Get Mystery Box with random crypto!

Adoni Gospel channel

የቴሌግራም ቻናል አርማ adonigospel — Adoni Gospel channel A
የቴሌግራም ቻናል አርማ adonigospel — Adoni Gospel channel
የሰርጥ አድራሻ: @adonigospel
ምድቦች: ሃይማኖት
ቋንቋ: አማርኛ
ተመዝጋቢዎች: 6.70K
የሰርጥ መግለጫ

የእግዚአብሄርን ፍቅር፣ ምህረትና ይቅርታ በተገለጠው የወንጌሉ ቃል መሰረት የምንማማርበት ቻናል ነው። ትምህርቶቹን በሚያመቻችሁ የሶሻል ሚድያ በኩል ለመጠቀም ከስር ያሉትን ሊንኮች ይጠቀሙ።
Telegram ፦ @adonigospel
WhatsApp ፦ https://chat.whatsapp.com/BnTcBA0mML6E7gakQUIJ8X

Ratings & Reviews

3.00

3 reviews

Reviews can be left only by registered users. All reviews are moderated by admins.

5 stars

0

4 stars

0

3 stars

3

2 stars

0

1 stars

0


የቅርብ ጊዜ መልዕክቶች 4

2022-07-02 10:30:39                     በጉን አለበሰን

   "እግዚአብሔር አምላክም ለአዳምና ለሚስቱ የቁርበትን ልብስ አደረገላቸው፥ አለበሳቸውም።"
ኦሪት ዘፍጥረት 3 : 21


           አዳምና ሔዋን በሀጢአት ምክንያት ከእግዚአብሔር ባፈነገጡ ጊዜ ሀጢአት ሰላማቸውን ነጥቆ ፈሪ፤ እግዚአብሔርን የሚሹ ሳይሆን የሚሸሸጉ አደረጋቸው። ራቁታቸውን ሆኑ እርስ በእርስም ሀጢአተኛው ሀጢአተኛዋን ያፍር ጀመር። ሀጢአት እርስ በእርስ እንኳ ክብርን ድፍረትን አይሰጥም።

         እግዚአብሔር ግን ሀጢአተኛ የሆኑትን አዳምና ሄዋንን እርስ በእርስ ሲተፋፈሩ ቅጠል ሲያገለድሙ እያየ አልሳቀባቸውም። ይልቅ አንድ በግ አርዶ የበጉን ቁርበት አለበሳቸው። ለአዳምና ሔዋን እፍረት መሸፈኛ የሆነው በጉ ታርዶ፤ ቆዳው ተገፎ፤ ደሙ ፈሶ ነው። እግዚአብሔር በበጉ ጨክኖ አዳምና ሔዋንን ከእፍረት ታደጋቸው።

           እግዚአብሔር በሀጢአት ወረዳ በሞት ቀጠና ስንቅበዘበዝ እያየ አልተዝናናብንም አልሳቀብንም ይልቅስ አዘነልን። ሁላችንም በገዛ ፍቃዳችን በሀጢአት ተዋርደን፤ በአደባባይ ተራቁተን፤ እርቃናችንን ተጋልጠን ነበር። እግዚአብሔር እንደለመደው በበጉ በክርስቶስ ላይ ጨከነ። ክርስቶስን ለኛ ሰዋልን። "ጌታን ኢየሱስ ክርስቶስን ልበሱት" (ወደ ሮሜ ሰዎች 13 : 14)

በመስቀል ላይ እርቃኑን ሲሆን የተራቆተውን ህሊናችንን፣ መንፈሳችንን፣ ስጋችንንም ብርሃኑን አለበሰን። ደሙን አፍስሶ የሚፈሰውን ደማችንን ገደበው፤ መቃብር ገብቶ መቃብራችንን ደፈነው፤ ሞቶ ሞታችንን ገደለው፤ ቆስሎ ቁስሌችንን ሻረው።

          ዝቅታውን ሁሉ ወስዶ ከፍታውን ሰጠን፤ በረቱን መርጦ ሲወለድ እኛን በአብ ቀኝ አስቀመጠን፤ መስቀሉን ሲሸለም እኛን የመንግስቱ ወራሽ አደረገን፤ ሲሞት በህይወት ኑሩ አለን።

          ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስማችንን ከክስ መዝገብ ላይ ሰረዘው በሞቱም ዘጋው፤ በህይወት መዝገብ ላይ ስማችንን ፃፈው። ላይረሳንም በመዳፉ ቀረፀን። ስለዚህ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን ልበሱት ምክንያቱም ታርዷልና። አሜን ክብር ላንተ ይሁን።

                        አዶኒ

ጥር 10/2013 በድጋሚ የተለጠፈ

@adonigospel
@adonigospel
1.4K views@doni, 07:30
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-01 04:39:13          ትንሽ ሲጎል ግብፅን መናፈቅ


“የእስራኤልም ልጆች፦ ይህን ጉባኤ ሁሉ በራብ ልትገድሉ እኛን ወደዚች ምድረ በዳ አውጥታችኋል፤ በሥጋው ምንቸት አጠገብ ተቀምጠን እንጀራ ስንበላ ስንጠግብ ሳለን በግብፅ ምድር በእግዚአብሔር እጅ ምነው በሞትን! አሉአቸው።”
  — ዘጸአት 16፥3

      
    እስራኤላውያን ፈጣን የመርሳት ችግር ነበረባቸው። ትላንት እግዚአብሔር በዋና የማይሻገሩትን የኤርትራን ባህር በሚያስደንቅ ተዓምራቱ ከፍሎ እንዳሻገራቸው ረሱና ዛሬ አንድ ብርጭቆ ውኃ ጠማን፤ የግብፅ ምንቸት ናፈቀን ብለው ማጉረምረም ጀመሩ። ከመዳናቸው ይልቅ በግብፅ በሞትን ይሻለን ነበር ብለው ከምስጋና ይልቅ አንደበታቸውን በብስጭት ቃላት ሞሉት።

       እግዚአብሔር ግን እስራኤላውያንን የራሳችሁ ጉዳይ አላላቸውም፤ አውጥቶም በሜዳ አልበተናቸውም። እንደስራቸው አልሰጣቸውም ይልቁንም እግዚአብሔር ለህዝቡ መሀሪ መሆንን መረጠ። አመፀኞችና ምስጋና ቢስ ቢሆኑም ወደዳቸው። የእግዚአብሔር ፍቅር በኛ ማንነት ላይ የተመሰረተ ሳይሆን በራሱ ማንነትና ምህረት ላይ የተመሰረተ ነው። ባይገባቸውም መባረክን መረጠ።

      “እግዚአብሔርም ሙሴን አለው፦ የእስራኤልን ልጆች ማንጐራጐር ሰማሁ፦ ወደ ማታ ሥጋን ትበላላችሁ፥ ማለዳም እንጀራን ትጠግባላችሁ፤ እኔም እግዚአብሔር አምላካችሁ እንደ ሆንሁ ታውቃላችሁ በላቸው።” — ዘጸአት 16፥11-12

     ቅሬታቸውን በምግብና ውኃ እንዲሁም በጥበቃውና በአቅርቦቱ መለሰላቸው።

     ወዳጆቼ ትላንትና በእውቀታችንም በጉልበታችንም፤ በገንዘባችንም በጥበባችንም የማናልፈውን ትልቅ መከራ እግዚአብሔር በተዓምራቱ አሻግሮን ዘምረናል። ዝማሬያችን አርጎ ሳይጨርስ ዛሬ በገጠመችን ትንሽዬ ተግዳሮት ተስፋ እንቆርጣለን፤ ትላንት የረዳን ጌታ ዛሬ እንደማይረዳን ቆጥረን እናጉረመርማለን።

      እግዚአብሔር ግን የትላንት መልካምነቴን በጭቃ ለወሳችሁት፤ ቅን ባሰብኩላችሁ እንደ ክፉ ቆጠራችሁኝ፤ ፍቅሬን በአመፃ ለወጣችሁት ሳይል ዛሬም ምህረቱን አብዝቶልን፣ የእንደገና አምላክ ሆኖልን ዛሬም በረድኤቱ ከኛ ጋር ነው። 

     በትልቁ ችግራችን የደረሰውን ጌታ በትንንሽ ነገሮች ይተወናል ብለን አንጠርጥረው። ሲዖል ድረስ በፍለጋ ገብቶ፣ መቃብር ድረስ በፍለጋ ሰምጦ፣ መስቀል ድረስ ወጥቶ ያዳነን ጌታ ዛሬ በገጠመችን ጥቂት ነገር ተነስተን አናጉረምርም። ከዚህ በኋላ ከሚያደርግልን በላይ እስካሁን ያደረገልን ነገር ከሁሉ ይበልጣል።

