2022-06-21 13:32:42
ጥበብ የመንፈስ ቅዱስ ስጦታ
በክቡር አባ ጴጥሮስ በርጋ
በዮሐንስ ወንጌል ም. 4 ቁ 10 ላይ እንደ ተጠቀሰው መንፈስ ቅዱስ የእግዚአብሔር ስጦታ ነው፡፡ እሱ እራሱ መንፈስ ቅዱስ ልባቸውን ከፍተው ለሚቀበሉት መንፈሳዊ ስጦታዎችን ያድላል፡፡ ከእነዚህም ስጦታዎቹ መሃከል አንዱ ስለሆነው ስለ ጥበብ፤ በራሱ በመንፈስ ቅዱስ እገዛ ተደግፈን እናስተነትናለን፡፡ ይህ የመንፈስ ቅዱስ ስጦታ የሆነው ጥበብ የእግዚአብሔርን ፈቃድ በሕይወታችን፣ በአገልግሎታችን በተሰማራንበት ቦታ ሁሉ እንድንገነዘብ የሚያደርገን ውስጣዊ ብርሃን ነው፡፡
ጥበብ ከሰው ዕውቀትና ልምድ ያልሆነ የመጀመሪያው የመንፈስ ቅዱስ ስጦታ ነው፡፡ ይህ ጥበብ በ1ኛው መጻፈ ነገስት 3፤9 ላይ ሰለሞን የእሥራኤል ንጉስ ተደርጎ በተሾመበት ዕለት እግዚአብሔር እንዲሰጠው የጠየቀው ስጦታ ነው፡፡ ስሆነም እንደ መጽሐፍ ቅዱስ አገላለጽ ጥበብ፤ ሁሉንም ነገሮች በእግዚአብሔር አይን መመልከት የመቻል ጸጋ ነው፡፡ የመንፈስ ቅዱስ ስጦታ የሆነው ጥበብ፤ ዓለምን፣ ሁኔታዎችን፣ ችግሮችን፣ ፈተናዎችን፣ ስኬትም ሆነ ሽንፈትን፤ የምንገኝበት ሁኔታ ሁሉ በእግዚአብሔር እሳቤ ውስጥ የመመልከት ችሎታ ነው፡፡ ጥበብ እኛ ነገሮችን በእግዚአብሔር ዓይን የማየት ብስለት እስክናዳብር ድረስ መንፈስ ቅዱስ በእኛ ውስጥ በቀጣይነት የሚያከናውነው ሥራ ነው፡፡ ይህን ዓይነት ጥበብ የምናገኘው ደግሞ ከራሱ ከእግዚያብሔር ጋር ካለን ግንኙነት ነው፡፡ እንደ ልጆች ሆነን ከእግዚያብሔር አባት ጋር ከምናደርገው ጉዞ ይመነጫል፡፡ ከእግዚአብሔር ጋር የልጅነት ትሥሥር ሲኖረን፤ መንፈስ ቅዱስ እራሱ ይህንን የጥበብ ስጦታ ይሰጠናል፡፡ ከአምላክ ጋር ባለን ግንኙነት መንፈስ ቅዱስ ቀስ በቀስ ልባችንን፣ አስተሳሰባችንን ይቀይራል፤ እኛን ለእግዚአብሔር ፈቃድ ያዘጋጀናል፤ ፈቃዱንም የመረዳት ጥበብ ያጎናጽፈናል፡፡
ስሆነም እኛን እንደ ክርስቲያን ጥበበኞች የሚያደርገን መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ ይህ ማለት ደግሞ ለሁሉም ነገር መልስ አለን፤ ሁሉንም ነገር እናውቃለን ማለት አይደለም፡፡ ነገር ግን ስለ እግዚአብሔር በማወቅ እንበለጽጋለን፤ እግዚአብሔር እንዴት እንደሚሰራ እንገነዘባለን፣ በመንፈስ ቅዱስ ጥበብ ስንመራ፤ በዙሪያችን የሚሆነው ነገር ከእግዚአብሔር መሆኑንና አለመሆኑን ይንለያለን፤ የምናደርጋቸው ውሳኔዎች፣ የምንከተለው መንገድ፣ በየዕለቱ የምንመርጠው ምርጫ ከእግዚአብሔር ፈቃድ አኳያ ስለመሆኑን እናስተውላለን፡፡ እንደ ክርስቲን እንዲህ አይነቱ ጥበብ በልባችን ካለ፤ ከውጭ በምናያቸው ነገሮች ሳንደናገጥና ተስፋ ሳንቆርጥ ለሚቀርቡን ሁሉ የሕይወትን ጣዕም ልንሰጥ እንችላለን፡፡
