የሸራው ላይ ምስሌ (ሱመያ ሱልጣን) ያ የኔ ጎረቤት፣ ያ ምስኪን ሰዓሊ ፣ ሸራውን ወጥሮ፣ የበዙ ቀለምን ፣ከስሩ ደርድሮ፤ ይሞነጫጭራል። ልብን የሚመስል፥ ትንሽዬ አካል፣ በጥቁር አቅልሞል። ወዲያ በዚያ ደግሞ፥ በጫማ ምስል ስር ፣ የወደቀ አእምሮ፣ አቧራ ቀብቶ፡ ከጭቃ ጋር አስሮ ፣ ከእድፍ ከምሮ። ደግሞ ባንደኛው ጥግ፡ እጆች ይታያሉ፣ የተንጠለጠሉ፤ የሆነ ብልጭልጭ፡ ሊያወርዱ ሚመስሉ። ያ የኔ ጎረቤት፣ ያ ምስኪን ሰዓሊ፣ ፈግጎ ይስላል፣ ደግሞ ይኮሳተራል። ጥያቄዬን እንደታቀፍኩ ፣አስተዋልኩት ያንን ሙንጭርጭር፣ ለምን ራሴን አየሁት? ቀድምውንስ እዛ ነበር?? ፊቴን ነው እንጂ ያልሳለው፣ ስእሉማ የኔ እኮ ነው። የ እጆቼን መዳረሻ፡ ያዛን ልቤን አጠቋቆር፣ በብሩሹ ሳለብኝ፣ የአመታት አኗኗሬን፡ በሸራው ላይ ለጠፈብኝ፤ ይፋ አወጣኝ። ፊቴን ነው እንጂ የቀረው፣ ምስሉማ የኔ እኮ ነው። @sumeyasu 3.1K views09:00