      በሕይወት እስካለን ድረስ የሚኖርብን የትኛውንም ጉድለት ግብፅ ልትሞላልን አትችልም፣ ዓለም ልትቸረን አትችልም፤ የኛን ክፍተት ሳይሰቅቀው የሚሸፍን አቅም ያለው እግዚአብሔር አምላክ ብቻ ነው።

አዶኒ

ሰኔ 23/2014

@adonigospel
@adonigospel
1.5K views@doni, 01:39
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-06-29 08:10:35 ሒድ አንተ ሰይጣን


“እርሱ ግን ዘወር ብሎ ጴጥሮስን፦ ወደ ኋላዬ ሂድ፥ አንተ ሰይጣን፤ የሰውን እንጂ የእግዚአብሔርን አታስብምና ዕንቅፋት ሆነህብኛል አለው።”
  — ማቴዎስ 16፥23


   ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በካህናት አለቆችና በፈሪሳውያን ተይዞ ብዙ መከራ እንደሚቀበል፣ እንደሚገደል ደግሞም እንደሚነሳ ለደቀመዛሙርቱ ነገራቸው። ጴጥሮስ ይህን ሰምቶ ይህ እንዲሆን ፈጽሞ እንደማይፈቅድና አይሁንብህ ብሎ ማከላከል ጀመረ። ጌታችንም ሂድ አንተ ሰይጣን ብሎ ገሰፀው።

     አንድ ብርጭቆ ውስጡ ወይ ውሀ ይኖረዋል አልያም አየር ይኖረዋል እንጂ ባዶ መሆን አይችልም። ልክ እንደዚሁ ሁሉ በሕይወት ስንኖር ባዶ መሆን አንችልም። ማንም ገዢ የለኝም ብለን መኖር አንችልም። ወይ እግዚአብሔር ይገዛናል እግዚአብሔር አይገዛኝም ካልን ሰይጣን ይገዛችኋል። ከሁለቱ በቀር ሌላ ምርጫ አይኖራችሁም።  ጴጥሮስ ጌታን ከመጣበት የማዳን ዓላማ ሊያስተጓጉል ሲፈልግ የእግዚአብሔርን ፍቃድ እየተከተለ አልነበረም። ሰው የእግዚአብሔርን ፈቃድ ካልተከተለ የሰይጣንን ፈቃድ መከተሉ አይቀርም። ጴጥሮስን ሂድ አንተ ሰይጣን ያስባለው የሰይጣንን ሃሳብ በማራመዱ ነው።

     ጴጥሮስ በችኮላ የሚሰማና በችኮላ የሚናገር እንጂ አስተውሎ የሚሰማና አስቦ የሚናገር አይደለም። ጴጥሮስ ጌታችን እሞታለሁ እሰቀላለሁ የሚለውን ብቻ እንጂ እነሳለሁ የሚለውን የጌታን ንግግር ልብ አላለም ነበር። ጴጥሮስን አይሁንብህ የሚል ክልከላ ውስጥ የከተተው ሞቶ የሚቀር መስሎት እንጂ እነሳለሁ የሚለውን ቃል ቢሰማ ኖሮ ሰይጣናዊ ሃሳብን አያራምድም ነበር።

     ወዳጆቼ በሕይወታችን ውስጥ እግዚአብሔር የሚናገረውን በሙሉ መስማት አለብን። መስማት የምንፈልገውን ብቻ መርጠን፣ የንግግሩን ጅማሬ ብቻ ወስደን መስማት የለብንም። ምክንያቱም በጣም ጥሩ የሆነውና ወሳኙን ክፍል ልናጣ እንችላለን።

     ጴጥሮስ የተመለከተው የአጭር ጊዜ ችግሮችን ብቻ እንጂ የሚፈጠረውን ረጅም ዘላለማዊ ውጤት አይደለም። በአንድ ጆሯችን ብቻ ስንሰማ በጊዜያዊ ነገር ብቻ ተይዘን እንቀራለን በሁለቱም ጆሯችን በእርጋታ ስናዳምጥ ዘላለማዊ ዓላማውንም ማወቅ እንችላለን።

