Get Mystery Box with random crypto!

Adoni Gospel channel

የቴሌግራም ቻናል አርማ adonigospel — Adoni Gospel channel A
የቴሌግራም ቻናል አርማ adonigospel — Adoni Gospel channel
የሰርጥ አድራሻ: @adonigospel
ምድቦች: ሃይማኖት
ቋንቋ: አማርኛ
ተመዝጋቢዎች: 6.70K
የሰርጥ መግለጫ

የእግዚአብሄርን ፍቅር፣ ምህረትና ይቅርታ በተገለጠው የወንጌሉ ቃል መሰረት የምንማማርበት ቻናል ነው። ትምህርቶቹን በሚያመቻችሁ የሶሻል ሚድያ በኩል ለመጠቀም ከስር ያሉትን ሊንኮች ይጠቀሙ።
Telegram ፦ @adonigospel
WhatsApp ፦ https://chat.whatsapp.com/BnTcBA0mML6E7gakQUIJ8X

Ratings & Reviews

3.00

3 reviews

Reviews can be left only by registered users. All reviews are moderated by admins.

5 stars

0

4 stars

0

3 stars

3

2 stars

0

1 stars

0


የቅርብ ጊዜ መልዕክቶች 3

2022-07-14 08:34:59 የልባችሁን ዕንባ ያብስላችሁ


“ሙሴም በባሕሩ ላይ እጁን ዘረጋ፤ እግዚአብሔርም ሌሊቱን ሁሉ ጽኑ የምሥራቅ ነፋስ አምጥቶ ባሕሩን አስወገደው፥ ባሕሩንም አደረቀው፥ ውኃውም ተከፈለ።”
  — ዘጸአት 14፥21


     ቀን ደምቃ በምትወጣው ፀሀይ ፋብሪካው ሲጮህ፤ መኪናው ሲተራመስ፤ ሰውም በስራ ሲሯሯጥ ስለሚውል ምድር በሁከት ትሞላለች። ፀሐይ አዘቅዝቃ ስትገባ አብዛኛው ሰው ጎኑን ያሳርፋል ምድር በፀጥታ ትሞላለች። እግዚአብሔር ለህዝቡ በሌሊት እንኳ ተግቶ የሚሰራ አምላክ ነው።

     ሌሊት ሰው የሚተኛበት፣ ብዙ ነገሮች የሚዘጉበት ብቻ ሳይሆን ሌባ ሊሰርቅ የሚወጣበት ወቅቱ ነው። ሌሊት ብዙ ወንጀሎች የሚደረጉበት፣ ብዙ እርኩሰቶች የሚከናወኑበት ሰዓት ነው። በሌሊት ግን እግዚአብሔር ባህርን ይከፍላል።

      እስራኤላውያን በሌሊት የሚመለከቱት የሚከተላቸውን ጠላት፤ የሚሰሙት የጠላታቸውን ኮቴ ነበር። እግዚአብሔር ግን የሚሰሙትና የሚያዩት ወደኋላ ስለዞሩ እንጂ ከፊታችሁ ያዘጋጀሁላችሁ ዘመናት የሚሻገር ተዓምር ነው። ኋላችሁን በማየት አትሸበሩ የፊታችሁን በማየት ተደሰቱ እያላቸው ነው።

     እግዚአብሔር የፈረቃ ሰራተኛ አይደለም። እርሱ ሊሰራ ሲነሳ የቀኗ ፀሐይ አትረዳውም፣ ሌሊቱ አያግደውም። ከጊዜ ክበብ ውጪ የሚኖር ድንቅ አምላክ ነው። እግዚአብሔር ሌሊቱን ሁሉ በእስራኤል ፊት የተጋረጠውን ባህር ሲከፍለውና ሲያስወግደው አደረ።

     ወዳጆቼ ሌሊት የሆነ የሕይወት ክፍልን እያለፋችሁ ይሆናል፤ የነፍስ ድቅድቅ ጨለማ የገጠማችሁ ወቅት ይሆናል፤ ሁሉ ነገር የተኛባችሁ፣ መንገዱም በሩም ተዘግቶባችሁ ይሆናል፤ የሚታይ ተስፋ ያለው ነገር አጥታችሁ ይሆናል፤ በተስፋ መቁረጥ በተሸናፊነት መንፈስ ዝላችሁ ወድቃችሁ ይሆናል። እግዚአብሔር ግን ከእናንተ ጋር ነው።

     ጨለማውን የምታልፉበትን ብርሃን ይሰድላችኋል፣ ገደሉን የምትሻገሩበትን ድልድይ ይዘረጋላችኋል፣ ባህሩን ሰንጥቃችሁ የምታልፉበት ተዓምርን ይሰራላችኋል። ጨለማውም ይበራል፣ ባህሩም ይከፈላል፤ እናንተም ትሻገራላችሁ።

