የፋይናንስ ደኅንነት አገልግሎት ሕገወጥ ገንዘብ አስተላላፊዎችን አስጠነቀቀ የፋይናንስ ደኅንነት አገልግሎት ሰኞ መስከረም 16 ቀን 2015 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ፣ በሕገወጥ ገንዘብ ማስተላለፍ ድርጊት መሰማራታቸውን አረጋግጫለሁ ብሎ የጠቀሳቸው አዶሊስ፣ ሸጌ፣ ሰላምና ሬድ የተባሉ የገንዘብ አዘዋዋሪዎችና የውጭ ምንዛሪ በማስቀረት በአገር ውስጥ በብር የሚከፍሉ ሌሎች አካላት፣ ከድርጊታቸው እንዲታቀቡ በማሳሰብ ሕጋዊ ዕርምጃም እንደሚወስድ ማስታወቁን ሪፖርተር ዘግቧል፡፡
ተቀማጭነታቸውን በውጭ አገሮች ያደረጉና በገንዘብ ማስተላለፍ ድርጊት የተሰማሩ አካላት፣ በሕጋዊ መንገድ ውደ ኢትዮጵያ መግባት የነበረበትን የውጭ ምንዛሪ ለኢትዮጵያ ባንኮች የላኩ በማስመሰል፣ የውጭ ምንዛሪ እዚያው ሲያስቀሩ እንደነበርም አስታውቋል፡፡
ሐሰተኛ ደረሰኝ ጭምር በማዘጋጀትና በመጠቀም የውጭ ምንዛሪውን በውጭ አገሮች በማስቀረት፣ በኢትዮጵያ ውስጥ የውጭ አገሮች ገንዘብ ምንዛሪና የኑሮ ውድነት እንዲባባስ በማድረግ ላይ መሆናቸውንም፣ ባገኘው መረጃ ማረጋገጡን ገልጿል፡፡ አገልግሎቱ መሰል የፋይናንስ ወንጀሎችን የሚፈጽሙ አካላትንም ሆነ ግብረ አበሮቻቸውን በሕግ ተጠያቂ እንደሚያደርግ አስታውቋል፡፡
• @ThinkAbyssinia •