       ብዙ ሰው የእግዚአብሔርን ቃል ቦጭቆ ይወስድና እርሱን ብቻ ያብላላል የእግዚአብሔር ቃል ግን የተቦጨቀው ብቻ ሳይሆን ከዳር እስከ ዳር ያለው መሆኑን ይዘነጋል። እግዚአብሔርን ጨርሰን ልንሰማው ይገባል። ፀሀፊዎች " ሁለት ጆሮ የተሰጠን ብዙ እንድንሰማ አንድ አፍ የተሰጠን ጥቂት እንድናወራ ነው። ብዙ እንድናወራ ቢፈለግ ኖሮ ሁለት አፍ ጥቂት እንድንሰማ አንድ ጆሮ ይሰጠን ነበር" ብለዋል። እውነት ነው ሕይወታችንን የሚዘውራት የምናወጣው ሳይሆን ወደ ውስጥ የምናስገባው ላይ ነው። ስለዚህ አጣርተንና ጨርሰን ሰሚዎች እንሁን።

አዶኒ

ሰኔ 22/2014

@adonigospel
@adonigospel
1.8K views@doni, 05:10
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-06-28 10:59:03 ያላንተ ክብር የለኝም

@adonigospel
1.5K views@doni, edited  07:59
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-06-28 09:51:31 የማታልፍ ጽዋ


“ጥቂትም ወደ ፊት እልፍ ብሎ በፊቱ ወደቀና ሲጸልይ፦ አባቴ፥ ቢቻልስ፥ ይህች ጽዋ ከእኔ ትለፍ፤ ነገር ግን አንተ እንደምትወድ ይሁን እንጂ እኔ እንደምወድ አይሁን አለ።” — ማቴዎስ 26፥39


    ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በጌቴሴማኒ የአትክልት ስፍራ ነበር። በሁሉን አዋቂ ማንነቱ መከዳት ሊደርስበት፤ ሁሉም በአንድ ልብ ተስማምተው ሊሰቀል እንደሆነ፤ የዓለም ሁሉ ኃጢአት በእርሱ ላይ ሊሆን እንደሆነ ያውቃል።

     ወዳጆቼ እስቲ ለአንድ ደቂቃ ራሳችንን ጌታ ኢየሱስ በነበረበት ቦታ ላይ አስቀምጠን እናስብ። እኛ ነገ ሊሆንብን ያለውን ነገር ብናውቅ እንሸሽ ነበር፤ ራሳችንን እንሰውር ነበር። ጌታ ግን የሚደርስበትን ሁሉ እያወቀ ተዘጋጀ።

      ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ፍፁም ኃይል አለው። ፕላኔቶችን ከዋክብትንና ሁሉንም ፍጥረት በቃሉ የፈጠረ ጌታ ነው። ይህ ጌታ በሰውም ሆነ በእግዚአብሔር አብ ላይ ምንም ስህተት አላደረገም ግን ሊሰቀል ነው። ከመሰቀልም አልፎ ለዘላለም አብሮት የነበረው አባቱ ፊቱን ሊመልስበት ነው። ልመናው የማይሰማበት ጸሎቱ የማይመለስበት ጊዜ ሊመጣ ነው።

      ጌታችን ሞትን መቅመስ ሳይሆን ፍርሀት የገባው ለባህሪው የማይስማማውን ኃጢአት ሊሸከም መሆኑን ሲያስብ ይህች ጽዋ ከኔ ትለፍ ብሎ ጸለየ። ጌታችን እንዲህ ብሎ በመጸለዩ ላይ ምንም ስህተት የለም። ነገር ግን እግዚአብሔር አብ ሃሳቡን አይለውጥም፤ መልሱንም አይቀይርም። የእግዚአብሔር ፍቃድ ጌታችን ኢየሱስ እንዲሰቀል ነው።

      ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያለመሰቀል፣ መከራ ያለመቀበል ሙሉ ኃይልና ስልጣን ቢኖረውም ያንን ስልጣኑን ወደጎን በማስቀመጥ የአብን ፍቃድ ለመፈፀም ወስኗል።