ንጉስ ሰለሞን እንዳደረገው በመሪነት፣ በአገልግሎት ዘርፍ፣ በቤተሰብ አስተዳዳሪነት እና በተለያዩ የሕይወት ስምሪቶች ውስጥ ስንገኝ፤ በዚህ የመንፈስ ቅዱስ ስጦታ በሆነው ጥበብ ስንመራ መልካም ነው፤ የእግዚአብሔርንም ፈቃድ የማወቅ አቅማችን ይጎለብታል፡፡ ይህ ጥበብ ምርጫዎቻችንን፣ ውሳኔዎቻችንን መንገዳችንን ሲመራ እናያለን፡፡ ይህ ጥበብ ሁሉንም ነገሮች በእግዚአብሔር ዓይን እንደ እግዚአብሔር ሐሳብ ማስኬድ እድንችል ያደርገናል፡፡
እንደ ክርስቲያንና በእግዚአብሔር መንፈስ ጥበብ እንደ ተሞላ ሰው፤ በማህበረሰባችን፣ በሥራ ቦታችን በተለያዩ የሕይወት ዘርፍ ውስጥ ስንገኝ መንገዳችንን አቅንተን፤ መንገድ የምንጠቁም፤ ይህ ከእግዚአብሔር ነው፤ ያ ደግሞ ከእግዚአብሔር አይደለም የምንል፣ የጊዜውን ሁኔታ መለየት የምንችል መሆን ይጠብቅብናል፡፡ በተሰማራንበት ሁሉ በዚህ ጥበብ መመራት ስንችል፤ የእግዚአብሔር ሰላምና ዕርቅ በመሃከላችን ይሰፍናል፡፡ ንጉስ ሰለሞን ለእግዚአብሔር ‹‹ሕዝብህን ለመምራት ካንተ የሆነው ጥበብ ያስፈልግኛል›› ሲል፤ የሕዝቡን፤ በአስተሳሰብ፣ በማንነትና በፍላጎት የተለያየ መሆንና ያን ሕዝብ ደግሞ ወደ አንድነት ለማምጣት የፍቅር፣ የዕርቅ መንፈስ እንደሚያስፈልገው ስላመነ ነው፡፡ ዛሬ እያንዳንዳችን በተሰማራንበት ቦታ ሁሉ ብናስተውል፤ የሚያስፈልገን ይህን የሰላምና የዕርቅ መንፈስ ነው፡፡ እያንዳንዳችን ለዚህ የሰላምና የዕርቅ ግንባታ ጉዞ ላይ መንፈስ ቅዱስ በሚሰጠን የጥበብ ስጦታ አማካኝነት አስተዋጾ እንድናደርግ እንጠራለን፡፡
ይህን ጥበብ ስንከተል፤ እግዚአብሔር በሕይወታችን ይናገራል፡፡ ሁለነገራችን የእግዚአብሔርን መገኘት ይናገራል፤ ያከብራልም፡፡ ይህ እኛ ልንፈጥረው የምንችለው ነገር ሳይሆን እግዚአብሔር ለመንፈስ ቅዱስ ክፍትና ታዛዥ ለሆኑት የሚያበረክተው ሥጦታ ነው፡፡ እኛ ውስጥ መንፈስ ቅዱስ አለ፤ የማዳመጥም ሆነ ያለማዳመጥ ነጻነት አለን፡፡ ብናዳምጠው ይህን የጥበብ መንገድ ያስተምረናል፤ ይህም በእግዚአብሔር ዓይን የማየት፣ በእግዚአብሔር ጆሮ የማዳመጥ እና በእግዚአብሔር ልብ የማፍቀር እንዲሁም በእግዚአብሔር ፍርድ ነገሮችን የመፍረድ አቅም እንዲኖረን ያደርጋል፡፡ ከጠየቅነውና ለመቀበልም ዝግጁዎች ከሆንን ፤ መንፈስ ቅዱስ የሚለግሰን የጥበብ ስጦታ ይህ ነው፡፡
በዚህ ጥበብ ብቻ ተመርተን፤ ማህበረሰብን፣ ቤተሰብን፣ ቤተክርስቲያንን መገንባት እንችላልን፡፡ መንፈስ ቅዱስ ይህን የጥበብ ጸጋ እንዲለግሰን እንለምን፡፡ አሜን፡፡
591 views10:32