አዲሱ የፋይናንስ ስርዓት ወደ ሀገር ውስጥ በሚገቡ የውጭ ባንክ ተወካዮች ዘንድ ቅሬታን ፈጠረ
በኢትዮጵያ የሚገኙ የውጭ ባንኮች ተወካዮች የውጭ ዜጎች ወደ ባንክ ዘርፉ እንዲገቡ የሚጠበቀውን አዲሱን የፋይናንስ ኮድ በቅርበት እየመረመሩ ይገኛሉ። ተወካዮቹ ለሚኒስትሮች ምክር ቤት ቀርቦ ተግባራዊ እንዲሆን በፀደቀው አዲሱ ፖሊሲ ላይ ቅሬታ እንዳላቸው ካፒታል ጋዜጣ አስነብቧል።
ፖሊሲው ዓለም አቀፍ የፋይናንስ ዘርፍ ተጫዋቾች እንደጠበቁት አይደለም ያሉ ሲሆን ይህም ብዙ እጩ ተወዳዳሪዎች ወደ ገበያው ለመግባት ፍላጎታቸው እንዲቀንስ ያደርጋል” ሲሉ ስማቸው እንዳይገለጽ የጠየቁ የውጭ ባንክ ተወካይ ለካፒታል ተናግሯል። ተወካዩ አክለውም የውጭ ዜጎች በአስተዳደርና በውሳኔ አሰጣጥ ሂደቶች ላይ የሚኖራቸውን ሥልጣን መገደብ ተገቢ አይደለም ብለዋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ መቀመጫውን በዩናይትድ ኪንግደም ያደረገው የቻርተርድ አካውንታንቶች እና የአስተዳደር አማካሪዎች ድርጅት ዋና ስራ አስፈፃሚ የሆኑት አቶ ጌታቸው በሻወርድ መንግስት ዘርፉን ሙሉ በሙሉ መክፈት የለበትም ባይ ናቸው። የውጪ ባንኮች ድርሻቸው ካልተወሰነ የአገር ውስጥ ባንኮችን ተወዳዳሪነት ያጠፋሉ፤ ኢኮኖሚውም ሙሉ በሙሉ በውጭ ዜጎች ቁጥጥር ስር ሊወድቅ ይችላል ሲሉ ስጋታቸውን ለካፒታል ገልጸዋል። አቶ ጌታቸው አክለውም “መንግስት አንድ ነገር ከመከሰቱ በፊት ጉዳዩን ለማከም እድሉ ስላለው የረጅም ጊዜ ጥቅሞችን እና ውጤቶችን በአግባቡ ማየት አለበትም ብለዋል።
የባንክ ዘርፉ ለውጭ ባለሃብቶች መክፈቱ የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ ከተቀረው አለም ጋር ያለውን ትስስር ከማጠናከር በተጨማሪ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን እና እውቀትን ወደ ኢንዱስትሪው ለማምጣት ያስችላል ተብሏል።
• @ThinkAbyssinia •