2023-03-31 14:37:21
በአበርገሌ በመድሃኒት እጦት የ47 ሰዎች ህይወት አለፈ
በህወሓት ኃይሎች ተይዞ እንደቆየ በተገለጸው የዋግ ኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን ውስጥ በሚገኘው አበርገሌ ወረዳ በመድኃኒት እና በምግብ እጥረት የ47 ሰዎች ሕይወት ማለፉን የወረዳው አስተዳዳሪ እና ቤተሰቦቻቸውን በሞት ያጡ ነዋሪዎች ለቢቢሲ ገለጹ።
አስተዳዳሪው አቶ አለሙ ክፍሌ ከሁለት ዓመታት በላይ በህወሓት ኃይሎች ቁጥጥር ሥር የቆየው ወረዳው፣ ረቡዕ መጋቢት 20/2015 ዓ.ም. መለቀቁን ገልጸው፣ የመከላከያ ሠራዊት እና የክልሉ የፀጥታ ኃይሎች ወደ ሥፍራው መግባታቸውን ተናግረዋል።
ይህንንም ተከትሎ አደረኩት ባሉት ማጣራት እና ቀድሞ በነበራቸው መረጃ መሠረት ከ47 በላይ ሰዎች በመድኃኒት፣ ሕክምናና በምግብ እጥረት ሕይወታቸው ማለፉን ገልጸዋል።
ኪሮስ ገላው የተባሉ የወረዳው ነዋሪም የወንድማቸውን ባለቤት በወሊድ ምክንያት በሞት ማጣታቸውን ለቢቢሲ ተናግረዋል።
ሙሉነሽ ጣፈጠ ሲሉ የሚጠሯት እናት፣ ሦስተኛ ልጇን ለመውለድ ለቀናት ካማጠች በኋላ በስቃይ ብትወልድም ከወሊድ በኋላ ባጋጠማት የደም መፍሰስ የሕክምና እርዳታ ሳታገኝ ሕይወቷ ማለፉን አቶ ኪሮስ ተናግረዋል።
“ለአምስት ቀናት አምጣ ወለደች። ከዚያ የደም መፍሰስ አጋጠማት የትራንስፖርት አገልግሎት ባለመኖሩ በቃሬዛ ተሸክመን በእግር ወደ ሰቆጣ ለመሄድ ጉዞ ጀመርን። [ከአበርገሌ ሰቆጣ በእግር አንድ ቀን ይወስዳል] ነገር ግን መንገድ ላይ ሞተችብን” ብለዋል።
1.0K viewstadi Sis, 11:37