረት ሳያንስ ወሎ ክልል ይሁን ወይም ጎንደር ክልል ይሁን ብሎ ጥያቄ የአማራነት ወይም የኢትዮጵያዊነት ነፀብራቅ አለመሆኑ ልብ ሊባል ይገባዋል:: አንድ አማራን ከመፍጠር ይልቅ የተበታተነ አማራን ለመፍጠር የሚደረገዉ ጥረት ሀገር አፍራሽነት መሆኑም ሊታወቅ ይገባል::

የአማራን ክልል ለአብነት አነሳሁ እንጂ ከደቡብ ሕዝብ የሚሰሙት የክልል እንሁን ጥያቄዎችም መሠታቸዉ ክልል በመሆን የሕዝቡን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ሳይሆን ለግል ሥልጣን እና ጥቅማ ጥቅም በዘረኛ ፖለቲከኞቻችን የሚደረግ ሩጫ መሆኑን መገንዘብ አያዳግተንም:: እዚህም ላይ ዘረኝነታችን እንደ ዓባይ እንዲገደብልን መመኘታችን ስህተት አይሆንም::

ኢትዮጵያ እና ኤርትራ በሕዝበ ውሳኔ ተለያይተው ኢትዮጵያ ወደብ ማጣቷ ወይም ኤርትራ የምግብ ሰብል በማጣቷ የሚጎዳው ማነው ካልን “ሁለቱም” የሚለው ትክክለኛው መልስ ይመስለኛል:: በኦሮሚያ፣ አማራ፣ ደቡብ ወይም አፋር ክልል ከፍተኛ ድርቅ ቢከሰት (አይበልብንና) የሚጎዱት በድርቁ አካባቢ የሚገኙት ሰዎች ብቻ ናቸው ወይስ ሁላችንም እንደ ሀገር እንጎዳለን? ብለን ከጠየቅንም መልሱ የሚሆነው ሁላችንም እንደ ሀገር እንጎዳለን የሚል ነው::

የኢትዮጵያ ብሔራዊ የወንዶች እግር ኳስ ቡድን በቅርቡ የግብፅ አቻውን ሲያሸንፍ ያልተደሰተ ኢትዮጵያዊ ማነው? በእርግጠኝነት “ማንም” ብዬ መመለስ እችላለሁ:: ምክንያቱም ያሸነፍነው እንደ ብሔር ሳይሆን እንደ ሀገር ስለሆነ ነው:: ያሸነፍነው እንደ ቋንቋችን፣ እምነታችን ወይም ሌላ ሳይሆን እንደ ኢትዮጵያዊነታችን ስለሆነ ነው:: ለዚያም ነው ከብሔር ስኬት በላይ ብሔራዊ ስኬቶቻችን ደምቀው የሚያደምቁን::

በተለያዩ ክልሎች ብሔርን፣ ቋንቋን፣ ዘርን፣ ሀይማኖትን እና ማንነትን መሰረት ያደረጉ ግጭቶች እየተከሰቱ ክቡር የሆነው የሰው ልጅ ህይወት አልፏል:: በርካታ ንብረት ወድሟል::

በርካቶችም ተሰደዋል:: በእነዚህ ግጭቶች የተሰው ዜጎች ባይሰው ኖሮ የምናጣው ምንድ ነው? የወደሙት ንብረቶችስ ቢሆኑ በተዘዋዋሪም ቢሆን ለአውዳሚዎቹ አይጠቅሙም ነበር? መልሱን ለንፁህ ህሊናችሁ ትቼዋለሁ:: (በእርግጥ ንፁህ ህሊና ያለው ሰው ንፁሃንን አይገድልም::)

ከዘረኝነት ተጠቃሚ የለምና ዘረኝነታችንን እንደ ዓባይ እንገድበው ስል በሀሳቤ የማይስማሙ ይኖራሉ:: ምክንያቱም በዘረኝነት የሚነግዱት ብዙዎች ስለሆኑ ነው:: የዘር ፖለቲካ ለሕዝባችን እንደማይጠቅመው እያወቁ ዘረኝነትን እና መከፋፈልን የሚያቀነቅኑት ፖለቲከኞች የእነሱ ኪስ እስኪሞላ ድረስ ጥላቻ እና ዘረኝነት ሞልቶ ቢፈስም ግድ አይሰጣቸውም::

ኢትዮያጵያችን በጉባ በረሃ ላይ እየገነባችው የሚገኘው ታላቁ የህዳሴ ግድብ ለኢትዮጵያውያን ምን ይጠቅማል? ብሎ ጥያቄ ማቅረብ ለሳውዲዎች የተፈጥሮ ነዳጅ ምን ያደርግላቸዋል? ለብራዚሎች ቡና ምን ጠቀማቸው? ለሩሲያ የሰብል ምርት ምን ያደርግላታል? ብሎ ከመጠየቅ አይተናነስም:: ይልቁንም የዓባይ ግድብ ሙሉ በሙሉ በስኬት ተጠናቆ የኃይል እጥረታችን በተወገደልን ብሎ መመኘት የዋህነት ሳይሆን ብልህነትም ጭምር ነው::

