Get Mystery Box with random crypto!

«ከትናንት እስከአሁን በ24 ሰዓታት ያልተፈጠረ ነገር የለም ብልሽ ይቀላል። አንድ ቀን ሳይሆን አን | ወግ ብቻ

«ከትናንት እስከአሁን በ24 ሰዓታት ያልተፈጠረ ነገር የለም ብልሽ ይቀላል። አንድ ቀን ሳይሆን አንድ ዓመት የሆነ ነው የሚመስለው። ኪዳንን ላስለቅቅ በነበረ ሂደት የተኩስ ልውውጥ ነበር። በዛ መሃል ሲመስለኝ የሽጉጥ ተውሱ ትውስታዬን የወሰደብኝ ተኩስ አደጋን አስታወሰ እና ትውስታዬን ቀሰቀሰው። አላውቅም የተከሰተውን ብቻ አስታወስኩ ሁሉንም!!»

«wait a minute …. It’s too much information eko (ጭንቅላቷን የሆነ ከደነዘዘበት እንደማባነን፣ እንደማንቃት ያለ እየወዘወዘች) እሺ የትውስታ መሄድ መምጣቱ ይቆየኝ! ኪዳን safe ሆነ? ሆ! አይገርምሽም?  I felt it ደግሞ እኮ……. Something was off » አለች አሁንም ዓይኗ እላዬ ላይ መርመስመሱን ሳታቆም!

«አልሆነም!! አሁንም እነሱጋ ነው ለዛ ነው እርዳታሽን የምፈልገው!!»
«ምንም እየገባኝ አይደለም! ተኩስ ነበር አላልሽኝም? አንቺ ታዲያ እንዴት እዚህ ተገኘሽ?»
«እሙዬ እመኚኝ ስናወራ ውለን ብናድር አይገባሽም!! ጎንጥ ከነርሱ አንዱ ነው። እኔ በሱ ምክንያት ነው እዚህ ያለሁት! እሱ ደግሞ ሆስፒታል ነው ተመትቶ!! (ይበልጥ ሲዞርባት አየሁ) ሌላ ቀን እነግርሻለሁ እሱን!!»

«ጎንጤ ጥጋቡ የእነሱ? እኮ ዘበኛሽ ሰላይ? እመኚኝ አመትም ብትነግሪኝ ይሄ ነገር አይገባኝም!!»
«እኔም ብዙ አልገባኝም ኪዳኔን ቅድሚያ ልስጥ ብዬ እንጂ!!»
«እሺ ምንድነው እንዳደርግልሽ የምትፈልጊው?»
«እናንተ ቴሌቭዥን ጣቢያ አሁን በምርጫው ዙሪያ እየሰራ ያለ ጋዜጠኛ እንዲተባበረኝ እንድታደርጊልኝ እፈልጋለሁ። እና ደግሞ ዛሬ የሁለት ሰዓቱን ዜና የሚያነበውን ሰው!»

«እሺ አገኘሁልሽ! ምን አስበሽ ነው?» አለች ጭራሽ ግራ ተጋብታ!!
«የምርጫው ዜና ሲተላለፍ አቶ ደሳለኝም አንዱ እጩ ተወዳዳሪ እንደመሆናቸው አንዱ ጋዜጠኛችሁ እቤታቸው ተገኝተው ላይቭ አጭር ቃለመጠይቅ ያደርጉላቸዋል። የምታደርጉትን አድርጉ ስትፈልጉ ሙሉውን ቃለመጠይቅ ከዜና በኋላ ያቅርቡት። እኔ የምፈልገው ከእኔጋ በተቀናጀ ሰዓት ላይቭ መግባታቸውን ነው።»

«እየገባኝ አይደለም!! የማስበውን እያሰብሽ ከሆነ በጣም ሪስክ አለው!»
«አውቃለሁ ግን ከዚህ የተሻለ ደም ሳይፈስ፣ ህይወት ሳይጠፋ ኪዳንን ላገኝ የምችልበት ምንም አማራጭ አልታየኝም!! ብቻ አንቺ ይሄን ማድረግ ትችዪ እንደው ንገሪኝ?»

