Get Mystery Box with random crypto!

አቅራቢያው ስደርስ የጋዜጠኛው ቡድን እኩል ደረሰ። ስልኬ ላይ የማየውን እቤት ያሉት ካሜራዎች እይታ | ወግ ብቻ

አቅራቢያው ስደርስ የጋዜጠኛው ቡድን እኩል ደረሰ። ስልኬ ላይ የማየውን እቤት ያሉት ካሜራዎች እይታ አቀበልኳቸው። እነርሱ በኮምፒውተር ፣ በተለያዩ ገመዶች ፣ ማይክራፎኖች  እና ሌሎች ነገሮች በሞላው የመኪናቸው ጀርባ የሚሰካካውን ሰካክተው ዝግጁ መሆናቸውን ሲነግሩኝ መኪናችንን የአጥር በሩጋ አስጠግተን አቁመን እኔ እና አንድ ማይክራፎን የያዘ ጋዜጠኛ እና ሌሎች ሁለት ካሜራ እና ካሜራ ረዳት ወርደን ስንጠጋ ጠባቂው የያዘውን መሳሪያ ወደፊት አስቀድሞ ወደእኛ ቀረበ።

«ጋዜጠኞች ነን!! ላይቭ ነው! አቶ ደሳለኝ ስለምርጫው ትንሽ እንዲሉልን ነው!» አለው አብሮኝ ያለው ጋዜጠኛ። ጠባቂው ምኑም አልተመቸውም። ለሌላኛው ጠባቂ መልዕክቱን ለአቶ ደሳለኝ እንዲያስተላልፍ ጮክ ብሎ ተናግሮ እኛን እንድንጠብቅ አዘዘን። ሌላኛው ጠባቂ ከደቂቃዎች በኋላ አቶ ደሳለኝን አስከትሎ ብቅ አለ።

«እኔ ከምንም ዓይነት ጋዜጠኛ ጋር ቀጠሮ አልያዝኩም!! ምን አይነት ጣጣ ነው! ሰው ማረፍ አይችልም? ደግሞ ይሄን ቤት ማን አሳያችሁ?» እያለ እየተነጫነጨ ቀና ሲል ከእኔ ጋር ተያየን። ሊቀየር ሲዳዳው አብሮኝ ያለው ጋዜጠኛ ለካሜራ ማኑ እንዲጀምር ምልክት ሰጠው። ቀጥሎም የቴሌቭዥን ጣቢያውን ፈቃድ እያቀበለው

« አቶ ደሳለኝ ላይቭ የኢትዮጵያ ህዝብ እየተከታተሎት ነው። በዚህ ምርጫ ለየት ባለ የምርጫ ቅስቀሳዎ የህዝብን ቀልብ የሳቡ ይመስላል። ወደ ውስጥ ገብተን አንድ ሁለት ነገር ቢሉን? » አለው። ግራ ተጋባ እና እየተወነባበደ ሳቅ አይሉት ስላቅ ያልለየለት ፈገግታ ፈገግ እያለ ወደውስጥ ጋበዘን። ይሄኔ ፅፌ አዘጋጅቼው የነበረውን መልዕክት ኪዳን ያለበትን ክፍል ጨምሮ ካሜራ የተገጠመባቸውን ክፍሎች ምስል ከሚያሳየው ምስልጋ ላኩለት። ስልኩ መልዕክት መቀበሉን ቢሰማም አላየውም።

«አቶ ደሳለኝ መልዕክቱ የሚያስፈልጎ መልዕክት ይመስለኛል።» አልኩት ጠጋ ብዬው። በጥፍሮቹ ቢቦጫጭረኝ ደስ እንደሚለው እያስታወቀበት የግዱን ፈገግ ብሎ ወደሳሎን እየመራን መልዕክቱን አነበበው።