ይልቁንም ዘረኝነታችን እንደ ዓባይ ተገድቦ ኢትዮጵያውያን በጋራ ሆነን እንደ አትሌቶቻችን እና እንደ ዓድዋ ጀግኖቻችን ታሪክ ሠርተን ሀገራችንን ወደ ከፍታዋ የምንመልስበት ጊዜ ቅርብ እንዲሆን እንመኝ:: ዘረኛ ፖለቲከኖቻችን ሕዝብን በመከፋፈል ከምታገኙት ጥቅም ይልቅ ለሕዝብ ዕውቀታቻሁን በማካፈል የነገዋን ብሩህ ኢትዮጵያ በጋራ እንገነባት ዘንድ አግዙን!
1.4K views03:08
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-08-22 14:52:39
2.3K views11:52
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-08-22 14:52:14 ከ2010 ዓ.ም ጀምሮ ለአማራ ክልል እና ለሕዝቡ ከበጀት አንፃር ምን ለውጥ ተገኘ?
ለለውጡ መምጣት አንዱ ገፊ ምክንያት የሆነው ኢ - ፍትሐዊ የሆነው የሀብት ክፍፍል እና ኢ- ፍትሐዊ የሆነ የፕሮጀክት ስርጭት መኖሩ ነው:: የፌዴራል መንግሥቱ እነዚህን ችግሮች ገምግሞ የሄደባቸው መንገዶች አሉ:: ለምሳሌ በመንገድ መሰረተ ልማት ላይ ጥናቶች ተደርገው ኢ- ፍትሐዊ የመንገድ ልማት እንደነበረ ተረጋግጧል:: ያንን መሰረት አድርጎ ማስተካከያዎችን ለማድረግ ተሞክሯል::

ከቀመር ውጪ የሆኑ እና ግልፅነት የጎደላቸው የበጀት ዓይነቶች ወደ ክልሎች መሄዳቸውን ተከትሎ በለውጡ የተሰሩ ሥራዎች አሉ:: ግልፅ የሆነ የበጀት ቀመር እና አመዳደብ እንዲኖር የፌዴሬሽን ም/ቤቱ እየሠራ መሆኑም በለውጥነቱ እና በበጎ ጎኑ የሚታይ ነው:: ሁሉም ክልሎች ፍትሐዊ የሆነ እና በቀመር የተሰላ የሀብት ክፍፍል እንዲኖራቸው የፌዴሬሽን ም/ቤት የቤት ሥራውን እየሠራ ይገኛል::

በውጥን የቀሩ ፕሮጀክቶች ዕጣ ፈንታቸው ምን ይሆን?
በጅምር የቀሩ ፕሮጀክቶች ባለቤቶች ቢሮዎች ናቸው:: ቢሮዎች ያሏቸውን ፕሮጀክቶች አና የቆሙም ካሉ የቆሙበትን ምክንያት ገምግመው እንዲያቀርቡ ተነግሯቸዋል:: የቢሮዎቹ ሪፖርት ተገምግሞ በካቢኔ ደረጃ ውሳኔ የሚያገኝ ይሆናል:: በዋጋ ንረት የቆሙ እና የተቋረጡ ብዙ ፕሮጀክቶች እንዳሉ እናውቃለን:: በእርግጥም የዋጋ ንረቱ ለፕሮጀክቶች መጓተትም ሆነ መቋረጥ ምክንያት እንደሆነ አኛም ተገንዝበናል:: በዚሁ ጉዳይ ላይ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ቢሮ ጥናቶችን አስደርጎ የ30 ከመቶ የዋጋ ማስተካከያ እንዲረግላቸው ውሳኔ ላይ ተደርሷል::

በጀቱ ምንም እንኳን በቂ ነው ባይባልም የክልሉ መንግሥት ጭማሬውን ያደረገው ካለው አቅም አንፃር በመሆኑ በጭማሬው የሚጠናቀቁ ፕሮጀክቶች ይኖራሉ ብለን ተስፋ እናደርጋን:: በዚህ ውሳኔ መሰረት ወደ ሥራ የሚገቡ ፕሮጀክቶች እንዳሉት ሁሉ የማይገቡም ይኖራሉ:: የማይገቡት ችግራቸው ለርዕሰ መስተዳድር ቢሮ ቀርበው ውሳኔ የሚሰጥባቸው ይሆናል::

በክልሉ በጀት በአግባቡ እና በፍትሐዊነት ለመጠቀም ምን ታቅዷል?
በጀት አብዛኛውን ጊዜ በቂ አይደለም ካልን መጠቀም ያለብንም በቁጠባ ነው:: በጀትን ቅድሚያ ለሚሰጣቸው ፕሮጀክቶች እና ጉዳዮች በአግባቡ በመጠቀም ፍትሐዊ ማድረግ ይቻላል:: ስለ በጀት እጥረት እያወራን ብክነት መኖር የለበትም:: የሥራዎችን ቅደም ተከተል ማስቀመጥ ያስፈልጋል:: ለሁሉም ሥራዎቻችን በጀትን መበተን ብክነትን እንጂ ውጤትን አያስገኝም::

ከቁጠባ ጋር ተያይዞ እንደ ክልል የጀማመርናቸው ሥራዎች አሉ:: ለአብነትም ከመስተንግዶ ጋር የሚያያዙ ወጪዎች እንዲቀንሱ ተደርጓል:: ቲሸርት እና ኮፍያዎች እንዳይታተሙ ተደርጓል:: እነዚህ ነገሮች አስፈላጊ ናቸው ቢባል እንኳን ካሉብን ብዙ ችግሮች አንፃር እንደማያስፈልጉን ታምኖባቸው የቀሩ የበጀት መቆጠቢያዎች ናቸው::
በጀት ፍትሐዊ የሚሆነው የበጀት ምዝበራ ሲወገድ እና በጀትን በቁጠባ መጠቀም ሲቻል ነው:: ለሕዝብ አገልግሎት ለሚውሉ ፕሮጀክቶች ቅድሚያ መስጠትም ሕዝብን ተጠቃሚ የማድረግ እና በጀትን በአግባቡ የመጠቀም አንዱ አካል ነው::

ለሰጡን ማብራሪያ እጅግ አድርገን እናመሰግናለን!