     ነገራችሁን በጊዜው የሚያስውበው ጌታ ከእናንተ ጋር ነው። ብዙም ሳይቆይ ዘፀ 14:24 ላይ "ንጋትም ሆነ" ይላል። እስራኤላውያን ንጋት ላይ ራሳቸውን ያገኙት ተሻግረው ነው። ወዳጆቼ በሕይወታችሁ እግዚአብሔር ድንቅን ነገር አድርጎላችሁ ራሳችሁን ከጨለማው ተሻግራችሁ፣ ከችግራችሁ አልፋችሁ ታገኙታላችሁ። የደስታ ቀን ይሁንላችሁ።

አዶኒ

ሐምሌ 07/2014 ዓ.ም

@adonigospel
@adonigospel
617 views@doni, edited  05:34
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-12 09:31:29 እንደምን አደራችሁ! 

     ቀናችሁ በአዎንታዊ ነገሮችና በበረከቶች የተሞላ ይሁን። የምታደርጉት እርምጃ ሁሉ በደስታ፣ በፍቅርና በሰላም የተሞላ ይሁን። ለህይወታችሁ አዲስ ተስፋ ይስጣችሁ፤ በእያንዳንዱ ጊዜ ሁሉ እግዚአብሔር የደስታን መንፈስ ይሙላባችሁ።

    ዛሬ ለእናንተ እግዚአብሔር የእንደገና እድል በቸርነቱ ሰጥቷችኋል ምክንያቱም ዋጋ የከፈለባችሁ ጠቃሚ ልጆቹ ስለሆናችሁ ነው። እግዚአብሔር በውሏችሁ ሁሉ የእሳት ቅጥር ሆኖ ይጠብቃችሁ።
                 እወዳችኋለሁ ተባረኩ

አዶኒ

ሐምሌ 05/2014 ዓ.ም

@adonigospel
@adonigospel
1.0K views@doni, 06:31
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-11 14:07:09 “እግዚአብሔር ከዮሴፍ ጋር ነበረ፥”
         — ዘፍጥረት 39፥2


   እግዚአብሔር በህይወታችን ውስጥ ያስቀመጠውን ራዕይ ተግባራዊ እንድናደርገው ሲፈልግ የሚያስኬደን መንገዶች እንደ ፒስታ መንገድ ምቾት የማይሰጡ፣ የሚጎረብጡ፣ ከአንዱ ወደ አንዱ የሚያላትሙ ናቸው። የእግዚአብሔር ዓላማ በዚህ መንገድ ሳይሆን መከራ በሌለበት በቀይ ምንጣፍ ላይ የሚፈፀም ይመስለናል። ነገር ግን እግዚአብሔር የለም በምንልበት መንገድ እኛን ሊሰራን አብሮን አለ።

    የያዕቆብ ልጅ ዮሴፍ የመጨረሻ ልጅ እንደመሆኑ መጠን ለቤተሰቡ ተላላኪ ነው። በግ የሚጠብቅ እረኛም እርሱ ነው። እግዚአብሔር ራዕይ ሲሰጥ እድሜ አይገድበው፣ የስራ ድርሻችን አያግደው፣ አለመማራችን አይመክተውም። ዮሴፍ ብላቴና ሳለ እግዚአብሔር ራዕይ ሰጠው።

     እግዚአብሔር በዮሴፍ ላይ ያለው ዓላማ በግ በማርባት ተሸላሚ አርብቶ አደር እንዲሆንለት አይደለም። ይልቁንም በግ ከማገድ ይልቅ ለሀገሩና ለወገኑ የሚጠቅምን ስራ እንዲሰራ ነው። ስለዚህ ዓላማውን እንዲያሳካ በቤተሰቡ ዘንድ ያለውን ምቾት ማጣት ነበረበት። በወንድሞቹ መጠላት ነበረበት፤ እንደ ዕቃ መሸጥ ነበረበት። አንድ አልማዝ ተውቦ እንዲታይ ቅርፅ ይወጣለታል፣ ይቆረጣል፣ ይሞረዳል። ይሄ ሁሉ ውብ ይሆን ዘንድ ነው። መቆረጥና መሞረድ ህመም አለው ዮሴፍም በመጠላት እየተሞረደ በመሸጥ ቅርፅ እየወጣለት ነበር። ስለዚህ ስኬቱ ላይ እንዲደርስ በነዚህ ሁሉ ነገሮች መሀል ማለፍ ነበረበት።

       በወንድም በመጠላት ውስጥ እግዚአብሔር ያለ አይመስልም፣ በጉድጓድ በመጣል ውስጥ እግዚአብሔር ያለ አይመስልም፣ በመሸጡ ውስጥ እግዚአብሔር ያለ አይመስልም። እግዚአብሔር ግን በሁሉ ቦታ አብሮት ነበር።

    ወዳጆቼ ራዕይ ካላችሁ ብዙ መከራ ወደናንተ ይመጣል። ራዕይ ነበረኝ ግን እኔን ከማገዝ ይልቅ ቤተሰቦቼ አርቀው ጣሉኝ እያልክ ይሆናል። ምንም ክፉ ሳላደርግባቸው ወዳጆቼ ሁሉ አገለሉኝ እያልሽ ይሆናል። አንቺ የሚታይሽ በሰዎች መገፋትሽ ነው እግዚአብሔር በዛ ውስጥ የሚሰራውንስ ለመመልከት አስበሻል?

