Get Mystery Box with random crypto!

«በአምላክዎት! ግን ሀሳቤን አንስቻለሁ!! ከዚህ ወድያ የእርሶ እርዳታ አያሻኝም!» አለ ሁኔታው ን | ወግ ብቻ

«በአምላክዎት! ግን ሀሳቤን አንስቻለሁ!! ከዚህ ወድያ የእርሶ እርዳታ አያሻኝም!» አለ ሁኔታው ንቀት ወይ ፅያፌ በሚመስል ሁኔታ እየጎፈላ !! የተሰማኝ ስሜት ልሰጠው የነበረውን ኩላሊት አልፈልግም የተባልኩ ሳይሆን ሊሰጠኝ የነበረ ኩላሊት ተከልክዬ ሞቴ የፈጠነ አይነት ነገር ነበር። ምክንያቱን ደጋግሜ ብጠይቀውም መልሱ

«ራሴን እንዳብራራ አያስገድዱኝ!! ሌላ ሰው ተገኝቷል!» ብቻ ነው። የሆነ የማላውቀው ተስፋ ልበለው ደስታ አላውቅም የተነነ! የሆነ ነገሬን የቀማኝ መሰለኝ። ያበሳጨኝ ደግሞ ንግግሩ ትህትና እንኳን ያልነበረው መሆኑ ነው። የሆነ በድክመቴ ያገኘን ነገር መሰለኝ።

«ድሮምኮ የሰው ልጅ ያለቦታው ክብር ሲሰጡት ሽቅብ ካልሸናሁ ይላል።» አልኩት ብስጭት እያልኩ
«እትዬ ይልቅ እላፊ አንነጋገር!! ስራዬን መልቀቅ ስለምሻ ሌላ ዘበኛ ቢፈልጉ ጥሩ ነው!» ሲለኝ የተናደድኩበት ምክንያት የቱ እንደሆነ ሳይገባኝ ጨስኩ!

«ለአንድ አመት ነው ልትሰራ የፈረምከው!! ኮንትራትህን ሳትጨርስ ወዴትም አትሄድም! ሞክረኝና ታያታለህ!» ብዬው ገባው። በነጋታው ለራሴ ራሱ በማይገባኝ ምክንያት ልጁ ደህና መሆኗን ማወቅ ፈለግኩ። አላውቅም ብቻ እጇን ይዤ <አይዞሽ> ማለት አማረኝ። ምናልባት እሙ እንዳለችው የከደንኩት እናት የመሆን ስሜት ይኖር ይሆናል። እልሄን ውጬ ልጁን ላያት እንደምፈልግ ስነግረው።

«ይቅርታ ያድርጉልኝ እትዬ ለጊዜው ከቤተሰብ ውጪ ማንም እንዲያያት አልፈቅድም!! በሌላ አይዩብኝ ልነግሮት በማልችለው ምክንያት ነው!! አለኝ። የፈረደባት እመቤት ጋር ሄጄ

«ይሄ የማይረባ! ሌላ ሰው ስለተገኘ አያስፈልግም አይለኝም? ቱ! » እያልኩ ስደነፋ እንባዋ እስኪፈስ እየሳቀች

«እንዲህ ያበሳጨሽ ለምን ኩላሊቴ አልወጣም ነው ወይስ ለምን እሱ እንደሌሎች በዙሪያሽ ያሉ ሰዎች እቴጌ እመቤቴ አላለኝም አልተሽቆጠቆጠልኝም ነው? ይሄ ሰውዬማ ከገባ ጀምሮ ነርቭሽን ነክቶታል።»

«ባክሽን አንቺ ደግሞ! ጭራሽ ስራዬን እለቃለሁ ይበለኝ?» እኔ እበሳጫለሁ እሷ ትስቃለች። «ምኑ ነው አሁን ይሄ የሚያስቀው?»

«ለማንም ሰውኮ እንዲህ ቦታ ሰጥተሽ አታውቂም! ያውም ለዘበኛሽ? ጥጋቡ ነው የሚያንተከትክሽ ወይስ ሌላ ነገር አለ?» አለችኝ መሳቋን ሳታቆም። ከዛን ቀን በኋላ ስለጎንጥ ስናወራ < ጎንጤ ጥጋቡ> ነበር የምትለው።

ከቀናት በኋላ እሙ እንዳለችው የመንተክተኬ ምክንያቱ አልገባ ሲለኝ። ስራውን መልቀቅ እንደሚችል ሌላ ዘበኛ እንዳገኘው ስነግረው ደግሞ