እኔም የጋዜጣዋ እንግዳ በመሆኔ ከልቤ አመሰግናለሁ!

(እሱባለው ይርጋ)
በኲር ነሐሴ 16 ቀን 2014 ዓ.ም ዕትም
በአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን ዘወትር ሰኞ የምትታተመውን የበኲር ጋዜጣን ሙሉ ፒዲኤፍ
በhttp://www.amharaweb.com/Bekur ላይ ማግኘት ይችላሉ።
2.0K views11:52
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-08-22 14:52:14 የክልሉ በጀት አሰባሰብ በምን ደረጃ ላይ ይገኛል? የአሰባሰብ ችግሮች ካሉስ እንዴት ለመፍታት ታቅዷል?
የክልሉ በጀት የሚሟላው በሁለት መንገዶች ነው:: አንደኛው ከፌዴራል መንግሥት የበጀት ድልድል ቀመርን ታሳቢ አድርጎ የሚመደብ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ክልሉ ከራሱ ከልዩ ልዩ የገቢ አርዕስቶች የሚሰበስበው ነው:: የፌዴራል መንግሥቱ በዚህ በጀት ዓመት ከባለፉት ዓመታት ጋር ሲነፃፀር በክልሉ ከሚመደበው በጀት እኩል ነው የመደበው:: ዘንድሮ ክልሉ 50 ነጥብ አንድ በመቶ በጀት ሊያመነጭ ያቀደ ሲሆን የፌዴራል መንግሥቱ ግን ከዚህ በፊት የሚደለድለው በጀት ከፍተኛ የነበረ ሲሆን አሁን ላይ ክልሎች በራሳቸው የሚያመነጩት በጀት እንዲያድግ ተደርጓል::

ከፌዴራል መንግሥቱ የምናገኘው የ49 ነጥብ ዘጠኝ ከመቶ በጀት በየወሩ የሚላክልን እና በዓመቱም ሙሉ በሙሉ የሚሰበሰብ ነው:: ክልሉ በራሱ አቅም የሚያመነጨው እና የሚሰበስበው በጀት ላይ ግን ከፍተኛ ትኩረት ሰጥቶ መሥራትን ይጠይቃል:: እስካሁን የደረጃ ሐ ግብር ከፋዮች ብቻ ናቸው ግብራቸውን የሰበሰቡት:: በቀጣይ ከደረጃ ለ፣ ከደረጃ ሀ፣ ከልዩ ልዩ ገቢዎች እና ከፊዴራል መንግሥት የምናገኘው የጋራ ገቢ ውስጥ የሚሰበሰብ ይሆናል::

እነዚህ የግብር ዓይነቶች እንዲሰበሰቡ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ ነው:: ለግብር አሰባሰቡ ይረዳ ዘንድም መመሪያዎች ተሻሽለው እየወጡ ይገኛሉ:: መመሪያ ያልነበራቸውም መመሪያ እንዲወጣላቸው እየተደረገ ነው::ግብር መሰብሰብ የአንድ ተቋም ሥራ ብቻ ባለመሆኑ ከንግድ ቢሮ ጋር፣ ከከተማ አና መሠረተ ልማት ቢሮ ጋር፣ ከፀጥታ አካሉ ጋር፣ ከፍትህ አካሉ ጋር፣ ከመሬት አስተዳደር እና ከገንዘብ ቢሮ ጋር በቅንጅት በመሥራት ለመሰብሰብ የታቀደውን ግብር መሰብሰብ ይቻላል:: ገቢን በመሰብሰብ በኩል ሁሉም አመራርም የድርሻውን ሊወጣ ይገባል::

የክልሉ በጀት በጦርነት የወደመውን የክልሉን ሀብት ታሳቢ ያደረገ ነወይ?
በመጀመሪያ በክልሉ ላይ የደረሰው ጉዳት ምን ያህል ነው? የሚለውን ማየት ያስፈልጋል:: ከሰኔ 2013 እስከ ታህሳስ 2014 ዓ.ም ድረስ በትግራይ ወራሪ ኃይል ምክንያት የደረሰው ጉዳት ሲጠና ከ290 ቢሊዮን ብር በላይ ነው:: ሌሎች መጠናት ያለባቸው በኦነግ ሸኔ የወደሙ መሰረተ ልማቶች፣ ከፅንፈኛው ቅማንት ጋር ተያይዞ የወደሙ ሀብቶች፣ ከሱዳን ወረራ ጋር ተያይዞ በምዕራብ ጎንደር አካባቢ የወደሙ ንብረቶች እና ከጉሙዝ አማፂ ጋር ተያይዞ በአዊ አካባቢ የወደሙ ንብረቶች ላይ ጥናት ማካሄድ ያስፈልጋል::

