Get Mystery Box with random crypto!

የመኖር አካፋይ የመሞት ሲሶ መንገድ መሃል........ ክፍል ሀያ ሰባት (ሜሪ ፈለቀ) የሰው ል | ወግ ብቻ

የመኖር አካፋይ የመሞት ሲሶ መንገድ መሃል........ ክፍል ሀያ ሰባት
(ሜሪ ፈለቀ)

የሰው ልጅ ለውጥ የአንድ ጀምበር ክስተት አይሆንም። ወይ ተሸርፎ ተሸርፎ የተጋተው ልምድ እየቆየ ይለውጠዋል አልያም በህይወቱ ከባድ ክስተት እንደሚወዱትን ማጣት ያለ ንዝረት 360 ዲግሪ ይቀይረዋል። የአባቴን ገዳዮች ለመጥላት የአባቴ ሞት እና የእናቴ አይኔ ስር መደፈር በቂ ነበር። የበቀል ጥንስሴን ከዜሮ መቶ ለማድረስ ለቁጥር የሚታክት ጊዜ አባቴ የሞተበት ደጃችን ላይ ተመላልሼ ክስተቱን በጭንቅላቴ ስያለሁ!! አንድ ቀን ባልሳቅኩ ቁጥር፣ ልጅነቴን ሁሉ እኔና ወንድሜ እናትና አባት እንደሌለን ባሰብ ቁጥር ሁሉ አምርሬ ጠልቼ አምርሬ ላጠፋቸው ሰውነቴ ጥላቻ ረጭቷል።

ሴት ልጅ እርቃኗን የወንድ መዝናኛ ሆና የምታስገኘውን ገንዘብ እንደገቢ ከመቁጠሬ ከዓመታት በፊት የሴት ልጅ ገላ ሲቀል አይቼ ዘግንኖኝ ነበር። <እንዴት አይነት አስተዳደግ ብታድግ ነው?>ም ብዬ ፈርጄባታለሁ። ቀን በቀን በትንሽ በትንሹ ስጋተው ቀጭን ወገብ ሳይ ፖሉ ላይ ስትጥመለመል የሚስል ጭንቅላት ኖረኝ እና አረፈው።

ያኔ ታክሲ በር ላይ ተለጥፌ ፒያሳ ሜክሲኮ የምል ጊዜ ……. በጉልበቴ ተከበርኩ። ተራ አስከባሪውም ሹፌሩም ከዛን ቀን በፊት አይቶኝ በማያውቀው የክብር ዓይን አየኝ። ፀሃይ ሲያነደኝ ውዬ የማገኘው ገንዘብ ግን ኪዳንዬን እንደምፈልገው የሚያኖርልኝ አልነበረም። ያ ሰውዬ የሰጠኝን ቢዝነስ ካርድ ለማይቆጠር ያህል ጊዜ ካሸሁት በኋላ ደወልኩለት። ሰውየው ደላላ ነው። ሊያስቀጥረኝ ያጨልኝ ቦታ እንኳን ለእንደእኔ ዓይነቷ ከትንሽ ክፍለሀገር ለመጣች ሴት ቀርቶ የፈረንጅ ፊልም ስታይ ላደገች ከተሜም ቀላል አይመስለኝም። ከተማዋ ውስጥ እኔ ነኝ ያለ የመናዊ ሰውዬ ጠባቂ መሆን ነው። መጠበቁ ደግ ነበር። ሰውየው የጋዳፊ(ስለጋዳፊ ሳውቅ ነው የገባኝ ጉዳዩ) ታናሽ የሚሰራራው ወፈፌ ነው። ጠባቂዎቹ ሴቶች እንዲሆኑ ከመፈለጉ አንድ ደርዘን ሴት እንዲጠብቀው መፈለጉ ግራ ያጋባል። ብስራተ ገብርኤል ካለው ቤቱ ቦሌ ለመድረስ በአራት መኪና እና በ10 ሴት ጠባቂ በሁለት ወንድ አጃቢ መከበብ ጤንነት ነው?