« ቴሌቭዥንህን ክፈተው ካላመንከኝ ላይቭ ነህ!! ኪዳን ያለበት ክፍል ጨምሮ ኮሪደርህ እና ሳሎንህ በድብቅ ካሜራ እይታ ውስጥ ነው። የምስሉ መዳረሻ መቼም ይገባሃል የኢትዮጵያ ህዝብ አይን ነው። አርፈህ በቀጣፊ ምላስህ ለኢትዮጵያ ህዝብ ያለህን ፍቅር እና ብትመረጥ የማታደርገውን የውሸት ቃልህን ላይቭ ዘብዝበህ የምርጫ ቅስቀሳህን ብታደርግ ይሻልሃል ወይስ ዜናውን ከምርጫ ቅስቀሳ ወደአፈና ወንጀል ብንቀይረው? ምርጫው ያንተ ነው!! ከጋዜጠኞቹ ጋር እያወራህ ወንድሜን ሳሎን አስመጣልኝ። ምንም ግርግር ሳንፈጥር ከጋዜጠኞቹ ቀደም ብዬ ውልቅ ብዬ እወጣልሃለሁ!! አይ ካልክ ግን እዚሁ ላይቭ ወንድሜን እንዳገትከው ከነምስሉ ለጋዜጠኛው ሹክ እለዋለሁ። እዛው ላይቭ ጮማ ዜና አይመስልህም? በዛ ላይ ያን የቪዲዮ ቅጂ እመርቅላቸዋለሁ።!!» እያነበበ ጋዜጠኛው ደጋግሞ ስሙን ይጠራዋል። አልሰማውም!! እንደመባነን ብሎ

«እ እ!! የሆነ ትንሽ አስቸኳይ መልዕክት ደርሶኝኮ እ!!» ተንተባተበ።
«አዝናለሁ መጥፎ ዜና ነው?» አለው ጋዜጠኛው።
«አይ እንደው ትንሽ ነገር ነው። እኔ የምልህ እና አሁን ይሄም ላይቭ እየተላለፈ ነው?» ብሎ የቴሌቭዥኑን ሪሞት አንስቶ እየከፈተ  የሆነች ተንኮል ያለበት አስተያየት ወደእኔ አየ። ልቤ በመጠኑም ቢሆን መደለቅ ጀመረ። ደቂቃ እንኳን ዝንፍ ያለ ክፍተት ከተፈጠረ ሰውየው እዛ ያለነውን በሙሉ ጭጭ አድርጎ የቀደመ እቅዱን ለማሳካት የጋዜጠኞቹ ብዛትም ማንነትም የሚያሳስበው ሰው አይደለም። ጋዜጠኛው ነውም አይደለምም ሳይለው (ምክንያቱም እስከዛ ደቂቃ ድረስ ላይቭ አልነበረም) ቀጠለ። በቴሌቭዥኑ ዜና የምታቀርበዋ ሴት ስለአቶ ደሳለኝ አውርታ ስታበቃ ባልደረባዋን ጋበዘችው። ጋዜጠኛው ጥያቄውን ቀጠለ። መልሱም መላ ቅጡ የጠፋበት ወሬ ከመሆኑ በተጨማሪ በተቀመጠበት ላብ ያጠምቀው ጀመር። እየተንተባተበ ጥቂት እንዳወራ ሚስትየው ብቅ እንዳለች እየሆነ ባለው ነገር ግራ ተጋብታ ፍሬን ያዘች። በሚቀባጥረው ወሬ መሃል ወደሚስቱ ዞሮ «እስቲ ኪዳንን የሚጠጣ ውሃ እንዲያመጣ አድርጊልኝ! ቡናም ሻይም ሳልላችሁ በሞቴ ለእናንተስ ምን ይምጣላችሁ?» አለው ጋዜጠኛውን! ጋዜጠኛው ቀጥታ በዜና መሃል እየተላለፈ ያለ ፕሮግራም ላይ መዘለባበዱ እያናደደው ግን በጨዋ ደንብ ቀጠለ።

«በእውነቱ አቶ ደሳለኝ በዚህ አጋጣሚ ሳይዘጋጁ የመጣንቦት ቢሆንም እንግዳ ተቀባይነትዎ እና ልግስናዎ አልተለየንም። ከልብ እናመሰግናለን!! ባልደረባዬ የቀሩትን ዜናዎች ለማቅረብ እየተጠባበቀች ስለሆነ ለህዝቤ ማለት አለብኝ የሚሉት መልዕክት ካለ እድሉን ልስጦት!! »

ጋዜጠኛውን በቅጡ የሰማው አይመስልም። ሚስቱ እንደጅብራ መገተሯ አሳስቦት በግንባሩ መልዕክት ሊያስተላልፍላት እየሞከረ ነው። እያመነታች ከሳሎኑ ስትወጣ ልቤ መደለቋን ቀጠለች። እሱም ለዚህ የፈረደበት የኢትዮጵያ ህዝብ ላቡንና ወሬውን በቲቪ ማስተላለፉን ቀጠለ። ኪዳን የመጠጥ ውሃ የሞላው ብርጭቆ ይዙ ወደሳሎን ብቅ ሲል ልቤ ወደቦታዋ ተመለሰች። እዚህ ድረስ ያለውን በድል ተወጥቼዋለሁ!!


                       ..........  አልጨረስንም!! .........

@wegoch
@wegoch
@paappii