«ወይ ጉድ! እስኪ ስልክሽን ስጪኝ ልደዋውል!!»

«እሺ በስልኬ ግን ምንም አይነት መረጃ እንዳትቀያየሪ! ከእኔ ጋር እንዲገናኑ ብቻ በሆነ መላ ንገሪያቸው። ምናልባት አላውቅም!! ስልኬን ሲሰጡኝ ውስጡ የነበረ ብዙ ነገር አፅድተው ነው የሰጡኝ። ሁሉንም ሶሻል ሚዲያዎቼን አዘግተውታል። መቼም የማላስታውስ ነበር የመሰላቸው መሰለኝ ወይም ከማስታወሴ በፊት እንደሚደፉኝ እርግጠኞች ነበሩ።»

«እንደዛ ከሆነ መደወሉ በራሱ ሪስክ አለው!! (ዘወር ብላ ወደ ጠባቂው) ሼባው? ዛሬ ለሚስትህ ዓመትበዓል ማስመሰል አላማረህም? ስልክህን ለ5 ደቂቃ ልደውልበት ?» አለችው። የጠባቂውን ስልክ ተቀብላ ሁለት ቦታ ስልክ ደዋወለች። ስልኮቹንም ለእኔ እንድመዘግብ ነገረችኝ። እኔ በምፈልገው መንገድ አዘጋጀችልኝ። መልሳ ለጠባቂው ከሰጠኋት ብር ጋር ስልኩን እየሰጠችው

«ሳመኝኮ!» የሚለው ቃል አፌን አምልጦ ሲወጣ እኔው ራሴ ስሰማው እና እሷ ጆሮ ጠልቆ ሽው ብላ ዞራ ስታፈጥብኝ አንድ ቅፅበት ነው።

«ጎንጥ! ከንፈሬን አይደለም ደግሞ እጄን ነው! እዚህጋ! » ብያት የሳመኝን እጄን እንደሌላ ሰው ባዕድ እጅ ሳየው አይታ

«እርፍ መጃጃል!! እጅሽን ስሞሽ ድንግልናዋን ዛሬ እንደሰጠች ልጃገረድ እንዲህ የተሽኮረመምሽ ሌላ ነገር ቢያደርግሽ ክንፍ አውጥተሽ ልትበሪ ነው?» ብላ መሳሜን ስላቀለለችብኝ ተናደድኩ። እንዲህ ያለ መሳም ተስማ ባታውቅ ነው ያልገባት። ወዲያው ቀጥላ  «እንዴ ደግሞ ቆይ አሁን ከደቂቃዎች በፊት የእነርሱ ወገን ነው አላልሽኝም? አንቺ ሴት ዛሬ ግራ ያልተጋባ ምንም ወሬ ያለሽ አልመሰለኝም!»


«እንዳልሽው ነው ሁሉም ነገር ግራ የተጋባ ነው!! እጄን የሳመኝ ግን ግራ አያጋባም ሃሃሃሃሃሃ ኩልልል ብሎ ጥርት ያለ ነው።» ብያት ዝርዝሩን ከሰሞኑ መጥቼ ልነግራት ተስማምተን ተለያየን።

ተመልሼ ወደከተማ እየሄድኩ ተናኜጋ ደውዬ የተወሰነ ጥሬ ብር እና ለእንዲህ አይነት ጊዜ ለመጠቀም ገዝቼ አስቀምጫቸው ከነበሩ ሲሞች አንዱን እንድታመጣ ቦታውን ነገርኳት። በመንገዴ አዲስ የስልክ ቀፎ ገዛሁ። ዳዊትጋ ስልክ ደውዬ መኪናዬ ስለተበላሸች አሁኑኑ የእርሱን እንዲያውሰኝ ስጠይቀው በዛ ጭንቅንቅ መንገድ ነድቶ ሳይሆን በአየር ላይ በሮ በሚመስል ፍጥነት ያልኩት ቦታ ደረሰ። መኪናዋን ልነዳ ከተቀመጥኩ በኋላ ምንም እንኳን ሁሉም ትውስታዬ ቢመለስ ለሰከንዶች መንዳት መቻሌን እርግጠኛ አልሆንኩም ነበር። ወይም ፍርሃት ተሰምቶኝ ነበር።