ከላይ በተዘረዘሩት አካባቢዎች ከወደሙት ንብረቶች በተጨማሪ ተፈናቃዮችን ያስጠለሉ ከተማ አስተዳደሮች እና ወረዳዎችም ብዙ የበጀት ችግር አጋጥሟቸዋል:: ስለዚህ ጦርነቶች በተካሄዱባቸው አካባቢዎች ብቻ ሳይሆን በአቅራቢያቸው በነበሩ ወረዳዎች እና ከተማዎችም ላይ ጦርነቱ ከፍተኛ ጉዳት አስከትሏል:: እነዚህ ሁሉ ጉዳቶች መጠናት አለባቸው:: በቅደም ተከተልም እየተጠኑ ይገኛሉ:: በቅደም ተከተልም መፍትሄ ሊበጅላቸው ይሞከራል::

የትግራይ ወራሪ ኃይል ከሰኔ እስከ ታህሳስ ያደረሰው ጉዳት የተጠና ቢሆንም እስካሁንም ያልለቀቃቸው አካባቢዎች ስላሉ የጉዳት መጠኑን በትክክል ማወቅ አልተቻለም:: በተጠኑ አካባቢዎች ያለው የ290 ቢሊዮን ብር ጉዳትም ወደፊት ነፃ በሚወጡ አካባቢዎች ልክ የሚጨምር ይሆናል:: ይሄንን ጉዳት በክልሉ መንግሥት የበጀት ድጎማ ብቻ ማስተካከል አይቻልም:: ዘጠና አምስት ነጥብ ሦስት ቢሊዮን ብር ዓመታዊ በጀት ለያዘ ክልል በተገኘው የጥናት ውጤት መሰረት ያለውን የ290 ቢሊዮን ብር ጉዳት መልሶ ማቋቋም አይቻልም:: በክልሉ መንግሥት አቅም ሳይሆን እንደ ሀገርም ለመልሶ ግንባታው የፌዴራል መንግሥቱም አቅም ምላሽ ሊሆን አይችልም::

የክልሉ መንግሥት ለዚህ ችግር መፍትሄ የሚያፈላልግ የመልሶ መቋቋም እና ግንባታ ፕሮጀክት ፈንድ ጽ/ቤት አቋቋሟል:: ይህንንም የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት /UNDP/ የበጀት ድጋፍ እያደረገ ሀብት የማሰባሰብ ሥራ እየተሠራ ነው:: ሀብቱ የሚሰበሰበው ከፌዴራል መንግሥት፣ ከዓለም አቀፍ ድርጅቶች፣ ከዲያስፓራው ማህበረሰብ እና ከሌሎችም ነው::

የፌዴራል በጀት ድልድሉ ፍትሐዊ ነው? ካልሆነ እንዴት መስተካከል ነበረበት?
በፌዴራል መንግሥት ከተያዘው አጠቃላይ በጀት ላይ ለክልሎች የተደለደለው 26 ከመቶ ብቻ ነው:: ከአምናው ጋር ሲታይም ጭማሪው አነስተኛ ነው:: ክልሎች ካሉባቸው በርካታ ችግሮች አንፃርም በጀቱ አነስተኛ ነው:: ወደፊት የፌዴራል መንግሥቱ በክልሎች በጀት ላይ ያለውን ጫና በመገንዘብ የጥቅል በጀት ድጎማውን ያሳድገዋል የሚል ተስፋ አለን::

ፌዴራል መንግሥቱ ሀገሪቱ ከነበረችበት ጦርነት አንፃር የበጀት ችግር እንደሚኖርበት እሙን ነው:: ይህንን እና ሌሎችንም ሀገራዊ ወጪዎች ታሳቢ በማድረግ እንጂ በፌዴራል መንግሥቱ በኩል ለክልሎች የተደረገው የበጀት ጭማሪ በቂ ነው ብለን አናስብም:: በተለይም የአማራ ክልል ጦርነት የተካሄደበት እና ከ90 ወረዳ እና ከተማ አስተዳደር በላይ በጦርነት የተጎዱ ናቸው:: ጦርነቱን ለመደገፍ ሲባልም የካፒታል በጀቶችን ሁሉ ለጦርነቱ በማዋል የተጎዳ ክልል በመሆኑ የበጀት ጭማሪው ከክልሉ ጉዳት ጋር ተመጣጣኝ አይደለም::

ከኅብረተሰቡ ጉሮሮ በመነጠል፣ መደበኛ በጀትን በማጠፍ ለጦርነቱ እገዛ እንዳደረገ ክልል በተለየ የተመደበለት በጀት የለም:: ይሄ ችግር የአፋርንም ክልል የሚመለከት ነው:: ምናልባትም ወደፊት ራሱን ችሎ በጦርነት የወደሙ አካባቢዎችን ለመደገፍ የሚያስችል በጀት በፌዴራሉ መንግሥት በኩል እንዳለ መረጃው አለኝ:: ያ በጀት በምን አግባብ ድልድል ይሰራለታል የሚለውን ወደፊት የምናየው ይሆናል:: እንደ ዓለም ባንክ ያሉ እና ሌሎችም ዓለም አቀፍ ተቋማት ግን ይህንን ችግር ዝም ብለው ይተውታል ብለን አናስብም::