       ዮሴፍ የመጨረሻ ዝቃታ የሆነውን ጉድጓድ ነካ! እግዚአብሔር አብሮት ነበረና ትልቁን ከፍታ ስልጣንን ሰጠው። ልብን የሚያስተክዝ ምሬት በቤተሰብ መጠላት ነው እግዚአብሔር ግን በማያውቀው ሰው አስወደደው። ወንድሞች ተስማምተው ቢጠሉትም እግዚአብሔር ግን እጅግ ይወደው ነበር።

        ወዳጆቼ ዛሬ ራሳችንን ለምናገኝበት ለእያንዳንዱ ከፍታ እግዚአብሔር በገፊዎቻችን በአሳዳጆቻችን የሰራው ስራ አለ። እኛ ዛሬ እንረግማቸዋለን ግን የእግዚአብሔር አገልጋዮች ስለሆኑ ልንመርቃቸው ይገባል። ብዙ ነገሮች ቢዳምኑም ቢጠቁሩም እግዚአብሔር እየሞረዳችሁ፣ እያበጃጃችሁ፣ እያስጌጣችሁ እንደሆነ አስቡ። እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር ይሁን እንጂ ዓለም ሁሉ ፊቱን ቢያዞር አይድነቃችሁ። ብቻውን እግዚአብሔር በቂ ነው።

    እግዚአብሔር በዝቅታም በከፍታም ከእናንተ ጋር ይሁን።

አዶኒ

ሐምሌ 04/2014 ዓ.ም

@adonigospel
@adonigospel
1.1K views@doni, 11:07
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-08 10:27:05     “ጻድቅ ሰባት ጊዜ ይወድቃልና፥ ይነሣማል፤”
                    — ምሳሌ 24፥16


      ሕይወት እስካለህ ድረስ መውደቅ አለ ደግሞም መነሳት አለ። ውድቀት ባንተ ፍላጎት ላይ ላይመሰረት ይችላል መነሳት ግን ያንተን ፍላጎትና ውሳኔ ይፈልጋል።

      በዚህ ምድር ላይ ታሪክን የለወጡ፣ ነገርን የገለበጡ ሰዎች አትጠቅሙም የተባሉ ሰዎች ነበሩ። #አልበርት አንስታይን አራት አመት እስኪሞላው ድረስ መናገር አይችልም ነበር። በአስተማሪውም አንተ ለትምህርት የማትጠቅም ሰው ነህ ተብሏል። በተለያዩ የትምህርት ተቋማት ገብቶ ለመማር ብዙ ጊዜ ሞክሮ አልተሳካለትም። ነገር ግን በትዕግስትና በጥረት ፈተናዎችን ተቋቁሞ የክፍለ ዘመናችን ተወዳዳሪ የማይገኝለት ምርጥ የሒሳብ ሊቅና ሳይንቲስት ሆኗል።

      ዛሬ ጠላት አንተኮ አትችልም ይልሃል፣ አንቺኮ እንዲህ አይነት ድክመት አለብሽ ስለዚህ ይህንን ማድረግ አትችዪም ይልሻል፣ ሰዎች ይመጡና ይህ በእናንተ አቅምና እውቀት አይሳካም ብለው ተስፋ ያስቆርጧችኋል። ወዳጆቼ እናንተ ግን ከአይቻልም በላይ አሻግራችሁ ይቻላልን ተመልከቱ። ከተሸነፈበት ጊዜ በላይ አንድ ጊዜ መነሳት የሚችል ሰው አሸናፊ ይሆናል። መውደቅ ችግር አይደለም። ነገር ግን ወድቆ መቅረት ችግር ነው። ተነሳ ምክንያቱም ስኬት የሚጀምረው ከወደክበት በመነሳት ነው።
   
      አንዳንድ ነገሮች የማይቻሉ ዓለቶች ሆነው ውስጣችን ተቀምጠው ይሆናል። እስራኤላውያን ሁሉ ጎልያድን የሚጥል ምንም ኃይል አለው ብለው አላሰቡም። እጣችን ብለው ያሰቡት በእርሱ እንደ እንጀራ ተጠቅልሎ መጎረስና በእርሱ አለንጋ መሞትን ነው። ነገር ግን አይቻልምን አልፎ ማየት የቻለው ብላቴናው ዳዊት ግን ይቻላል ብሎ ተነሳ ትልቁን ትንሽ አደረገው ገዳዩን ሙት አደረገው። በህይወታችን ከእግዚአብሔር ጋር የማንችለው ነገር የለም።