ሁሉንም ነገር ባቀድኩት መሰረት ማስተካከሌን ለመቶኛ ጊዜ ካረጋገጥኩ በኋላ መፀለይ አሰብኩ። ሰዓቱ ገና ስለነበር የቀረበኝ ቤተክርስቲያን ገባሁ እና በሩ አካባቢ ቆምኩ። ከዛ ግራ ተጋባሁ!!! ላለፈው በደሌ ሁሉ አንድም ቀን መጥቼ ንሰሃ አልገባሁም!! በደም የተነከረ እጄን ወደ እርሱ መዘርጋት ድፍረትም ሆነብኝ!! ከዛ ደግሞ ያለፈውን ሁ,ለት ወር ከምናምንኮ ፀልዬ ነበር!! ሰምቶኝ ይሆን ወይስ አያውቀኝ ይሆን? ወይስ ባኮረፈ ፊቱ ነው ሲያየኝ የነበረው? ደግሞ መልሼ ከሰማኝ ይስማኝ ብዬ መፀለይ ጀመርኩ።

«አምላክ ሆይ ታውቀኛለህ ብዬ አስባለሁ። ካላወቅከኝ ሜላት ነኝ። ያለፈውን ሀጥያቴን ሁሉ ብናዘዝ መሽቶ ይነጋል። ከዛ በፊት ግን ያንተን እርዳታ እሻለሁ ተለመነኝ!! አሁንም የምሰራው ባንተ ዘንድ ልክ ይሆን ስህተት አላውቅም! ግን የተሻለ የመጨረሻ አማራጭ የምለውን ነው የመረጥኩት። እኔም ራሴ የድሮዋን ሜላት መሆን አልፈልግም! አንተም እንደማትወዳት ነው የማስበው!! ያለፈውን ሁሉ ማረኝ እና ለእኔ ስትል ሳይሆን ለወንድሜ ስትል፣ ለዛች ደጅህ ለማትጠፋ ምስኪን እናቴ ስትል ….. ወንድሜን ይዤው እንድመለስ እርዳኝ!! እባክህ እ? ከፈለግክ አትማረኝ! ከፈለግክም ቅጣኝ ግን በወንድሜ አትቅጣኝ!! እ? » የሆነ ከሰማይ <እሺ> የሚል ድምፅ እሰማ ይመስል አንጋጥጬ ቆየሁ!!

መኪናዬ ውስጥ ገብቼ ኪዳን ወዳለበት ቦታ መንዳት ጀመርኩ። ትናንት ከነበረበት ቤት ቀይረውታል። ከምሽቱ 3 ሰዓት የሚፈልገውን ይዤለት እንደምመጣ ስለነገርኩት እኔን ለመጠበቅ በጊዜ ከሚስትየው ጋር ወደዛው መሄዳቸውን አረጋግጫለሁ። የእሱ እቅድ ያው እንደተለመደው የራሱን ሰዎች እና መኪና ልኮ ይዘውኝ ልሄዱ ነው። እኔ ቀድሜ እዛው እንደምደርስ የሚጠረጥርበት ምንም ፍንጭ የለውም። በገዛሁት ስልክ እቤቱ ውስጥ የተጠመዱትን ካሜራዎች መቆጣጠር እችላለሁ። ሳሎኑን በሁለት አንግል፣ ኮሪደሩን እና ኪዳን ያለበትን ክፍል። ኪዳን አልጋው ላይ ኩርምት ብሎ ከመጋደሙ ውጪ ምኑም ታግቶ ያለ አይመስልም። ደጁ ላይ ጠብደል ጠባቂ ቆሟል። ለአፍታ ጎንጥን አሰብኩ> አሁን በዚህ ውጥንቅጥ ውስጥ ሆኜ የእሱን አሳሳም ማሰብ ነበረብኝ? አስቤስ እጄን መሳም ነበረብኝ?