Get Mystery Box with random crypto!

«መሸነፊያዬም መጀገኛዬም አንተ መሆንህን አታውቅም? ባንተ ሲመጡብኝ ነው እጅ የምሰጠውም አውሬ የም | ወግ ብቻ

«መሸነፊያዬም መጀገኛዬም አንተ መሆንህን አታውቅም? ባንተ ሲመጡብኝ ነው እጅ የምሰጠውም አውሬ የምሆነውም! ያን ታውቃለህ አይደል?»

«አውቃለሁ ሜል። ግን አሁንኮ ትልቅ ሰውዬ ነኝ!! ሚስትኮ ላገባ እየተሰናዳሁ ያለው ግብዳ ሰውዬ ነኝ! እስከመቼ ነው የምትጠብቂኝ? (ዞር ብዬ ያለፉትን ቀናት እንደማስታወስ ሳየው) ይሄ የተለየ situation ነው። እንዲህ ያለ አጋጣሚ ከተፈጠረማ በድዴም ቀርቼ እንደምትደርሺልኝ አውቃለሁ። ገብቶሻል ምን ማለት እንደፈለግኩ!! መቼ ነው አንቺ የራስሽ የሆነ ህይወት የሚኖርሽ? ለእኔ ብለሽ ፣ ለአባዬ ብለሽ ወይም ለእማዬ ብለሽ የማትኖሪው። ለሜላት ብለሽ የምትኖሪው ቀን መቼ ነው? (ይሄን ሲለኝ ስለእማዬ ለካ መንገር አለብኝ። ምን ብዬ ነው የምነግረው? የሞተችዋ እናታችን ከሞት ተነሳች! ነው የምለው?)  ደግሞ አባት ልሆንልሽ ነው!» ሲለኝ ስለእማዬ ያሰብኩት ጠፋብኝ። መኪናውን አቆምኩ።

«ሊንዳ እርጉዝ ናት? ስንት ወሯ ነው?» እያልኩት እሺ የአሁኑ እንባ ምን የሚሉት ነው? እንደትናንት በሚመስለኝ የቀናት ርዝመት ውስጥ እግሬ ላይ ተጠምጥሞ ትተሽኝ አትሂጂ ብሎ የሚያለቅስ ትንሽዬ ልጅ ነበርኮ!! አባቱ የሞተበት እናቱ ትታው የሄደች ቀንኮ <አባዬ ዳቦ ገዝቶ ሲመጣ ዳቦ በሻይ ነው የምበላው እንጀራ አልበላም!> ብሎ ያለቀሰ የአባቱ ሳጥን ውስጥ መቆለፍ ያልገባው ሚጢጢ ነበረ።

«ስድስት ወር ሆናት! ሴት ናት!» አለኝ እንደመኩራትም እያደረገው። ዝም አልኩ!! ዝምታዬ ውስጥ ግን ብዙ ጩኸት ነበረ። ደስ የሚል ከዛ ደግሞ የሚከፋ ስሜት እንዴት ተብሎ ይብራራል? የእኔ ኪዳን ፣ ልጄ ፣ ታናሼ ፣ ዓለሜ ፣ ብቸኛ የዓይን ማረፊያዬ አደገልኝ!! እሱ አድጎ ልጅ ሊያሳድግ ነው!! እንዲኖረው የተመኘሁለትን እና የተመኘውን ሁሉ አንድም ሳይጎድልበት አግኝቷል። በህይወቴ ትልቁ ድሌ እና ስኬቴ እኮ እሱ ነው!! ከዛ ግን ለምን የመከፋት ስሜት ተሰማኝ? ለእሱ ደስ አለኝ ለእኔ ግን ከፋኝ። የሆነ እዝህች ምድር ላይ ለመኖር የመጣሁበትን ዓላማ የጨረስኩ ፤ የምኖርለት ምክንያት ምንም ያልቀረኝ ፤ ከዚህ በኋላ እኔ የማላስፈልገው ፤ የራቀኝ ዓይነት ስሜት ተሰማኝ። ይሄን ግን ለእርሱ ልነግረው አልፈለግኩም። ደስታው ትንሽ እንኳን እንዲደበዝዝበት አልፈልግም!! አቅፌው እንባዬን እየጠረግኩ ደስ እንዳለኝ ነግሬው መኪናዬን መንዳት ጀመርኩ። ሆቴሉ ደውለን ሪሴፕሽን እቃውን እንዲያስቀምጡልን አድርገን። የሚከፋፈለውን ከፍለን ሻንጣውን ወሰድን። ለአፍታም ቢሆን ከእኔ እይታ ዘወር እንዲል ስላልፈለግኩ ሆቴል ከመያዛችን በፊት ጎንጥን ለማየት ወደሆስፒታል ነዳሁ።

«የእኔ ኪዳን? አውቃለሁ ታጥበህ ልብስ ለመቀየር እንደቸኩልክ!! ለትንሽ ደቂቃ ሆስፒታል የሆነ ሰው ጠይቀን እንመለስ እና ደግሞም የምነግርህ ትልቅ ነገር አለ።» አልኩት በመንገዳችን።

«ምንድነው እሱ? የምነግርህ ትልቅ ነገር ስትዪ ሁሌም የሚከተለው ደስ የማይል ነው!! ምንድነው እሱ? ምን ልታደርጊ ነው? ደህና ነሽ አንቺኣ?»

«ኸረ ጭራሽ እንደሱ አይነት ነገር አይደለም!! እንደውም ደስ የሚል ነው መሰለኝ! ቢያንስ በግማሽ!»

ጎንጥ የተኛበት ክፍል ስንገባ ትንፋሹን ሰብስቦ የሆነ መርዶ እየጠበቀ ያለ ይመስል ነበር። ከሆዱ ድረስ ትንፋሹን ስቦ በረጅሙ የመገላገል ዓይነት ተነፈሰ እና ፈገግ አለ።

«ነፍሴን እኮ አወክሻት ዓለሜ? ከቤቱ ወጣች ካሉኝ ቆየ!! ስትዘገዪ ከመንገድ ምን አገኘሽ ብዬ ነፍሴ ከስጋዬ ልትለይ?» አለ የመጨረሻውን ዓረፍተ ነገር መልስ ባልጠበቀ ጥያቄ ዓይነት አስረዝሞ!! ማለት የፈለግኩት የነበረው <ልቤንኮ በረደኝ! እጄን ያዘኝ! ጦሽ ብዬ ላልቅስና! ኸረ በመድሃንያለም ነፍሴን አታስጨንቂያት! እያልክ አባብለኝ!> ነው። ያልኩት ግን «የኪዳንን ሻንጣ ልናመጣ በዛው ሄድን! ይቅርታ ቢያንስ መልዕክት እንኳን መላክ ነበረብኝ!»

ኪዳን አንዴ እኔን አንዴ እሱን <እየሆነ ያለውን ነገር አንዳችሁ ትነግሩኝ?> በሚል አስተያየት ያየናል።


        .......... አልጨረስንም .......... 

@wegoch
@wegoch
@paappii