     ዛሬም ወዳጆቼ የውድቀት ዜማን ልናዜም እንችላለን። ደክሞኛል በጤንነቴ አሳሳቢ ሁኔታ ላይ ደርሷስ ስለዚህ ራዕዬን መፈፀም አልችልም፤ ገንዘብ በማጣት በጣም እየተፈተንኩ ነው ስለዚህ እቅዴን ዳር ማድረስ አልችልም እያልክ ይሆናል። ለአመታት ምንም ቢገጥምህ እንደምታሸንፍና ጥሰህ እንደምታልፍ ታምን ነበር አሁን ግን ሰልችቶሃል ደክሞሃል የሚሆን አይመስለኝም ማለት ጀምረሃል።

      ወዳጄ በአንተ አይን ፊት ሁሉም ችግር ከባድ ነው። እስቲ ችግርህን በእግዚአብሔር ዓይን ተመልከተው። እስቲ ፈተናህን በእግዚአብሔር አይኖች ተመልከተው።
ፈተናህን የምታልፍበት ገንዘብ የለህም ግን ከገንዘብ በላይ የሆነውን እግዚአብሔርን ይዘሃል፤ መከራህን የምትጋፈጥበት እውቀትና ጥበብ የለህም ግን ከእውቀትና ከአዕምሮ ጥበብ በላይ የሆነውን እግዚአብሔርን ይዘሃል።

      አይዞህ አልችለውም የምትለውን የሚያስችልህ ጌታ ካንተ ጋር ነው። አይሆንም የምትለውን ነገር የሚያሳካልህ ጌታ ካንተ ጋር ነው። አንተ ብቻ መሞከርህ እንዳታቋርጥ።

አዶኒ

ሐምሌ 01/2014 ዓ.ም

@adonigospel
@adonigospel
1.7K views@doni, 07:27
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-07 07:33:43           የማይጠገበው ርዕስ ፍቅርርር

   “ፍቅር ይታገሣል፥ ቸርነትንም ያደርጋል፤ ፍቅር አይቀናም፤ ፍቅር አይመካም፥ አይታበይም፤”
  — 1ኛ ቆሮንቶስ 13፥4

      ፍቅር አካል የለውም ግን ተገልጦ ይታያል፤ ፍቅር አይዳሰሰም ግን ብዙዎችን ይዳስሳል፤ ፍቅር ኪሎው ስንት ነው አይባልም ከልክ ያለፈ ነው። ፍቅር በሰውነታችን ውስጥ እንደ ኩላሊት፣ እንደ ልብ፣ እንደ ጨጓራ አንድ ስፍራ ይዞ እዚህ ጋር ነው የተቀመጥ አይባልለትም በመላ ማንነታችን ውስጥ የፈሰሰና የተሰራጨ ነው። ፍቅር በዓይኖቻችን ሆኖ ሰው የረሳቸውን ይመለከታል፤ ፍቅር በእጃችን ሆኖ የወደቁትን ያነሳል፤ ፍቅር በእግራችን ሆኖ ወዳጅ ወደሌላቸው ሰዎች ይገሰግሳል፤ ፍቅር በልባችን ሆኖ ሰውን ሁሉ ያፈቅራል።

      ፍቅር ስሜት አይደለም እውነት ነው። ስሜት ተለዋዋጭ ነው ፍቅር ግን የጸና ነው። ለዚህ ነው መጽሐፍ ቅዱስ ፍቅርን ከስሜት ጋር ብቻ
አያይዞ የማይጠቅሰው። ፍቅር ሰፊ የትዕግስት ትከሻ አለው፤ ፍቅር ለሌሎች የሚተርፍ ቸርነት አለው፤ ፍቅር በሰዎች ደስ ይሰኛል እንጂ አይቀናም፤ ፍቅር ዝቅ ብሎ የሚያከብር እንጂ ከፍ ብሎ የሚያዋርድ አይደለም።

      ወዳጆቼ እኛ ፍቅር የምንለው አለመተዋወቅን ነው። ይህ ማለት አንድን ሰው ያወቅነው መስሎን በጣም መልካም፣ ደግ፣ ጨዋ፣ ሩህሩህ ነው ብለን እንወደዋለን። ልክ እንድ የማንጠብቀውን ነገር ሲያደርግ ስናይ እንዲህ አይነት ሰው መሆኑን አላውቅም ነበር፣ እንዲህ አይነት መልኩን በፍፁም አላስተዋልኩም ብለን ስናውቀው እንጠላዋለን። ፍቅር ግን እንዲህ አይደለም። እውነተኛ ፍቅር የሚመጣው ስለ አንድ ሰው ጥንካሬና ድክመት በሚገባ ስናውቅ ነው።
እውነተኛ ፍቅር የያዘው ሰው እነዚህን ነገሮች
የሚያደርገው ጭፍን ስለሆነ ወይም ስለሚወደው ሰው ምንም ስለማያውቅ አይደለም፤ ከዚህ ይልቅ ስለ ግለሰቡ ማንነት የተሟላ እውቀት ስላለው ነው።

