Get Mystery Box with random crypto!

የቀጠለ ምስኪኒቷ እናቴ! በሞላ ጎዳና ባልጠበበ ድንበር ፥ በዘር ገመድ ታግዳ ነጻ ነኝ ትላለ | አጫጭር ግጥሞችና መጣጥፎች 📚

የቀጠለ


ምስኪኒቷ እናቴ!
በሞላ ጎዳና
ባልጠበበ ድንበር ፥ በዘር ገመድ ታግዳ
ነጻ ነኝ ትላለች
መንጋነት ያሰረው ፥ ባሪያ ትውልድ ወልዳ፡፡
የጀግንነት እብሪት
ልባችንን ደፍኖት ፥ ማሰብ እየከዳን
እንዴት ነው ነጻነት
እንዳበደ ፈረስ ፥ ስሜት እየነዳን፡፡
ገድሎ የመንገስ ጥማት
ጩኀት ላገነነ ፥ አመጽ ላጀገነው
ለዚህ ምስኪን ትውልድ
በጅምላ እየነዱት
በመንጋ እያሰበ ፥ ነጻነት እንዴት ነው?
ነጻነት ምርጫ ነው!
አምሮ ቢደላደል
ጥፋት ያመነነው ፥ የመንጋዎች መንገድ
እንቅፋቱን ወዶ
ለኖሩለት እውነት ፥ ለብቻ መራመድ!
ነጻነት ማመን ነው
ቀን ወዶ ቢያጀግን ፥ ቀን ጠልቶ ቢከዳም
ቢቆሽሹም ቢደምቁም
እራስን መቀበል
ራስን መምሰል ነው ፥ የነጻነት ገዳም!
ነጻነት ማሰብ ነው
በአንድነት መለምለም
የኔነትን አረም ፥ ከህሊና ማጥፋት
ዘር ሆኖ ከማነስ
ሀገር ሆኖ ማበብ ፥ ዓለም ሆኖ መስፋት።

ንገሯት ለሀገሬ ...
በጀግኖቿ ትግል
ድንበር ባታስደፍር ፥ ከእጀ ገዥ ብትወጣ
ነጻ ነኝ እንዳትል
በገዛ ልጆቿ ፥ በእጅ አዙር ተሸጣ ፡፡
ስሩን ካልሸመነው
በመዋሃድ ጥለት ፥ በማስተዋል ሸማ
ታሪክ አናደምቅም
በጭብጨባ ድግስ ፥ በሆይ ሆይታ ዜማ፡፡
ምን ብናቀነቅን
በየሰልፉ ሜዳ ፥ ወኔ ብንደግስም
በፈረሰ አይምሮ
በደቀቀ አንድነት ፥ ሀገር አናድስም፡፡
በጭፍን ከመሮጥ
አስቦ ማዝገም ነው ፥ የመራመድ ውሉ
ሁሉም እንቅፋቶች
እስኪጥሉን ድረስ ፥ ምርኩዝ ይመስላሉ፡፡
በድፍን ግልብ እሚያጋድል
ህዝብ የመሆን ፥ መንጋ አይንዳን
በማሰብ ስር እንፈወስ ፥ በሰውነት ፀበል እንዳን፡፡
ከእግዜር ልንወዳጅ
ለምህረቱ ጥላ ፥ እምባ ብንደግስም
ልብን ሳይመልሱ
ለንስሃ መሮጥ ፥ ከጽድቅ አያደርስም፡፡
ውብ ነገን እናውርስ
ትላንትን አክመን ፥ በይቅርታ ፀበል
ትውልድ ይጨርሳል
ያረገዝነው እምባ ፥ የቋጠርነው በቀል
ከመስጠት አንጉደል
ከቀማኞች ገደል ፥ ተረግጠን ብንጣል
ካሸከሙን በቀል
ምናወርሰው ፍቅር ፥ ሀገር ይለውጣል፡፡

ከዕድሏ ጣሪያ ላይ
ዘር የቀዳደው ፥ ሽንቁሯ ቢበዛም
ያ ከንቱ ፎካሪ
ባፈጀ ቀረርቶ ፥ ሺህ ጉራ ቢነዛም
ሚሊዮን ዘር ቢሸጥ ፥ አንድ ሀገር አይገዛም፡፡
ኢትዮጵያዊነት ነው
የትርታችን ልክ ፥ የነፍሳችን ግጥም
መልስ ቤት በራቀው
በከረመ ፀሎት ፥ ሰርክ ብታንጋጥም
አጎንብሳ ድሃ
ባፀናችው ጉልበት ፥ ብትረጋገጥም
ነፍሷን አደህይታ
ባሻረችው ቁስል ፥ ብትገሸለጥም
ሀገር ሆና ገዝፋ
በየ ጎጣጎጡ ፥ አትርመጠመጥም፡፡
የዘመን እውነት ነን
ከደግነት ሰማይ ፥ በጥበብ የኖርን
ትዕግስትም ልክ አለው
ፈርተን እንዳይመስለው ፥ ስላቀረቀርን፡፡
ማተብ አስሮን እንጂ
ተጣልተን እንዳንቀር ፥ በክፍፍል ገደል
ከሀገር ክብር በልጦ ፥ ሞት ብርቃችን አይደል፡፡
ንገሩት ለዛ ሰው
ከዓለም ጫፍ እስከ ጫፍ
ኃይል እንደ ተራራ ፥ ገዝፎ ቢከመርም
ክንዱን አፈርጥሞ
እልፍ የሰገደለት ፥ ጀግና ቢሰድርም
ዓለም የሞተበት
የጠላት ማርከሻ ፥ ጦር ቢደረድርም
በአንድ ዓይናችን ሰላም
በኢትዮጵያችን ክብር፥ አንደራደርም !!!

​​ ┈┈┈┈•◦●◉❖◉●••┈┈ ┈
ሕሊና ደሳለኝ
╰══•••┈ ┈ ┈•◦●◉❖◉●••┈┈ ┈
፳፻፲፪ ዓ.ም