የተገናኘን ቀን ዝርዝሩን ብዙም ሳይነግረኝ ሰውየው ቤት ይዞኝ ሄደ። የቤቱ ስፋትና ውበት ቤተመንግስት ራሱ እንደዚህ ይመስላል የሚል ምስል ጭንቅላቴ ውስጥ የለም። የአጥሩ በርጋ ብቻ ወንድ ሁለት ጠባቂዎች ሲኖሩ በተረፈው ሱፍ ኮት እና ሚኒ ጉርድ የለበሱ  በለበስኩት የመነቸከ ሸሚዝና ጅንስ ሱሪ የሚያሸማቅቁኝ የሚያማምሩ ሴቶች ሲቀባበሉ ብዙ ኮሪደር እና ክፍሎች አልፈን አንደኛው ቢሮ የሚመስል ክፍል አደረሱኝ። ሴቶቹ ምናልባት ከሁለቱ ውጪ ሀበሻ አይደሉም!! ሰውየው ፊቱ ከመንጣቱ የተነሳ የሰው ቆዳ ሳይሆን ነጭ ሸማ የመሰለ ፊት ያለው አረብ ነው። ጭንቅላቱ ላይ በቄንጥ የታሰረ ሻርፕ ነገር አድርጎ እንደወተት የነጣ ቀሚስ ለብሷል። ከደላላው ጋር በአረብኛ ሲነጋገሩ እንዳልወደደኝ ያስታውቅበታል። ከእግሬ እስከራሴ በማጣጣል እያየኝ ቁጣ የመሰለ ነገር ይንጣጣል። ደላላው ሽንጡን ገትሮ ይከራከራል። ሳይገባኝ አይኔን ከሰውየው ወደ ደላላው እያቁለጨለጭኩ ሳይ ከየት መጣ ያላልኩት የሆነ ጠባቂ መሰለኝ ከጀርባዬ ሳላስበ በእጁ ቆልፎ አንቆኝ ወደላይ አነሳኝ። እነርሱ ጭቅጭቃቸውን ቀጠሉ። ደመነፍሴን እየሆነ ያለው ሳይገባኝ በቀኝ እጄ ያነቀኝን እጁን ጠምዝዤ በግራ እጄ ፍሬውን አጎንኩት። እጁን ጠምዥዤ ወደፊት ስደፋው ነው ሆነ ብለው የፈጠሩት ድራማ መሆኑን ያወቅኩት። ሰውየው <ምንም አትል> አይነት ንቅናቄ ጭንቅላቱን ነቀነቀ።

እዚህ ድረስ ሰላም ነበር። እንድለካው ያመጡልኝን ልብስ ስለብሰው የለበስኩት ፓንት ሊታይ ትንሽ የቀረው ከመሆኑ ለፋሲካ የሚገዙትን በግ አዟዙረው እንደሚያዩት እየዞረኝ ሲገረምመኝ
«ምንድነው እሱ? ስራው ጥበቃ ነው አላልክም? ደግሞ ይሄን ብጣሽ ነገር አገልድሜ አንድ እርምጃ አልሄድም!! አልፈልግም ስራውን!» ብዬ ልብሱን እንድቀይር የወሰዱኝ ክፍል ሄጄ የራሴን ልብስ ስቀይር አሁንም እነርሱ እንደጭቅጭቅ ያለ ወሬ ሲያወሩ ይሰማኛል። ደላላው በኋላ ሲገባኝ ለሚከፈለው ጠርቀም ያለ ገንዘብ ነው ሽንጡን ገትሮ እንድቀጠር ሲከራከር የነበረው። ሰውየው ስራውን አልፈልግም በማለቴ ተናዶ መሆኑን በኋላ ሰማሁ። <ማን እንደሆንኩ አውቃለች? > ብሎ ነበር የደነፋው። ስንወጣ ደላላው ደሞዙን ሲነግረኝ ጠጅ እንደጠጣ ሰው ጉልበቴን ያዘኝ። ግን እንዲያውቅብኝ ስላልፈለግኩ መግደርደሬ እንዲታወቅልኝ

«የምሰራ ከሆነም ያን ቀሚስ አልለብስም። ሱሪ ከተደረገልኝ እሰራለሁ!! ደግሞ ቆይ ሴቶቹስ እግራቸውን ማንሳት ቢኖርባቸው በዛ ቀሚስ እንዴት ነው የሚሆኑት?»