      የፍቅር ሚዛኑ ካፍቴርያ ውስጥ መሳሳቅ መቻል አይደለም ትዕግስትን የሚፈታተኑ ድክመቶቹን ሳይሰለቹ በልበ ሰፊነት እያረቁ በትዕግስት መሸከም ሲቻል። በቸገረው ሰዓት፣ እጁ ባዶ በሆነበት ሰዓት እኔን ላንተ እግዚአብሔር የሰጠኝ ባዶ በሆንክበት ጊዜ ድክመትህን ሸፍኜ መቆም እንድችል ነው ብሎ ቸርነትን ማድረግ ነው።

    ሀበሻ በሰው ማጣት ይደሰታል በሰው መሳካት ግን ይከፋል። ክርስቲያን ግን የሰውን ስኬት ሲመለከት ከልቡ የእውነት መደሰት መቻል አለበት። ከደስታው ባለፈ በቻለው መጠን ለስኬቱ አስተዋጽዖ ማድረግ ይኖርበታል። ምክንያቱም ብዙ ጊዜ የልብ ወዳጅ ሳይሆን የጥርስ ብቻ ወዳጅ ስለሆንን እንስቃለን ልባችን ግን ጥላቻን ያመረቅዛል። ይህ ማንነታችን ብዙ አጠገባችን ያሉ ለብዙ ነገር መትረፍ የሚችል ራዕይ ተሸክመው ቁጭ ያሉ ሰዎችን በድካማቸው ገብቶ የሚረዳቸው የሚደግፋቸው ሰው ባለመኖሩ ከነራዕያቸው ያረጃሉ ያልፋሉ ።

     ወዳጆቼ አጠገባችሁ ያለውን የምታውቁትን፣ ወዳጄ የምትሉትን ሰው ራዕይህ ምንድነው? በቀጣይ ምን ለማድረግ አስበሃል? በአንተ ራዕይ ውስጥ የኔ ተሳትፎ ምን መሆን ይችላል? ብላችሁ ጠይቋቸው። የምትችሉትን ያህል ተዘርጉላቸው እናንተም እነርሱም ደስተኛ ትሆናላችሁ። እግዚአብሔር ፍቅርን ያብዛላችሁ።

አዶኒ

ሰኔ 30/2014

@adonigospel
@adonigospel
1.5K views@doni, edited  04:33
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-06 07:52:27 “በእኔ ኑሩ እኔም በእናንተ።”
  — ዮሐንስ 15፥4

    
     ብዙ ዘመን በራሳችን ኖረናል ግን አልተሳካልንም፣ ብዙ ዘመን እንደ ፍቃዳችን ኖረናል ግን ነፍሳችን ደስ አልተሰኘችም፣ ብዙ ዘመን በእውቀታችን ተጉዘናል ከኃጢአት በቀር ያተረፍነው የለም። ሕይወታችን ተጎሳቁላለች አሁን ግን መኖሪያችንን እንቀይርና በክርስቶስ ሕይወት ውስጥ እንኑር።

     መኖር በገንዘብ አይደለም መኖር በእግዚአብሔር ነው፤ መኖር በብልጠት አይደለም መኖር በክርስቶስ ነው። መኖሪያ የሚመስሉን ነገሮች የሚጠፉና የሚከስሙ ናቸው። መኖሪያ የምንላቸው ነገሮች እኛ በእነርሱ ውስጥ እንኖር ይሆናል እንጂ እነርሱ በእኛ ውስጥ አይኖሩም። ክርስቶስ ብቻ በእርሱ ስንኖር እርሱም በእኛ ውስጥ ይኖራል።

    ወዳጆቼ ለምንድነው ክርስቶስ በእኔ ኑሩ ያለን? ትዳሮች ስለሚወድቁ፣ ሀብት ስለሚሸሽ፣ ጤና ስለሚጠፋ፣ ንብረት ስለሚበላሽ፣ ጓደኞች ስለሚከዱ፣ መተማመን ስለሚፈርስ ምንም የሚቆይ ነገር ስለሌለ በእኔ ኑሩ አለን።

    በክርስቶስ ስንኖር ምንም ነገር በማይቆይበት ጊዜ እንኳ በዋስትና መቆየት እንችላለን። በምድር ላይ የሚቆይ ቀርቶ የሚዘገይ ነገር የለም። ሁሉም እንደ ጤዛ ታይቶ ይጠፋል። አንድ ግን አለ ጸንቶ የሚኖር እርሱም ክርስቶስ ነው።