በክልሎች መካከል ያለው የበጀት ድልድልስ ፍትሐዊ ነው?
የአማራ ክልልን የበጀት ድልድል በተመለከተ ከሕዝብ እና ቤት ቆጠራ ጋር አያይዘን ደጋግመን የምናነሳው ጉዳይ አለ:: በ1999 ዓ.ም የሕዝብ እና ቤት ቆጠራ ሲካሄድ ትክክለኛ ቆጠራ አልተካሄደም፤ ትክክለኛ መረጃዎችም አልተያዙም፤ የአማራ ክልል ሕዝብና ቤት ቆጠራ መረጃ ትክክል አይደለም የሚሉ ቅሬታዎችን በተደጋጋሚ እናነሳለን::ያንን የሚያረጋግጡ መረጃዎችም አሉ:: ይህ በሆነበት ሁኔታ የፌዴራል መንግሥቱ ለክልሎቹ የሚሰጠው ጥቅል በጀት የሚደለደልበት ቀመር በአብዛኛው ከሕዝብ ቁጥር ጋር የተያያዘ ነው::
የውኃ፣ የመንገድ፣ የጤና እና የትምህርት ሽፋን መሰረት የሚደረጉት በሕዝብ ቁጥር ላይ ነው::

ስለዚህ በአማራ ክልል በጀት ላይ የቀደመው የሕዝብ እና ቤት ቆጠራ በእጅጉ ተፅዕኖ ያሳድራል:: ለዚህ ጥያቄ ፍትሐዊ ምላሽ የሚሰጠው ወደፊት የሚደረገው የሕዝብ እና ቤት ቆጠራ ወይም ፓለቲካዊ ውሳኔ ብቻ ነው::

በአማራ ክልል የተካሄደው የ1999ኙ የሕዝብ እና ቤት ቆጠራ ትክክለኛውን መረጃ ያልያዘ በመሆኑ ፍትሐዊነትን አጓድሏል የሚል ቅሬታችንን እያነሳን ነው:: ወደፊትም ማንሳታችንን እንቀጥላለን:: በጥቅሉ ግን የአማራ ክልል በጀት ባደረ የፓለቲካ ሸፍጥን የተጎዳ ነው ማለት ይቻላል::
1.3K views11:52
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-08-22 14:52:14 የአማራ ክልል በጀት ባደረ የፖለቲካ ሸፍጥ እየተጎዳ ነው

ነሐሴ 16 ቀን 2014 ዓ.ም
ተወልደው ያደጉት በአማራ ክልል፣ ምዕራብ ጎጃም ዞን፣ ደምበጫ ከተማ ነው:: የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርታቸውን እዚያው ደምበጫ በሚገኘው አዲስ አምባ ትምህርት ቤት እና የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን ደግሞ በደምበጫ ከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት ተከታትለዋል:: በ1989 ዓ.ም ለከፍተኛ ትምህርት የሚያበቃቸውን ውጤት አምጥተው በያኔው ጅማ ጤና ሳይንስ ኮሌጅ፣ በአሁኑ ጅማ ዩኒቨርሲቲ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን በአካውንቲንግ አግኝተዋል::

ሁለተኛ ዲግሪያቸውን ከህንዱ አንድራ ዩኒቨርሲቲ በፋይናንስ እና ማርኬቲንግ በ1999 ዓ.ም ያገኙ ሲሆን ሦስተኛ ዲግሪያቸውንም በዚያው በህንድ ሀገር ከሚገኘው ፉንጃቢ ዩኒቨርሲቲ በቢዝነስ ትምህርት ለመመረቅ ችለዋል:: ከጅማ ዩኒቨርሲቲ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን ካገኙ በኋላ በባሕር ዳር ከተማ በሚገኘው የኦዲት ቢሮ በኦዲተር ባለሙያነት ተቀጥረዉ ሥራቸውን ጀምረዋል::

ከክልሉ ኦዲት ቢሮ የጎንደር ዩኒቨርሲቲን በመምህርነት የተቀላቀሉት የዚህ ዕትም እንግዳችን በጎንደር ዩኒቨርሲቲ ለስምንት ዓመታት በመምህርነት እና በተለያዩ የኃላፊነት ቦታዎች ላይ ካገለገሉ በኋላ ወደ ደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ ተዛውረው በዚያም በተለያዩ የኃላፊነት ቦታዎች ላይ ለስድስት ዓመታት አገልግለዋል:: በደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ እያሉ ሦስተኛ ዲግሪያቸውን አጠናቀው የክልሉ ገንዘብ እና ኢኮኖሚ ትብብር ቢሮ ኃላፊ በመሆን እያገለገሉ ይገኛሉ: :ከእንግዳችን ዶ/ር ጥላሁን መሐሪ ጋር በክልሉ የ2015 ዓ.ም በጀት እና ከበጀት ጋር ተያያዥ ጉዳዮች ቆይታ አድርገናል::
መልካም ንባብ!