       እግዚአብሔር ፈቃዱ ዛሬም በእኛ ሕይወት እንዲፈፀም ይፈልጋል። ግን ፍቃዱን ለማድረግ ፍቃደኛ ነን? ብዙ ጊዜ እግዚአብሔር አንድን ነገር እንድናደርግ በግልፅ ሲናገረን እንሰማለን ነገር ግን ይህንን ላለማድረግ እንወስናለን። እግዚአብሔርን እንጠይቃለን ግን መልሰን የራሳችንን መንገድ እንወስናለን።

     እግዚአብሔር እንድንሞት እየጠየቀን ላይሆን ይችላል ነገር ግን ራሳችንን ወደ ጎን እንድንተውና አንድ ነገር እንድናደርግ እየጠየቀን ነው። ያ ነገር ምንም ቢሆን ለእኛ ጥቅም፣ ለሎሎች ጥቅም፣ ለእግዚአብሔር ክብር ነው።

      ጌታችን ጽዋዋ እንድታልፍ ቢፈልግም የራሱ ፍላጎት ሳይሆን የአባቱ ፍቃድ እንዲፈፀም ፈለገ። እኛም በሕይወታችን በየዕለት ተዕለት ጉዟችን የኛ ፍላጎት ሳይሆን የእግዚአብሔር ፍቃድ እንዲፈጸም መፈለግ አለብን። የአጭር ጊዜ ምኞቶቻችንን ወደ ጎን አስቀምጠን እግዚአብሔርን ሙሉ በሙሉ መከተል አለብን። ይህ ሲሆን መጨረሻችን ዋጋ ያለው ይሆናል።

      ብዙ ሰው በራሱ ምኞትና ሀሳብ ለብዙ ኪሳራና እንግልት ተዳርጓል የእግዚአብሔር ፍቃድ ግን ከአጉል ውሳኔና ሕይወት ይጠብቀናል። መልስ ከሌለው ጥያቄ ይጋርደናል። ፍቃዱ ከፊታችን ያለውን ጭጋግ ወጋገን ሆኖ ይመራናል።

       ጸሎት

     አቤቱ እግዚአብሔር ሆይ እስከ ዛሬ እንደልባችን ተጉዘናል እንደልባችን ሆነናል ዛሬ ግን አንደ ልብህ መሆን ይሁንልን። ለፍላጎታችን ተሸንፈን ለምኞቶቻችን ተታለን አንተን አሳዝነናል ዛሬ ግን ለፍቃድህ መሸነፍ እንዲሆንልን ባየህልን ጎዳና መጓዝ እንዲሆንልን መንፈስህ ያግዘን። ለሕይወታችን ፍላጎት ስንል ከአንተ ፍቃድና ዓላማ እንዳንመለስ በጸጋህ እርዳን። አሜን

አዶኒ

ሰኔ 21/2014

ቤተሰብ ይሁኑ

@adonigospel
@adonigospel
1.5K views@doni, 06:51
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-06-27 13:44:40 ውድ አምላክ እግዚአብሔር ሆይ ለሊቱን አሳልፈህ ብርሃን እንድናይ ስለፈቀድክልን ተመስገን።

  አቤቱ እግዚአብሔር ሆይ በምንሄድበት ቦታ ሁሉ ቀድመህ አስከትለን። የምናየውም የማናየውም ነገር ሁሉ በዓይንህ ስር ይሁን። ልባችንን ሃሳባችንን እግራችንንም እንደፈቀድህ ምራልን።

    ሕይወታችን በምህረት እጆችህ ላይ ትቀመጥልን ነገራችንን ሁሉ በእጃችን ላይ አስቀምጥልን። የሚሰማን ስሜት ሁሉ በመንፈስህ የተቃኘ ይሁን። መልካሙን ለማድረግ መንፈስህ በውስጣችን ይንቀሳቀስ። የምንፈልገውን ሁሉ በፍቅርህ ውስጥ እንድናገኘው ፍቀድልን።

    አቤቱ እግዚአብሔር ሆይ የሕይወታችን አቅጣጫ ወዴት እየሄደ እንደሆነ አንጠይቅህም አንተ ከኛ ጋር በልባችንም በነፍሳችንም ጥልቅ ውስጥ ስላለህ ከጥያቄያችን አርፈናልና ተመስገን። እየመራኸን ነው እኛም ደህና ነንና በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተመስገን! አሜን።

አዶኒ

ሰኔ 20/2014

@adonigospel
@adonigospel
1.5K views@doni, 10:44
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-06-25 09:09:52 አቤቱ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፦