   በእርሱ መኖር ስንጀምር ቋሚ እንደሆንን እናምናለን፣ ፍፁም ጀርባውን አያዞርብንም፣ ሁሉም ሲፈርስ ዘላለም ፀንቶ ይኖራል፣ ሁሉ ሲንሸራተት እርሱ ብቻውን ዐለትና ጋሻ ሆኖ ይኖራል፣ ከረገጥነው መሬት በላይ የሚታመን ጌታ ነው።

     በክርስቶስ መኖር ሁሉን በሚችል አምላክ ጥላ ውስጥ መኖር ነው። በክርስቶስ መኖር ወደፊት መገስገስ እንጂ ወደ ኋላ አለመመለስ ነው። በክርስቶስ መኖር በጥበቃው ስር መሆን፣ በእርሱ መገኘት ከበባ ውስጥ መሆን፣ ከጠላቶች መጠበቅ፣ በእጁ መያዝ፣ በእውቀቱና በመንፈሱ መመራት፣ በእርሱ እንክብካቤ ላይ መደገፍ፣ በኃይሉና በሉዓላዊነቱ ላይ ማረፍ ነው።

                 አዶኒ

ሰኔ 29/2014 ዓ.ም

@adonigospel
@adonigospel
1.4K views@doni, edited  04:52
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-05 13:34:17
ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን መስቀል ላይ የያዘው ምስማር ሳይሆን ፍቅር ነው።

@adonigospel
@adonigospel
1.4K views@doni, 10:34
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-05 07:50:11 የሚያበረታ ወዳጅ


“ከዚህም በኋላ ጌታ ሌሎቹን ሰብዓ ሾመ፥ ሁለት ሁለትም አድርጎ እርሱ ሊሄድበት ወዳለው ከተማና ስፍራ ሁሉ በፊቱ ላካቸው።”
  — ሉቃስ 10፥1

     
       ግለኝነት የዓለም ስርዓት ሲሆን ህብረት ግን የእግዚአብሔር ዓላማና እቅድ ነው። ጌታችን የመረጣቸውን ሁለት ሁለት አድርጎ ለአገልግሎት ይልካቸው ነበር። ጥቅሙም አንዱ ሲዝል አንዱ እንዲያበረታው ነው። መንፈሳዊ ጉዞ መንገዱ ረጅም ነው ስለዚህ ማንም ሜዳ እንዳይወድቅ ልቡም እንዳይደነድን እርስ በእርስ መበረታታት ግድ ነው።

     እርስ በእርስ መበረታታት ማለት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በማመን የጀመረውን የክርስትና ጉዞ እንዳያቋርጥ እግዚአብሔርን በማገልገል እንዲቀጥል ድጋፍ ማድረግ ነው።

      አንድ ሯጭ በመሮጫ ሜዳው ውስጥ ከገባ በኋላ እስከመጨረሻው እንዳይቀጥል የሚያደርጉት አስቸጋሪ ነገሮች ይገጥሙታል። ከጎኑ የሚወጋው ከባድ ህመም፣ ድካም፣ ተስፋ መቁረጥ ይገጥሙታል። ይህ ሯጭ እነዚህ ሁሉ ነገሮች እንዳያስቆሙት ማበረታቻ ያስፈልገዋል። አይዞህ ደርሰሃል፣ ማሸነፍ ትችላለህ፣ ጎበዝ ቀጥል የሚሉ የማበረታቻ ድምፆችን ሲሰማ ውስጡ የከሰመው ጉልበት ይታደሳል በተስፋ መገስገስ ይጀምራል።

     በህይወት ውስጥ እንደ አማኝ፣ እንደ አገልጋይ ሊያጋጥሙን የሚችሉ ብዙ ፈተናዎች ይኖራሉ። እነዚህ ፈተናዎች በቀጥታ እግዚአብሔርን የሚቃወሙ ባይሆንም ከእግዚአብሔር ጋር የሚያደርገው ጉዞ እንዲስተጓጎል ሊያደርጉት ይችላሉ። ብዙ እግዚአብሔርን ያገለግሉ የነበሩ ሰዎች እኛም የተገለገልንባቸው ሰዎች አይዟችሁ የሚል ደጋፊ በማጣታቸው ብዙ የችግር ዱላ አርፎባቸው ሜዳ ቀርተዋል። እነዚህ አገልጋዮች እንዲቀጥሉ ማበረታታት ከጎናቸው በመሆን ጉድለታቸውን መሸፈን ይገባናል። 

     እናንተም ወደተሳሳተ አቅጣጫ የሚሄዱ፤ ወዳልተፈለገ ጎዳና የሚያስገቡ ፈተናዎች የገጠሟቸው ጓደኞች ሊኖርዎት ይችላሉ። በዚህ ጊዜ ነው የናንተ ማበረታቻና ትክክለኛውን ነገር ማድረግ እንዲችሉ ማበርታት ያለባችሁ። ግለሰቡን ማውገዝ፣ ስህተቶቹን መጠቆም ሳይሆን ፍቅርን ማሳየት አለውልህ ማለት ሰውዬውን ከሞት የማስነሳት ያህል አቅም ትሆኑታላችሁ።

