Get Mystery Box with random crypto!

ዉጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በተለያዩ አገራት የሚገኙ ዲፕሎማቶች ስለ አገራቸዉ ጥቅም የተሻለ ስራ የሰሩትን | YeneTube

ዉጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በተለያዩ አገራት የሚገኙ ዲፕሎማቶች ስለ አገራቸዉ ጥቅም የተሻለ ስራ የሰሩትን እና ያልሰሩትን ሊገመግም ነው፡፡

ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ኢትዮጵያ አሁን ላይ ከአለም አቀፉ ማህበረሰብ እየገጠማት ያለዉን የተዛባ አመለካከት ለማስረዳት ሁሉም ድፕሎማቶች ስለ አገራቸዉ ብሄራዊ ጥቅም በትኩረት እንዲሰሩም አሳስቧል፡፡

የተወሰኑ ድፕሎማቶች በአለም አቀፍ መገናኛዎች ጭምር በመቅርብ በኢትዮጵያ ስላለዉ ሁኔታ እንዲሁም ስለ ህዳሴ ግድብ ግንባታ እያስረዱ ቢሆንም አብዛኞቹ ግን ብዙ የቤት ሥራ ይጠብቃቸዋልም ተብሏል፡፡

የዉጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ስለ አገራቸዉ ብሄራዊ ጥቅም የተሸለ አፈፃፀም የሰሩና ያልሰሩ ዲፕሎማቶችን በቁጥር ጭምር በመያዝ እንደሚገመግምም ኢትዮ ኤፍ ኤም ከሚኒስቴሩ ያገኘዉ መረጃ ያመለክታል፡፡

ኢትዮጵያን ወክለዉ በተለያዩ አገራት የሚገኙ የዲፕሎማት ማህበረሰቦች ባገኙት አጋጣሚ በአለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን እና በማህበራዊ ሚዲያዎችም ጭምር የአለም አቀፉ ማህበረሰብ ስለ ኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ ግንዛቤ እንዲኖረዉ በትኩረት እንዲሰሩም ጥሪ ተደርጓል፡፡

ከዚህ በተጨማሪም በተለያዩ አገራት የሚኖሩ የዲያስፖራ ማህበረሰብ እና ምሁራን የአገሪቱን ብሄራዊ ጥቅም በማስጠበቅ ረገድ ብዙ ስራዎችን ሊሰሩ ይገባል ተብሏል፡፡

በሰሜኑ የአገሪቱ ክፍል በነበረዉ የህግ ማስከበር ሂደት ጋር ተያይዞ የአለም አቀፉ ማህበረሰብ የተዛቡ መረጃዎችን እንደያዘ ያስታወቀዉ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ እዉነታዉን ለማስረዳት ሁሉም ዜጋ የበኩሉን እንዲወጣ ጥሪ አስተላልፏል፡፡

ከህዳሴ ግድብ እና ከኢትዮ ሱዳን የድንበር ዉዝግብ ጋር ተያይዞም ዲፕሎማቶች፤ ምሁራን፤ ዲስፖራዎች፤ እና የአገር ዉስጥ ሚዲያዎች ጭምር ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ ስለ አገራቸዉ ተጨባጭ ሁኔታ ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ማስረዳት አለባቸዉ ተብሏል፡፡

[Ethio FM]
@YeneTube @FikerAssefa