የክልሉ በጀት ምን ያህል እና ለምን ጉዳዮች የሚውል ነው?
ለአማራ ክልል በ2015 ዓ.ም የታወጀው አጠቃላይ በጀት 95 ነጥብ ሦስት ቢሊዮን ብር ነው:: በጀቱን ከ2014 ዓ.ም በጀት ጋር ካነፃፀርነው የ15 ነጥብ ሁለት ቢሊዮን ብር ብልጫ አለው:: በመቶኛ ስንለካውም የ19 በመቶ ዕድገት አለው:: በጀቱ በክልሉ ውስጥ ከሚገኙ የተለያዩ የገቢ ማመንጫዎች (አርዕስቶች) እና ከፊዴራል መንግሥት በድጎማ የሚገኝ ነው::

በጀቱ ሲደለደል የክልሉ መንግሥት የትኩረት አቅጣጫዎቼ ናቸው ያላቸው ጉዳዮች አሉ:: እነሱም የግብርናው፣ የቱሪዝሙ፣ የኢንዱስትሪ እና ኢንቨስትመንቱ እንዲሁም የማዕድኑ ዘርፍ፣ በትግራይ ወራሪ ኃይል የወደሙ መሰረተ ልማቶች መልሶ ግንባታ፣ ነባር ፕሮጀክቶችን ማጠናቀቅ እና የክልሉን የፀጥታ ዘርፍ ማጠናከር ናቸው::

ክልሉ በግብርናው ዘርፍ ትልቅ ሀብት ስላለው ይሄንኑ ታሳቢ ያደረገ በጀት ይዟል:: የቱሪዝም ዘርፍ ክልሉ በአግባቡ ያልተጠቀመበት ግን ደግሞ ብዙ የጎብኝዎች መዳረሻዎች ያሉበት በመሆኑ ዘርፉን ለማሳደግ እና ለማዘመን ታሳቢ ያደረገ በጀት ተይዟል:: የክልሉን ሕዝብ የአኗኗር ሁኔታ እንቀይረው፣ ለዜጎች በርካታ የሥራ ዕድሎችን እንፍጠር ከተባለ ኢንዱስትሪ እና ኢንቨስትመንቱን ማጎልበት የግድ ይሆናል::
በቡሬ እንደገነባው የግብርና ምርቶች ማቀነባበሪያ ዓይነት ኢንዱስትሪ በሌሎችም ቦታዎች መገንባት እና ማስፋፋት ያስፈልጋል:: ደብረ ብርሃን፣ ኮምቦልቻ እና ባሕር ዳር ላይ ያሉት የኢንዱስትሪ መንደሮችም ውጤታማ መሆን ይጠበቅባቸዋል:: የግል ባለሀብቶች በዚህ ዘርፍ ላቅ ያለ ሚና እንዳላቸው ታሳቢ በማድረግ ጭምር ለዘርፉ ውጤታማነት የሚያግዝ በጀት ተደልድሏል::

ክልላችን ያሉትን የማዕድን ሀብቶች በሚፈለገው ደረጃ አውጥቶ እየተጠቀመባቸው አይደለም:: ስለዚህ በአዲሱ የበጀት ድልድል የማዕድን ዘርፉም ትኩረት ተሰጥቶታል::

የትግራይ ወራሪ ኃይል ያወደማቸውን ተቋማት መልሶ መገንባትም በቂ ባይሆንም የበጀት ትኩረት ከተሰጣቸው ጉዳዮች ውስጥ በቀዳሚነት ተቀምጧል::
በክልሉ የተጀመሩ ፕሮጀክቶችን ለማጠናቀቅ እና ወደ ልማት ለማስገባት ትኩረት የሚሰጥ ሲሆን በአዲሱ በጀት ዓመት አዳዲስ ፕሮጀክቶች አይጨመሩም:: የክልሉን ሰላም እና ፀጥታ ለመጠበቅ በሁሉም ዘርፍ የሚገኙ የፀጥታ አካላትን ለማጠናከር ይሰራል:: ሌላው የፌዴራል መንግሥትን በጀት ጨምሮ ለመስኖ ልማት ልዩ ትኩረት ይሰጣል::

እንደ ርብ እና መገጭ ያሉ የመስኖ ፕሮጀክቶች ግን አሁንም ድረስ የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ሆነው ቀጥለዋል፤ ለምን?
የርብ እና የመገጭ መስኖ ፕሮጀክቶች በርካታ ዓመታትን ያስቆጠሩ ፕሮጀክቶች ናቸው:: የፕሮጀክቶቹ ባለቤት እና በጀቱም የፌዴራል መንግሥት ቢሆንም ጠቀሜታቸው ለክልሉ መንግሥት እና ለሀገር መሆኑ ይታወቃል::

እነዚህ ፕሮጀክቶች በተያዘለቸዉ ዕቅድ መሰረት ባለመጠናቀቃቸው መንግሥትን በርካታ ወጪ ከማስወጣታቸው በተጨማሪ ክረምት በመጣ ቁጥር የአካባቢውን ነዋሪዎች በጎርፍ አደጋ እያሰቃዩት ይገኛሉ:: ስለዚህ እነዚህ ፕሮጀክቶች በሚፈለገው ደረጃ ተጠናቀው ወደ ሥራ እንዲገቡ በመስኖ እና ቆላማ አካባቢዎች ቢሮ በኩል ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቷቸው እየተሰራ ይገኛል::