      የሚያበረታ ወዳጅ ሲኖራችሁ ልባችሁ እንዳይደነድን ያደርጋል። በኃጢአት ልምምድ ውስጥ እንዳትወድቁ ይጠብቃችኋል። እግዚአብሔር የሚያበረታ ወዳጅ ይስጣችሁ፤ እናንተንም የሚሰብር ሳይሆን የሚያበረታ ወዳጅ ያድርጋችሁ።

አዶኒ

ሰኔ 28/2014

@adonigospel
@adonigospel
1.5K views@doni, edited  04:50
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-04 10:12:26 የፍቅር አቅም


   "ዓለም በፍቅር ተጀመረች ዓለም በፍቅር ውስጥ አደገች ፍቅር በዓለም ውስጥ የጥንካሬ ምንጭ ነው። ፍቅር እውነት ነው። ሕይወት ከሞት ይልቅ ደካማ ናት ሞት ደግሞ ከፍቅር ይልቅ ደካማ ነው። ከሞት ቀጥሎ ሰው የማይመርጥ ረቂቅ ኃይል ቢኖር ፍቅር ነው።

     ተወዳጅ የፍቅር ስጦታ አበባ፣ ቸኮሌት፣ ወርቅ አይደለም ራስን መስጠት ነው። ራሱን የሰጠ ሰው ከእርሱ የሚያንሱትን ለመስጠት አይቸገርም። ብዙ ኃጢአት፣ ብዙ በደል፣ ብዙ ድክመት በፍቅር ይሸፈናል። ያለ ፍቅር ሕይወት ትርጉም አልባ ነች።

      ሕይወት ያለ ፍቅር ባዶ ናት። ጣዕሟን ታጣለች። በዚህ ግራ በሚያጋባና በመረረች ዓለም ውስጥ ሕይወትን ጣፋጭ የሚያደርጋት ፍቅር ነው። የፍቅር ዋናው ነገር ለሌሎች የምናስበው የንናደርግላቸውና የምንለግሳቸው ሳይሆን ከእኛነታችን የምንሰጣቸው መጠን ነው።

     እውነተኛ ፍቅር የራሱን ገደብ ያውቃል፣ የሰውን ገደብ ያከብራል፣ ነገሮችን በጥንቃቄ ይከውናል፣ ስሜትን ከመጉዳት ይቆጠባል፣ በመከራ ይጸናል በተስፋ ያጽናናል። ፍቅር ከእኔነት ወደ እኛነት ይሸጋገራል። በችግሩ ላይ ሳይሆን በመፍትሄው ላይ እንድናተኩር ይረዳናል።

     ብዙዎቻችን ሰውን ለመጥላት አንፈተንም። አንድን ሰው ለመጥላት ሁለቴ አናስብም ሰውን ለመውደድ ግን እንፈተናለን፣ በነፃ ለማፍቀር እንቸገራለን። ታክሲ ላይ  "እንኳን ለጠብ ለፍቅርም በማትበቃ እድሜ አንጣላ" ብለው ይለጥፋሉ። አዎ አንድ እውነት አለ እርሱም ይህችን ዓለም ጥለን እናልፋለን። ስለዚህ እያንዳንዷን እለት በፍቅር እንኑራት። አንዳችን ለአንዳችን በተግባር በተገለጠ ፍቅር እንዋደድ። ቸር ያውላችሁ ፍቅር ይብዛላችሁ።"

@adonigospel
@adonigospel
1.4K views@doni, edited  07:12
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-03 08:23:16 "ያልጠፋነው ከእግዚአብሔር ምህረት የተነሳ ነው"
                       ሰቆ ኤር 3፥22


      ሰው የመኖር ተስፋ እንዳለው ሁሉ የመጥፋትም ስጋት አለበት። እግዚአብሔር የማያስፈልግበት የህይወታችን ቀጠና የለም። ሁሉም ሰው በዚህ ሰአት ገንዘብ አያስፈልገውም አንዳንዶች እንጂ፣ ሁሉም ሰው ጤና አያስፈልገውም የታመሙት እንጂ፣ ሁሉም ሰው ቤት አያስፈልገውም ቤት አልባው እንጂ.....ሁሉም ሰው ግን አንድ ነገር እኩል ያስፈልገዋል። ምህረቱ!!