«ሀሳቤን አንስቻለሁ! ኮንትራቴን ሳልጨርስ ወየትም ፍንክች አልልም» ብሎ አናቴን በብስጭት አዞሮው።

«እኔ ነኝና ሜላት! ሰውዬ ስትፈልግ እወጣለሁ ስትፈልግ እገባለሁ እያልክ እንደፈለግክ ሀሳብህን የምታነሳ የምትጥልበት የሰፈርህ ጠጅ ቤት አይደለም ይሄ! የቀጠርኩህ እኔ ነኝ! ስፈልግ ደግሞ በቃኝ ብዬ የማባርርህም እኔ ነኝ! ከነገ ጀምሮ ላይህ አልፈልግም!»

«ተናገርኩኮ ፍርማዬን ሳልጨርስ አልሄድም!» ብሎ እያወራሁት ትቶኝ ሌላ ስራ መስራቱን ቀጠለ።

አሁን ሲመስለኝ ያልጨረሰው ስራ ስለነበረ ነው የቆየው። ከዛ ቀን በኋላ የሰላም ቃላት ተለዋውጠን አናውቅም ነበር። አሁን ልለው የነበረው። <ለልጅህ ስልኮ እዛ አልጋ ላይ ተኝቼ ልደነዝዝ ዝግጁ ነበርኩ። ያ እንኳን ለጠላቶቼ ከመስራት አላገደህም!> ልለው ነበር። ይቅር አልኩት እንጂ አልረሳሁትም።

                      ***********


ያቀበልኩትን ስልኩን ባልተመታበት ጎን እጁ እየነካካ ያልኩትን እንዳልሰማ ዝም ብሎ አልፎ!!
«ማንም ሰው እንዳልተከተለሽ እርግጠኛ ሆነሽ እዚህ ቦታ ሂጂ! የምትፈልጊውን ንገሪው።» ብሎ የምንገናኝበትን አድራሻ ሰውየው የሚለብሰው ልብስ እና ኮፍያ ቀለም። የምንግባባበት ኮድ ፣ የምንገናኝበትን ሰዓት እና የሰውየውን ፎቶ በጭንቅላቴ መያዝ እስክችል አስደጋገመኝ።

«እሺ ግን አንተ እርግጠኛ ነህ ምንም አትሆንም?»

«አታስቢ! ለጊዜው እኔን ለማጥቃት ሆስፒታል ድረስ የሚያስመጣ ምክንያት ያለው ጠላት የለኝም!» አለ እንድሄድ መውጫውን እየጠቆመኝ። ተነሳሁ ግን እግሬ አልተራመደም! ቆሜ ግራ በገባው ስሜት ዘቅዝቄ እያየሁት ቆየሁ። እጄን በሚይዘኝ አያያዙ ያዘኝ እና

« ድንገት ካንቺ አቅም በላይ የሆነ ነገር ቢፈጠር ቢያንስ ምንም ምርጫ ከጠፋሽ የምትደውይለት የመጀመሪያ ሰው እንደሆንኩ ቃል ጊቢልኝ!» አለኝ

«ብደውልልህስ? ቀና ማለት እንኳን የማትችል ሰው ምን እንድታደርግ ነው?»
«ብቻ ደውይልኝ! ምልክት ስጭኝ! ያን እንደምታደርጊ ቃልሽን ስጭኝ!!» እያለኝ ስልኩን ወደ ስልኬ ደወለ። «ስልክሽ ፊት ለፊት የኔ ቁጥር ይኑር!»

«እሺ በራሴ የማልወጣው ነገር ከገጠመኝ እደውላለሁ።» አልኩት እጄን አልለቀቀኝም። ላስለቅቀውም አልቸኮልኩም። በእጁ የአውራ ጣት እንደመደባበስ ካደረገው በኋላ አንስቶ ወደ ከንፈሩ አስጠጋው። የእጄን አይበሉባ ሳይሆን ገልብጦ መዳፌን የውስጥ እጄን መሃሉን በከንፈሩ በስሱ ሳመው። ሳመው ወይ ዳሰሰው ወይ ተጫነው። የሆነ ነገር …….. የእጅ ውስጥ ተስሞ ሰው እንዲህ እንደመስከርም እንደመጦዝም ያለ ስሜት ይሰማዋል?

«…. ተደናበርኩልሽ ጥይት እንደሳተው!» ያለው ዘፋኙ እንዲህ ተሰምቶት ነው የሚሆነው።

    .............. አልጨረስንም ..............

@wegoch
@wegoch
@paappii