የክልሉ መንግሥት ለሁለቱ ፕሮጀክቶች ልዩ ትኩረት በመስጠት፣ በመደገፍ፣ በመከታተል እና ግምገማ በማድረግ ፕሮጀክቶቹ ለአርሶ አደሮች የሥጋት ምንጭ ሳይሆኑ ጠቃሚው እንዲሆኑ እየሰራ ይገኛል:: የፌዴራል መስኖ እና ቆላማ አካባቢዎች ሚኒስቴርም ፕሮጀክቶቹን በተለየ መንገድ መከታተል ጀምሯል::
እነዚህ ፕሮጀክቶች ሁሌ የመልካም አስተዳደር ችግሮች ሆነው እንዲቀጥሉ ክልሉ ፍላጎት የለውም:: የበጀት መጠየቂያ ርዕስ ሆነው እንዲቀጥሉም አይፈለግም፤ በአፋጣኝ መጠናቀቅ አለባቸው:: የማይጠናቀቁ ከሆነ ለፕሮጀክቶቹ የፈሰሰው ገንዘብ ሀገራዊ ክስረት ይሆናል::

ለርብ እና መገጭ መስኖ ፕሮጀክቶች መጠናቀቅ የክልሉን መስኖ እና ቆላማ ቦታዎች ቢሮን ጨምሮ ርዕሰ መስተዳድሩም ጭምር ልዩ ትኩረት የሰጧቸው ናቸው:: እነዚህ ፕሮጀክቶች በሦስተኛ ወገን የይዞታ ቦታ እና በመሰል እንቅፋቶች ሳይቆራረጡ ለታለመላቸው ዓላማ እንዲውሉ ክልሉም ሆነ የፌዴራል መንግሥቱ ትኩረት ሰጥተው ይሰራሉ ብለን እናስባለን::
የበጋ ስንዴን በስፋት ለማምረትም የእነዚህ ፕሮጀክቶች ፋይዳ ብዙ ስለሆነ ልዩ ትኩረት እንደሚያገኙም እርግጠኞች ነን::

የክልሉ አዲሱ በጀት በቂ አይደለም ለሚሉ የኅብረተሰብ ክፍሎች የቢሮው ምላሽ ምን ይሆን?
የትኛውም ቦታ እና ሀገር ላይ በቂ በጀት የለም:: ፍላጎትን እና አቅርቦትን በፍፁም ማመጣጠን አይቻልም:: ከኛ ሀገር በጀት አንፃር ስናየውም የት የለሌ ለሆነው ፍላጎታችን የሚመጥን በጀት ሀገሪቱ የላትም:: ስለዚህ በጀቱ በቂ አይደለም የሚለው ሀሳብ ሁላችንንም የሚያስማማን ነው:: ለምሳሌ የክልሉ አጠቃላይ በጀት 95 ነጥብ ሦስት ቢሊዮን ሆኖ እያለ በክልል ቢሮዎች ብቻ (ወረዳዎችን ሳይጨምር) የቀረበው ፍላጎት ከ70 ቢሊዮን ብር በላይ ነው:: ስለዚህ ባለው በጀት በአግባቡ መጠቀም እንጂ ፍላጎትን እና አቅርቦትን ማመጣጠን ያስቸግራል::
893 views11:52
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-08-22 14:51:46
793 views11:51
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-08-22 14:51:08 የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት በልማት እናረጋግጥ!

ነሐሴ 16 ቀን 2014 ዓ.ም
የውጭ ተፅዕኖም ሆነ የሀገር ውስጥ ጊዜያዊ ችግር የማይበግረው የኢትዮጵያዊያን የዘመኑ የአንድነት ምልክት ነው፤ ወደ ዘላቂ የውሃ ሀብት ልማት የምናደርገው ጉዞ በትክክለኛ መስመር ላይ መሆኑን ማሳያ አሻራችንም ነው፤ በፈተና ውስጥ ሆነንም ወሳኝ የልማት አጀንዳዎቻችንን እንደማንዘነጋ ማረጋገጫ ነው፤ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ። የዘመኑ ትውልድ የአባቶቹን አይበገሬነት እና ከሁሉም በፊት ኢትዮጵያዊ ባይነት ታሪክ እየደገመ የሚገኝበት ዘመን ተሻጋሪ ሥራ ነው፤ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ።

ኢትዮጵያ በዓለም አደባባይ ፍትሕ ሲነፈጋት ሆድ ይፍጀው ብላ የማትቀበል፣ ፍርድ ሲዛባ ቀን ይፍታው ብላ የማትንበረከክ የጥቁር ሕዝብ የነፃነት ሰንደቅ ናት። በዓድዋ የታየው አንፀባራቂ የነፃነት ተጋድሎ ታሪክ፣ በካራማራ የተደገመው አኩሪ ተጋድሎ ዛሬም በዘመኑ ትውልድ እየተፈፀመ መሆኑን በግድባችን እያረጋገጥን ነው። ይህ በልማት የሀገርን ሉዓላዊነት የማስከበር ተጋድሎ ዳር እንዲደርስ ሚናውን በአግባቡ በመወጣት ላይ ያለው ትውልድም ሊመሰገን ይገባዋል።

ከታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጨት፤ የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጨት ብቻ የሚባል አይደለም። በዓባይ ወንዝ አቅም እንዳንጠቀም የተጎነጎነብንን ዘመን የተሻገረ ሴራ እየበጣጠስን መሆናችንንም ማረጋገጫ ነው። አትዮጵያዊያን የሌሎችን ፍትሓዊ ተጠቃሚነት ሳንጎዳ፣ በዙሪያችን ባለው ወጀብ ሳንናወጥ የምንቆም የመርህ ሰዎች መሆናችንንም ማረጋገጫ ነው። የዓባይ ዘመን ትውልድ ታሪክ መሥራት እንደሚችልም አንዱ ማሳያ ነው፡፡ ለዚህም ነው ኤሌክትሪክ ማመንጨት ብቻ አይደለም የምንለው።
ኢትዮጵያዊያን በርካታ ልዩነቶች አሉን። ነገር ግን ከነዚህ ልዩነቶቻችን በብዙ እጥፍ የሚልቁ አንድ የሚያደርጉን ጉዳዮች ባለቤትም ነን።

