2022-08-19 21:44:14
ኢብኑል ጀውዚ በ«ሲፈቱ ሰፍዋህ» እና ኢብኑ ነሕሓስ አድደመሽቂይ በ«መሻሪዑል አሽዋቅ» አቡ ቁዳማ አሽሻሚ ስለተባለ ሷሊህ ሰው የሚከተለውን አስፍረዋል።
ሰውየው ጂሃድንና በአላህ መንገድ ላይ ዘመቻን በጣም ይወድ ነበር። የጂሃድ ጥሪ ወይም በሙስሊሞችና በካሀዲያን መካከል ቂታል መኖሩን ከሰማ የሚቀድመው አልነበረም። አንድ ጊዜ መዲና መስጅድ ተቀምጦ ሳለ አንድ ሰው ጥያቄ አቀረበለት ፦
“አቡ ቁዳማ ሆይ! አንተ በአላህ መንገድ ላይ መጋደል የተወደደልህ ሰው ነህና እስኪ በጂሃድ ህይወትህ ያጋጠመህን ድንቅ ነገር ንገረን " አለው።
አቡ ቁዳማህ እንዲህ አለ፡- እሺ ልንገራችሁስኪ .....
ክስተቱ እንዲህ ነበር.... በአንድ ወቅት ከባልደረቦቼ ጋር መስቀላውያንን ለመዋጋት ወጣሁ። እናም በመንገዴ ላይ በረቃህ ከተማ (ኢራቅ ውስጥ በፉራት ወንዝ ላይ የምትገኝ ) አለፍኩ። ከርሷም መሣሪያዎቼን የምጭንበት ግመልን ገዛሁ። ሰዎችን በመስጂዶቻቸው ውስጥ ስለ ጂሃድ እና በአላህ መንገድ ላይ ስለመለገስ ዳዕዋ እያደረግኩ አጥብቄ አነሳሳኋቸው።
ሌሊቱ ሲመሽ የማድርበት ቤት ተከራየሁ ። ምሽቱ ገፋ ማድረግ ሲጀምር የቤቱ በር ተንኳኳ። በሩን ስከፍተው አንዲት በሒጃብ የተሸፋፈነች ሴት ቆማለች።
ምን ፈለግሽ ? አልኳት ።
፡- አንተ አቡ ቁዳማ ነህ?
፦ አዎ
፦ «ዛሬ ለጂሃድ ገንዘብ ስታሰባስብ የነበርከው አንተ አንተ ነህ?»
፦ «አዎ»
አንዲት ወረቀትና ትንሽ የታሰረች ከረጢት ሰጠችኝና እያለቀሰች ሄደች ..... ወደ ወረቀቱ ተመለከትኩኝ። እንዲህ ተፅፎበታል ፦ « ቅድም ወደ ጂሃድ ጥሪ አድርገህልን ነበር። ለማድረግ ምንም አቅም የለኝምና አለኝ የምለውን ቆርጬዋለሁ። እነሆ ሁለት የፀጉሬ ጉንጉኖች ናቸው። ይዤልህ የመጣሁት የፈረስህ ልጓም እንድታደርጋቸው ነው። ምናልባት አላህ ጸጉሬን በፈረስህ ላይ በርሱ መንገድ ላይ ታስሮ ሲያይ ወንጀሌን ይቅር ይለኝ ዘንድ።»
አቡ ቁዳማህ እንዲህ ይላል ፡- «በአላህ ይሁንብኝ! ጉጉቷና ትጋቷ ፣ እንዲህም ለአላህ እዝነትና ጀነቱ ያላት መንሰፍሰፍ አስገረመኝ። ሲነጋ እኔና ባልደረቦቼ ረቃ ከተማን ለቅቀን ወጣን። በመስለማህ ቢን አብዱል መሊክ ምሽግ አጠገብ ስንደርስ አንድ ፈረሰኛ ከኋላችን እየጮኸ ይጣራል።
ያ አባ ቁዳማህ ! ያ አባ ቁዳማ ! አላህ ይዘንልህና ቁም!
አቡ ቁዳማህ እንዲህ ይላል ፡- ለባልደረቦቼ እናንተ ተቀደሙኝ እኔ የዚህን ፈረሰኛ ዜና ልስማውስኪ አልኳቸው። ወደ ፈረሰኛውም ተመለስኩ።
ፈረሰኛው እንዲህ ሲል ጀመረ፦ « ያንተን ጓደኝነት ያልከለከለኝና አመድ አፋሽ አድርጎ ያልመለሰኝ አላህ ምስጋና ይገባው!» አለ።
እኔም ፦ «ምን ፈልገህ ነው?» አልኩት።
እርሱም፡- ከእናንተ ጋር ለመዋጋት መሄድ እፈልጋለሁ አለ።
እኔም ፦ «ፊትህን ተገለጥና ልመልከትህ !ትልቅ ሰው ሆነህ መዋጋት ግዴታ የሚሆንብህ ከሆንክ እቀበልሀለሁ። መዋጋት ግዴታ የማይሆንብህ ትንሽ ልጅ ከሆንክ ደግሞ እመልስሀለሁ» አልኩት።
.... ፊቱን ገለጠ፣ ፊቱም ጨረቃ ይመስላል ። ገና የአሥራ ሰባት ዓመት ታዳጊም ነበር።
እኔም፡- ልጄ ሆይ አባት አለህ? አልኩት።
እሱም፡- አባቴን የገደሉት መስቀላውያን ናቸው። እኔም ያባቴን ገዳዮች እዋጋለሁ። »
፡- እናት አለህ?