አክብረህና አፍቅረኸው የሞትክለት የሰው ልጅ ክብርን አጥቶ እንደ እንስሳ በየመዳው ይታረዳል እባክህ የሚፈሰውን ደም በደምህ ገድብልን።

የሚያነቡ የእናቶችን እንባ አብስልን። በሀዘን የተሰበሩትን ልቦች ሁሉ በፍቅርህ ዘይት ጠግንልን። አቤቱ ጌታችን ሆይ ያፈረስከውን ዘርና ጎሳ ብሄርና ቀለም መልሰን እየገነባን ልብህን አሳዘንነው እባክህ ይቅር በለን ፊትህን መልስልን።

አይሁድ አንተን ለመግደል በጨከኑበት ጭካኔ ዛሬም የእጅህ ስራዎች በዛው ልክ ተጨካክነዋል እባክህ ከጨካኞች ጀርባ ግፍን የሚያሰራውን ደም የሚጠጣውን የጥልቁ መንፈስ በትንሳኤው ኃይልህ በኢየሱስ ስምህ ገስፀው።

አቤቱ ልብ ላጣነው ሁሉ የስጋን ልብ አድለን። የዘመናትን የኃጢአት ጅረት እንደገደብከው ዛሬም ከሀገሬ ላይ ሞትን ገድብልን፣ ጭካኔን ገድብልን፣ ዘረኝነትን ገድብልን፣ ሰቆቃን ገድብልን፣ መለያየትን ገድብልን።

አቤቱ አሁን አድን፤ አቤቱ ለሀገሬ ፍቅርህን አዝንብ፤ አቤቱ ለሀገሬ ሰላሙን አዝንብ፤ አቤቱ ለሀገሬ ምህረትን አብዛልን፤ አቤቱ በሀገሬ ያለውን ህዝብ ሁሉ በፍቅር ግመደው። ጌታዬ ሆይ በሰው ሀገር በግፍ፣ በሰቆቃ፣ በብቸኝነት፣ በሰው ርሀብ፣ በበሽታ ተጠቅተው ያሉትን ሁሉ ያንተ የነፃነት መንፈስ ያግኛቸው። በሰላም ሂድ የሚለው የስልጣን ቃልህ ይታወጅላቸው። አቤቱ በስደት በእስር ላይ ያሉትን ሁሉ በስደት በመሪር አገዛዝ ውስጥ ያሉትን ሁሉ የእጅህ ተአምር ትድረስላቸው።

አቤቱ ጸልዩ እኔም እመልስላችኋለው በሚለው ቃልኪዳንህ ስምህን ይዘን ጸለይን። ስለሰማኸን ክብር ላንተ ይሁን።

አዶኒ

@adonigospel
@adonigospel
1.8K views@doni, 06:09
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-06-25 08:53:19 @adonigospel
1.4K views@doni, edited  05:53
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-06-24 07:41:57 አንተን መኖር ይሁንልን


“እግዚአብሔርን እንዲያውቁ በግልጥ ይናገራሉ፥ ዳሩ ግን የሚያስጸይፉና የማይታዘዙ ለበጎ ሥራም ሁሉ የማይበቁ ስለ ሆኑ፥ በሥራቸው ይክዱታል።”
  — ቲቶ 1፥16


        እግዚአብሔር ሥነ ፅሁፍን የጀመረ ደራሲ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ሐሳብ በሰው ቋንቋ የተፃፈበት መጽሐፍ ነው። ይህ መጽሐፍ ቅዱስ የተፃፈበት ምክንያት ዮሐንስ እንደሚነግረን ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ እናምን ዘንድና አምነን በስሙ ሕይወት እንዲሆንልን ነው።
(ዮሐ 20፥31)

       እግዚአብሔር 66 የመጽሐፍ ክፍሎችን ደርሶ አፅፎ አሰራጨልን። አንዱን መጽሐፍ ብቻ አላሳተመልንም። ነገር ግን በየቦታው እንዲነበብ አድርጎ በአለም ሁሉ አስራጭቶታል። ይህም ስልሳ ሰባተኛ መጽሐፍ ክርስቲያኖች ነን። ክርስቲያን ሕይወቱ የሚነበብ መፅሐፍ መሆን ሲገባው ጽሑፉ እንደማይነበብ ስርዝ ድልዝ እንደበዛበት ጽሑፍ ሕይወቱም ግራ የሚያጋባ ሆነ።