ኢትዮጵያዊያን የብዙ ጎሳ፣ ነገድ፣ ቋንቋ፣ ባህል፣ ዕምነት ባለቤቶች ነን። እነዚህ ግን ከልዩነት ምንጭነት ይልቅ ውበታችን እና ቀለማችን ሆነው ነው የኖሩት። አንዱን ጎሳ እና ነገድ ከሌላው መለየት እስኪያስቸግር ተዋልደናል፣ ተዛምደናል፣ ዕሴት ተጋርተናል። በዚህ አብሮነትም ብዙ የጋራ ታሪኮች ሠርተናል።

ይህንን መሰሉን በጥበብ የተሸመነ፣ ለመነጣጠል የሚከብድ ኅብረ ብሔራዊ አንድነት ለመበጣጠስ የተሠሩብንን ዕኩይ ተግባራት ጭምር በፅናት አልፈናል፤ ወደፊትም እንቀጥላለን። ኢትዮጵያዊነትን ከኢትዮጰያዊያን ልብ ውስጥ ለመፋቅ ብዙ ተደክሟል፤ በውጭ ታሪካዊ ጠላቶች እና በውስጥ ባንዳዎች ሕብረት። ትኩረታችን ከልዩነቶቻችን ይልቅ አንድነቶቻችን ላይ ሲሆን፣ ከግጭት ይልቅ ለውይይት እና ርስ በርስ ለመረዳዳት ቅድሚያ ስንሰጥ ታሪክ መሥራት በየትኛውም ዘመን ለእኛ ለኢትዮጵያዊያን ቀላል መሆኑን ግን አሁንም በግድባችን እያሳየን ነው።

አትዮጵያዊያን ከተመፅዋችነት ተላቀን ሉዓላዊነታችን የተከበረ እንዲሆን ግን በርካታ ግድቦች መሥራት አለብን። ኢንዱስትሪን ማስፋፋት ይጠበቅብናል። በመስኖ የማልማት አቅማችንን አሟጠን ልንጠቀም ግድ ይለናል። ሥራዎቻችን በበቂ መጠን መዘመን ይገባቸዋል። የሰብዓዊ እና ዴሞክራሲያዊ ሥራዎችም በቂ ትኩረት ማግኘት አለባቸው። ፖለቲካችን መስከን ይገባዋል። ወንዜነትን የተሻገረ፣ ኢትዮጵያን ያስቀደመ ፖለቲካን ማስፋት አለብን። ትውልዱን ከ”እኔ” ይልቅ የ”እኛ” በሚል አስተሳሰብ እንዲቃኝ ማድረግ እና ማበርታት ይገባናል። ከግል ጥቅም ይልቅ ሀገሩን እንዲያስቀድም ማድረግ አማራጭ የሌለው ምርጫ መሆን አለበት።

ዓባይን መግራት የጀመረው የዓባይ ዘመን ትውልድ ራሱን ለመግራት እንደማይቸገር እሙን ነው። ይህን ዘመን ተሻጋሪ ቅርስ የገነባው ትውልድ የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት በልማት የማረጋገጥ ሀገራዊ ሀላፊነት እጁ ላይ ነው።

ከእርዳታ አለመላቀቃችን ፍትሓዊ የሆኑ ጥያቄዎቻችንን እንኳን በዓለም አደባባይ ተቀባይነት ሲያጡ በበቂ መጠን ምላሽ እንዲያገኙ በቂ ጫና ማሳረፍ አላስቻለንም። ምጣኔ ሀብታዊ ነፃነታችንን ማረጋገጥ አለመቻላችን ሉዓላዊነታችንንም ይፈትናል።

እናም ይህ ትውልድ ጎጠኝነትን በሚያስፋፉ ፖለቲከኛ መሰል የሀገር ሸክሞች ሳይወናበድ፣ ርስ በርስ ለመጋጨት ሰበብ ሳይፈልግ፣ አንድ አድርገውት ከቆዩ ዕሴቶቹ ላይ በማተኮር ሀገሩን በልማት አብዮት ከፍ ማድረግ ይጠበቅበታልና ወገባችንን ጠበቅ አድርገን የጀመርነውን ዳር ልናደርስ ይገባል። በግድባችን የፈነጠቀው የልማት አርበኝነት በሌሎች ሥራዎቻችንም ሊረጋገጥ ይገባዋል።

በየተሰማራንበት መስክ ውጤታማ ተግባራትን ካከናወንን የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት በልማትም የምናረጋግጥበት ጊዜ ሩቅ አይሆንም።

(በቀለ አሰጌ)
በኲር ነሐሴ 16 ቀን 2014 ዓ.ም ዕትም
በአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን ዘወትር ሰኞ የምትታተመውን የበኲር ጋዜጣን ሙሉ ፒዲኤፍ
በhttp://www.amharaweb.com/Bekur ላይ ማግኘት ይችላሉ።
786 views11:51
ክፈት / አስተያየት ይስጡ