       እኛ የሰው ልጆች የገዛ የጫማ ማሰሪያችን ጠልፎ የሚጥለን ኋላም የምንሰበር ቅርብ የሆንን በጣም ስስ ፍጥረቶች ነን ምህረቱ ግን ከመሰናክሉ ያድነናል፤ እኛ የጠጣነው ውሃ ትን የሚለን በዛውም የምናሸልብ ደካሞች ነን ነገር ግን ምህረቱ ሲጋርደን የጠጣነው ውሃ ይስማማናል፤ እኛ ከተወረወረብን የጠላት ቀስት መትረፋችንን እንጂ ሳናየው ጠላት ከማሰልን ጉድጓድ እንደተሻገርን አናስብም ምህረቱ ግን እንደ አየር በውስጣችንም በውጫችንም ከቦ ጠብቆናል።

       ወዳጆቼ ያልጠፋነው በቂ ገንዘብ ስላለን አይደለም፣ ያልጠፋነው ሰፈራችን ሰላም ስለሆነ ብቻ አይደለም፣ ያልጠፋነው እውቀታችን የላቀ ስለሆነ አይደለም፣ ያልጠፋነው ከጥፋት ክልል ስለራቅን አይደለም፣ አዎ ያልጠፋነው የሚያጠፋን ስለተኛልን ሳይሆን የእግዚአብሔር ምህረት ስለጋረደን ነው።

       እኛ ማለት እንደ ጠዋት ጤዛ ታይተን ለመጥፋት፣ ነበረ(ነበረች) ለመባል ቅርብ የሆንን፣ እንደ እንፋሎት በሰከንድ ተነን ከመኖር ወዳለመኖር የምንቀየር ምስኪን ነን ነገር ግን በምህረቱ ባለፀጋ የሆነው አምካላችን እግዚአብሔር ከምናየውም ከማናየውም ጋርዶ በሰላም ስላቆመን ነው።

        በየዕለቱ ከአየር እኩል ምህረቱን እንተነፍሳለን ሰላም ወተን ለመግባታችን ግን ምስጋና አንሰጠውም። መብላት የማይችሉ የተዘጉ ጉሮሮዎች ባሉበት እኛ በልተን ይስማማናል ስለዚህ አናመሰግንም፤ ንፁህ ውሃ ማግኘት አቅቷቸው የደፈረሰ ወንዝ የሚጠጡ ወገኖች ባሉበት ዛሬ ቢራ መጠጫ አጣሁ ብሎ ተክዞ የሚውል ሲነጫነጭ የሚያመሽ ብዙ ነው። ለምን ምህረቱ ይጋረድብናል? ለምህረቱ የምንከፍለው ተመጣጣኝ ዋጋ የለም ምላሻችን ነፃ የሆነው ምስጋና ነው። ለመለመን ማልደን በፊቱ እንደፋለን ለማመስገን ዘመናት ነጉደውብናል።

          ምህረቱ የፍቅሩ ልጅ ናት ፡፡ ምህረቱ የልባችንን ስቃይ የሚያቃልል ፍቅር ነው፤ ምህረቱ የተራቡትን የሚያረካ እንጀራ ነው፤ ምህረቱ ስንጥቁን ልብ፣  የተጠማውን የነፍስ ጥማት የሚያረካ ቅዱስ ውሃ ነው፤ ምህረቱ የባዕድ አገር ሰው መኖሪያ ፍቃድ ነው፤ ምህረቱ እርቃናቸውን ለሆኑ ሁሉ የሚሸፍን ካፖርት ነው፤ ምህረቱ ለታመሙት ሥቃያቸውን የሚያረጋጋ ዘይት ነው፤ ምህረቱ በእስር ላይ ያሉትን የሚያጠናክር ቃል ነው።

         ይህ ምህረቱ ስለበዛልን በህይወት ቆመናል።
==//==

      የመፅናናት አምላክና አባት እግዚአብሔር ሆይ በዙፋንህ ተመስገን፣ በመንበርህ ተመስገን፣ በመንግስትህ ተመስገን። አቤቱ እግዚአብሔር ሆይ የሚያጠፋን ስላላጠፋን አንተ ግን ምህረትህ በዝቶልን ስላኖርከን እናመሰግንሀለን። አቤቱ ምህረትህን እንዳናይ የጋረደንን አለማስተዋል አንሳልን፣ አዚሙን ንቀልልን፣ በማስተዋላችን የተደገፍንበትን፣ በገንዘባችን የተመካንበትን ዘመን ይቅር በል። ድጋፋችን ምህረትህ ስለሆነልን፣ አቅማችን ምህረትህ ስለሆነልን፣ ምርኩዛችን ምህረትህ ስለሆነልን፣ የመኖራችን አምሮት ምህረትህ፣ የመኖራችን ዋስትና ምህረትህ ስለሆነ ክብር ላንተ ይሁን። ተመስገን እግዚአብሔር
  በድጋሚ የተለጠፈ

አዶኒ

                     ---------//---------
                    ቻናሉን ይቀላቀሉ
                        
@adonigospel
@adonigospel
4.8K views@doni, 05:23
ክፈት / አስተያየት ይስጡ