፡- አዎ።
፦ በል ወደ እናትህ ተመለስና እርሷን አገልግል ጀነት ከእግሯ በታች ናትና አልኩት።
፦ እናቴን አታውቃትምንዴ ? አለኝ።
፦ አላውቃትም ።
፡- እናቴኮ የአደራው ባለቤት ናት፡።
፦ የምን አደራ?
፦ የከረጢቱ ባለቤት ።
፦ የምን ከረጢት ?
፡- «ሱብሓነላህ! ምን ጊዜ ረሳሃው? ትናንት ምሽት መጥታ ከረጢትና ወረቀት የሰጠችህን ሴት አታስታውስም?»
እኔም፡- አ..ዎ! አስታወስኩ! አልኩት።
ቀጠለ... «እርሷ እናቴ ናት፣ ወደ ጂሃድ እንድወጣ አዛኛለች ፣ እንዳልመለስም ምላብኛለች። ስትሸኘኝ እንዲህ አለችኝ፦ «ልጄ ሆይ! ካሀዲያንን ስታገኛቸው እንዳትሸሻቸው ! ራስህን ለአላህ ስጥ! የአላህንም ጉርብትና ፈልግ። ከአባትህና ከአጎቶችህ ጋር በጀነት መኖርን ፈልግ ! አላህ ሰማዕትነትን (ሸሂድነትን) ከሰጠህ እንድታማልደኝ አደራ ።”
....ከዚያም ወደ ደረቷ እቅፍ አደረገችኝና አይኗን ወደ ሰማይ ከፍ አድርጋ እንዲህ አለች ፡- « ኢላሂ! ፣ ጌታዬና ተንከባካቢዬ ሆይ! ፣ ይህ ልጄ ነው። የልቤ ደስታ እና የልቤ ፍሬ ነው። ላንተ አስረክቤያለሁ ወደ አባቱና አጎቶቹ አቅርበው። »
ከዚያም ቀጠለና እንዲህ አለ፡- ( አቡ ቁዳማህ ሆይ!) በአላህ መንገድ ላይ ከአንተ ጋር ዘመቻ መሳተፍን እንዳትከለክለኝ በአላህ ስም እጠይቃሀለሁ! ። እኔ ኢንሻአላህ ሸሂድ የሸሂድ ልጅ መሆን ነው የምፈልገው። የአላህን መጽሐፍ ሸምድጃለሁ፣ ፈረሰኝነትንና መተኮስንም አውቃለሁ፣ ትንሽነቴን አይተህ እንዳትንቀኝ! »
አቡ ቁዳማህ እንዲህ ይላል፡- «ይህን ንግግሩን ስሰማ ከኛ ጋር እንዲሄድ አደረግኩት። በአላህ ይሁንብኝ ከርሱ የበለጠ ንቁ ሰው አላየንም፤ ስንጋልብ ቀዳሚ ነው፣ ስናርፍ እርሱ ንቁ ነው።በሁሉም ሁኔታዎቹም ውስጥ ምላሱ አላህን ከማውሳት በፍፁም አያርፍም።
የሆነ ቦታ ላይ አረፍን ..... ፆመኞች ነበርንና ማፍጠሪያችንን ልናዘጋጅ ፈለግን። ልጁም ከሱ በቀር ማንም ቁርስ እንደማይሰራ ማለ። ....እምቢ አልነው.. እርሱም እምቢ አለን።
ማፍጠሪያችንን ሊያበስል ሄደ... በጣም ዘገዬ ። ከጓደኞቼ አንዱ « አቡ ቁዳማ ሆይ ! እስኪ ሂድና ልጁ ምን እንደሆነ ተመልከት አለኝ።
ሄድኩኝ .... ልጁ እሳቱን አቀጣጥሎና ቶፋውን (ድስቱን) ጥዶ ድካምና እንቅልፍ አሸንፈውት ራሱን ድንጋይ ላይ ጭኖ ተኝቷል።
ከእንቅልፉ መቀስቀስ ጠላሁ.. ባዶ እጄን ወደ ጓደኞቼ መመለስም ከበደኝ .. ልጁን በእይታዬ ውስጥ አድርጌ ኢፍጣሩን ማዘጋጀት ጀመርኩ ....
በዚህ ጊዜ ነበር አቡ ቁዳማህ አስገራሚ ነገር የተመለከተው።
..... ይቀጥላል
272 views18:44