«ሰውየው በሴት የመከበብ ልክፍት ስላለበት እንጂ አሁን ማን ይሙት አዲስአበባ ውስጥ እንዲህ ተከቦ የሚያስኬድ ስጋት ኖሮበት ነው? የሀብታም ነገር ብሩን የሚጥልበት ሲጨንቀው ነው።» አለኝ። ከቀናት በኋላ ሱሪ መልበስ እንደተፈቀደልኝ ነገረኝ እና ስራውን ጀመርኩ። ጀመርኩ እንደዋዛ አይደለም። ከሰውየው ጠባቂዎች ጋር ኢላማ ተፈትኜ…… መጀመሪያ ሰሞን በየሄደበት በር ጠባቂ ካደረገኝ በኋላ ….. ከሀገር ውጪ ሲወጣ ባዶ ቤት ክፍሎች ጠባቂ ከሆንኩ በኋላ ….. ከኪዳን ጋር የተሻለ ቤት ተከራይተን መኖር ከጀመርን በኋላ ……. የግል ትምህርት ቤት ካስገባሁት በኋላ …… የሆነ ጊዜ ደላላው ሲመጣ በር ጠባቂ መሆኔን ሲያይ

«አንቺ ከእነዚህ እሳት ሴቶች ጋር እየዋልሽ ዛሬም በር ላይ ነሽ? አትማሪም? ምንድነው እንዲህ ማካበድ? ይሄኔ ብታቀምሺው ስንት ሀገር አይተሽ ነበር! ያንቺ የተለየ ነው እንዴ ይሄን ያህል?» ሲለኝ እስከዛን ቀን ዙሪያዬ እየሆነ ያለውን አለማጤኔ ገባኝ። አትማሪም ወይ? አለኝ እንጂ ሴቶቹ ከእኔጋ ጊዜ ኖሯቸውም አያወሩ ቢኖራቸውም የእነርሱ ዓይነት አራዳ ስላልነበርኩ ትዝም አልላቸውም። በዛ ላይ ከሁለቱ ሀበሾች ውጪ በቋንቋም አልግባባም!! ደላላው ከሄደ በኋላ ነው ከእኔ ውጪ ሁሉም ሴቶች ባለመኪና የመሆናቸው ሚስጥር እኔ ቅርብ ስራ ጀማሪ መሆኔ ሳይሆን እነርሱ መቀመሳቸው መሆኑ የተገለጠልኝ። እስከዛን ቀን ድረስ ሴትነትን ወይም ድንግልናን አስቤው የማውቅ ባልሆንም ነገሩን አስቤው ዘገነነኝ። ሴትነትን ሳስብ ትዝ የሚለኝ መሬት ላይ ቀሚሷ ተገልቦ የተኛች እናቴ ናት!! ሴቶቹም ዘገነኑኝ!! ሴትነቴም ዘገነነኝ!! ለውጥ የልምድ ውጤት ነው አላልኳችሁም? ለዛን ሰዓት ከመኪናው እና ሴቶቹ ሲይዙ ከማያቸው ውድ ስልኮች እና ሲያደርጉ ከማያቸው ዘናጭ ቦርሳና ጫማዎች በላይ የከዳሁት ሴትነቴን ክብር ማስጠበቅ መረጥኩ!! በየሄደበት በር ላይ መቆሙን ቀጠልኩበት!!

አዲስ አበባ እንደአደግኩበት ክፍለሀገር በጉልበቴ ብቻ የምከበርበት ሀገር አለመሆኑን ከረፈደም ቢሆን አውቄያለሁ። ከኛ ሰፈር የአባቴ ገዳዮች ሰፈር እኩዮቼን አጅቤ ሄጄ ጠላቴን አደባይቼ ልምጣ ብዬ እንደማቅደው የስልጣን ሽልማታቸውን የሚያጣጥሙ ያባቴን ገዳዮች በር አንኳኩቼ እንደማልገድላቸው አውቄያለሁ። ሁሉም ነገር ከባድ እንደሆነ ያወቅኩት እንኳን እኔ ቀርቶ ገጠር ሲመጣ <ሚንስትር ሙሉሰው ዘመዴ ነው! እኛ ቤት ይመጣል> እያለ የሚበጠረቀው የካራቴ አሰልጣኛችን እንኳን የሚንስትሩ ቤት ሰማይ ይሁን ምድር ካለማወቁ ቤተሰቦቹ እንኳን ያለምክንያት የማያገኙት ሩቅ ሰው መሆኑን ስረዳ ነው። ከሀገሬ ስወጣ እገድላቸዋለሁ ብዬ ስም ዝርዝራቸውን የፃፍኳቸው እና ስማቸውን ማወቅ ሳልችል በምልክት ጭንቅላቴ ውስጥ የመዘገብኳቸው ሰዎች ዋና ዋናዎቹ እዚሁ አዲስአበባ ተሿሹመው ሲኖሩ የተቀሩት የት