2022-08-26 14:56:49
ከአራት አመት በፊት ከፃፍኩት ማስታወሻ
" እግዚአብሔር ትቶኛል "
በዚህ ዓለም ላይ መከራ የማይደርስበት ቢኖር ራሱ መከራ ብቻ ነው። ስለዚህ ሁላችንም መከራ በተለያየ ጊዜ ይገጥመናል። በምንፈተንበት ጊዜ ደግሞ ከለመድነው እንጉርጉሮ መሃል እግዚአብሔር ትቶኛል፣ እግዚአብሔር ረስቶኛል፣ እግዚአብሔር አይሰማኝም የሚለው ተጠቃሽ ነው። ወዳጆቼ ፈተናው እጅግ ሲያስመርረን እግዚአብሔር እንዴት አይደርስልኝም? እንዴት ለብቻዬ ይተወኛል እንላለን። ህይወትን ሶስት መቶ ዲግሪ ማየት ስንጀምር የተደሰትነውን ያህል ማዘን እንጀምራለን፤ የሳቅነውን ያህል እናለቅሳለን፤ የጠገብነውን ያህል እንራባለን። ስለዚህ የገጠመህ መከራህ ህይወትን ሶስት መቶ ስልሳ ዲግሪ የማየትህ ማሳያ እንጂ እግዚአብሔር ትቶህ ወይም ረስቶህ አይደለም።
ንጉስ ዳዊት በእግዚአብሔር እንደልቤ የተባለ ሰው ነው።(1ኛ ሳሙ 13፥14) ይህ ማለት ቅድስናው 99.9 % የደረሰ ሰው ነው ማለት ነው። እንደውም ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ቀጥሎ ለእግዚአብሄር የቅርብ ወዳጁ ዳዊት ሳይሆን አይቀርም። ለእግዚአብሄር እንዲህ የቀረበው ዳዊት ግን እግዚአብሄር እጎኑ ያልተገኘ በሚመስለው ጊዜ ሁሉ እንዲህ በማለት በተደጋጋሚ ቅሬታውን ገልፃል። "እግዚአብሄር ሆይ ለምን እንደዚህ ርቀር ቆምህ? በመከራ ጊዜስ ለምን ድምፅህን አጠፋህ? " (መዝ 10፥1) "
ለምን ተውከኝ? "( መዝ 43፥2)
እግዚአብሔር ግን በዘመን ሁሉ ማንንም ትቶ አያውቅም ዳዊትንም አልተወውም። ታዲያ ከየት ባመጣው ባህሪው አንተና አንቺን ይተዋል? እንዲህ በማለት በተደጋጋሚ ተስፋ ተሰቶናል፦" አይለይህም ከቶም አይተውህም" (ዘዳ 31፥8)
እግዚአብሔር አልተውህም አልለይህም አለ እንጂ ህልውናዬ ሁልጊዜ ይሰማሃል በማለት ቃል አልገባም። እንደውም አንዳንድ ጊዜ ፊቱን ከእኛ የሚሰውር መሆኑን ያምናል። “የእስራኤል አምላክ መድኃኒት ሆይ፥ በእውነት አንተ ራስህን የምትሰውር አምላክ ነህ።”— ኢሳ 45፥15
በሕይወትህ የሚያከናውነውን ስራ አቋርጦ በድንገት የሚጠፋ የሚመስልባቸው ጊዜዎች አሉ። ትፀልያለህ ምንም አይሆንም፤ መንፈሳዊ ስሜቶችህ ሁሉ ትተውህ እንደጠፉ ትረዳለህ፤ ዲያብሎስን ትገስፃለህ ድርጊትህ የሚያመጣው ለውጥ የለም፤ ሀጥያትህን ትናዘዛለህ አሁንም ምንም የሚሆን ነገር አይኖርም።
ይህ መንፈሳዊ ጭጋግ እስከመቼ ነው የሚቆየው? የሚለው ነገር ያሳስብሀል። ለቀናት ለሳምንት ለወራት .... እውነት ልንገርህ ይህ ሁሉ ሲሆን አንተ ያጠፋኸው ነገር ያለ ይመስልሀል ግን አንተ ምንም አላጠፋህም። ከእግዚአብሄር ጋር ያለህን ወዳጅነት መፈተኛና ማሳደጊያ ሂደት ነው።
የእግዚአብሄር ህልውና በማይሰማህና በህይወትህ በመስራት ላይ ያለ የመሆኑ ግልጥ ማረገገጫ በማይኖርህ ጊዜ እግዚአብሄርን መውደድህን፣ማመንህን መታዘዝህን ማምለክህን ቀጥል። አዲስ ክርስቲያን በሆንክ ጊዜ እግዚአብሄር ብዙ የማረጋገጫ ስሜቶችን ይሰጥሀል በጣም ጨቅላና ግለ ተኮር ፀሎቶችህን ይመልሳል። ይህን የሚያደርገው ህያውነቱን ታውቅ ዘንድ ነው። በእምነት እያደክ ስትሄድ ግን እነዚህን ጥገኝነቶች ያቋርጣቸዋል።
መገኘቱ በማይሰማህ ጊዜ እንኳን እግዚአብሄር በቅርብህ አለ። መገኘቱ በስሜት መግለጥ የማይቻልና እጅግ ታላቅ ነው። መገኘቱ እንዲሰማህ ይፈልጋል ግን በስሜት ከምታውቀው ይልቅ በእርሱ ማመንህን ነው ይበልጥ የሚሻው። እግዚአብሄር የሚያስደስተው የስሜቶች ጉዳይ ሳይሆን እምነትህ ነው።
አዶኒ
Join፦ @adonigospel
@adonigospel
1.1K views@doni, 11:56