ሐዋርያው ጳውሎስ እግዚአብሔርን እናውቃለን ስለሚሉ ነገር ግን በእውነቱ በሕይወታቸው እርሱን ስለካዱ ሰዎች ይናገራል። በዚያን ጊዜ እግዚአብሔርን እናውቃለን ብለው የሚያወሩ በሕይወታቸው ግን የካዱት ነበሩ። እንዲህ አይነት ክርስቲያኖች ዛሬም በዝተናል።

      በእውቀት ደረጃ ክርስትናውን እንተነትነዋለን። ህይወታችን ሲገባ ግን ባዶ ደነናዎች ነን። እንዲህ አይነት አማኞችን ዲያብሎስ ሲያይ የሚለን አንድ ነገር  " ሁሉ ነገራቸው የእኔ ነው አፋቸው ብቻ የእኔ አይደለም" ይለናል። አዎ አንደበታችን ብቻ ስለክርስቶስ በመመስከር ድኗል ሕይወታችን ግን ይክደዋል።

     ቤተክርስቲያን እየታመሰች ያለችው በእንደኛ አይነት ሰዎች ነው። የደረቀ ሕይወት ባለን ሰዎች ነው። እሁድ እግዚአብሔርን ስለ ማመስገን እናወራለን ነገር ግን ከሰኞ እስከ ቅዳሜ የስራ ባልደረባችንን፣ አለቃችንን እንሳደባለን። ስራችን በማጭበርበር የተሞላ ነው፤ ቢዝነሳችን ሰውን የሚጎዳና እግዚአብሔር የማይከብርበት ነው። ለምናገኘው ማንኛውም ሰው ፍቅር አናሳይም በታጠፈ ግንባር ጥላቻን እናሳያለን። 

    ወዳጆቼ የእግዚአብሔር ቃል መነፅር ሳይሆን መስተዋት ነው። መነፅር ሌላውን ያሳያል መስታወት ግን ራስን ያሳያል። ስለዚህ ማንንም ሳይሆን ራሳችንን ማየት አለብን። ወደ ቤተ ክርስቲያን ልንሄድ እንችላለን ግን ሕይወታችን ከቤተክርስቲያን ውጭ ምን ይመስላል? ቤት ውስጥ ምን ይመስላል? በስራ ቦታስ ምን ይመስላል? ምን እያደረግን ነው? ለእግዚአብሔር ያለንን ፍቅር በተግባር ለማንጸባረቅ፣ እጅና እግር ያጣውን ክርስትናችንን ለመኖር ዛሬ እንወስን።

    አቤቱ እግዚአብሔር ሆይ አልጨበጥ ያለውን ላንተም ለኛም ግራ የሚያጋባውን፣ በክርስትና ሕይወት አልፀና ያለውን፣ መጣ ሲባል ሒያጅ ሔደ ሲባል የሚመጣውን ያልረጋ ሕይወታችንን አስተካክልልን። አቤቱ እግዚአብሔር ሆይ አንደበታችን ሌላ ሕይወታችን ሌላ ሆኖብናልና ቃልህን በሕይወታችን የምንፈፅምበትን ፀጋህን አብዛልን። እባክህን የማስመሰል ሕይወትን በቃ ብለህ በእውነትህ አሳርፈን። ፈለግህን መከተል እንዲሆንልን አንተን በሕይወታችን ገልጠን ደግሞም አስከብረን ዘመናችን እንዲያልቅ ኃይልህን ስጠን። በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አሜን።

አዶኒ

ሰኔ 17/2014 ተፃፈ

ቤተሰብ ይሁኑ

@adonigospel
@adonigospel
1.8K views@doni, 04:41
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-06-23 15:36:35      የክርስቶስ ደም ክፉውን ጊዜ ያሻግረን


"ደሙም ባላችኹበት ቤቶች ምልክት ይኾንላችዃል.
ደሙንም ባየኹ ጊዜ ከእናንተ ዐልፋለኹ እኔም የግብጽን አገር በመታኹ ጊዜ መቅሠፍቱ ለጥፋት አይመጣባችኹም።" ዘፀ 12፥13


    ሙሉ የግብፅን ህዝብ ያስጨነቀው የበኵር ሞት እያንዳንዱን የግብፅን ቤት ከድሀው እስከ ባለፀጋው ከተራው ዜጋ እስከ አስጨናቂው ገዥ ፈርዖን ቤት ዘልቆ ገባ። አንዱ አንዱን ለቅሶ እንዳይደርስ ሁሉም ቤት ሬሳ ታቀፉ። አዎ በዚህ ቀን ቀብሬ ላይ ሳላይህ የሚል ትዝብት፣ ሳታላቅሰኝ የሚል ቅሬታም የለም። ሃያላኑ በሞት ሲያለቅሱ ደካሞቹ በሰላም ይወጣሉ። ግብፅ ያለቅሳል እስራኤል በድል ያመልጣል። የግብፅን በኵር ሁሉ የገደለው እስራኤል አይደለም፤ ክንዳቸው አይደለም የሚያመልኩት ጌታ ነው። አዎ በአንድ ሀገር ውስጥ አንዱ በመዓት ሲቀጣ አንዱ በፀጥታ ሲጓዝ እናያለን። የሞት መልዓኩ ግብፅን እንዲቀጣ የቤት ቁጥራቸውን ዝርዝር ስለያዘ አይደለም እስራኤል የበጉን ደም በበራቸው ላይ በመርጨታቸው ነው። ደሙን አልፎ ሊያገኛቸው አልቻለም።

ወዳጆቼ የጎረቤት ችግር እኛን በሰላም አያስተኛም። ያ ሞተ በኵር የእስራኤልን ቤት የዘለለው ውስጥ ያሉት ሰዎችን የእውቀት ደረጃ ተመልክቶ፣ ፆታና ውበታቸውን አጮልቆ አይቶ፣ ዝናና ክብራቸውን ሰምቶ፣ ሀብት ገንዘባቸውን ተመልክቶ፣ የበራቸው ሰረገላ አልሰበር ብሎት አልነበረም የማያስነካቸውን ደም መሸሸጊያውን አይቶ ነው። ዛሬም በር ሳያንኳኳ ሀብት ዝና ክብር ሳይመለከት ከሀያላኑ እስከ ድሀው ሀገራት ዘልቆ መግባት የሚችለውን ዲያብሎስን ቀራንዮ ላይ በተሰዋው ንፁህ ፍሪዳ ክርስቶስን በመያዝ ልንሻገረው ይገባል። ደሙ የፀና ነው አንዳች ወራሪ ሀይል አያልፈውም። የዛሬው ችግር መፍትሄው ከጉልበት እስከመሬት ነው። የመስዋዕቱን ደም ይዘን መንበርከክ የመጣውን ሞት ይመክትልናል።

    ዛሬ የምንሰማው የምናየው የሀገራችን ዜና ሁሉ አስጨናቂ ነው። የሚያስነባ ልብ ሰባሪ ነው። ነገር ግን እንደ ክርስቲያን በአንድ አይናችን እያለቀስን በአንድ አይናችን በክርስቶስ ተስፋ እንበረታለን። አንናወፅ አንፍራ የሞተልን አይተወንም ለክፉ አሳልፎ አይሰጠንም። እግዚአብሄር መልካም ነው በመከራ ቀንም መሸሸጊያ ነው። የምንሸሸግበት የምንጠለልበት ታዛችን እግዚአብሄር ነው። ፀልዩ እግዚአብሄር የችግሩን ጉልበት ይሰብርልናል። የምናምነው ጌታ ከሞት በላይ አቅም ያለው፤ ከመቃብር በላይ ህይወት የሚሰጥ ነው። በዝግ በር ገብቶ ሰላም ለናንተ ይሁን ያለው ጌታ ወደ ታወከው ልባችሁ ዘልቆ በሰላሙ ልባችሁን ያረጋጋ። ቤታችሁ ሰላሙን፣ ብርታቱን፣ ፈውሱን፣ ህይወትን ይዞላችሁ ይግባ። እርሱ ሲገባ ፍርሃት ይወገዳል እርሱ ሲገባ ሞት ይወጣል። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጌታ ነውና የሞትን የበሽታን ጉልበት ይሰብራል።

አዶኒ

በድጋሚ የተለጠፈ

@adonigospel
@adonigosepl
5.2K views@doni, 12:36
ክፈት / አስተያየት ይስጡ