Get Mystery Box with random crypto!

#የማጀት_ሥር_ወንጌል ሙያተኛ ሀገሬ ከማጥገብ ጎደለ በረከት እራቀው ፥ የገበታሽ ለዛ ተሻምቶ | አጫጭር ግጥሞችና መጣጥፎች 📚

#የማጀት_ሥር_ወንጌል

ሙያተኛ ሀገሬ
ከማጥገብ ጎደለ
በረከት እራቀው ፥ የገበታሽ ለዛ
ተሻምቶ ለመጉረስ
ከበላነው ይልቅ ፥ የደፋነው በዛ፡፡
ሙያሽ ባያስደፍር ፥ አጀብ ቢሰኙበት
ማዕዱ ቢሙላላ ፥ ዓይነቱ ቢያምርበት
አበዛዙ አይደለም
አበላሉ ላይ ነው ፥ የገበታሽ ውበት፡፡
እየተማመንን!
የፉክክር ቅሚያ ፥ በርሃብ እየናጥን
ከደፋነው ጠግቦ ፥ ውሻችን በለጠን፡፡
ከምርት አላነስን
ጎተራችን ሙሉ
ጀግና አራሽ ፥ መች አጥተን?
ማሰብ የጎደለው
አያያዛችን ነው ፥ ገደል የከተተን፡፡
ይልቅ ግዴለሽም!
ከምግባር ምጣድ ላይ
ሳንበስል አንጋግተሸ ፥ ከማዕድ አትምሪን
ገበታሽ እንዲያምር
ከእግዜር የሚያስታርቅ ፥ ፍቅር አስተምሪን።

ገበታ ዕድሜ ነው ፥ ባለ ማሰብ መክነን
ሳንፀነስ ጃጀን ፥ ሳንጣድ አረርን
ከዘመን ገበታ
ከፊደል አቅድመን ፥ ዘር እየቆጠርን
ገበታ ሀቅ ነው
በክፋት ሊጥ ጋግረው ፥ ያሻገቱት እውነት
በሆዳም እስክስታ
ረግጠው ያፈኑት ፥ የምስኪናም ጩኸት
እስከ ልጠይቅሽ...
በጥም ደዌ ደቆ
የረሃብ ጠኔ ደፍቶት ፥ እልፍ ትውልድ ያልፋል
ቢራ ለመጥመቂያ
ሚበተን ገብስ ግን ፥ ከሀገር መች ይጠፋል፡፡
ከሆድ በማይሻገር
የማጀት ቤት ዕውቀት ፥ አጥብበሽ አትለኪን
እስቲ መኖር ይግባን
ከማስተዋል መቅደስ ፥ ሰው መሆን ስበኪን።

ዘመን ካልገበረው
ከችጋር ተራራ ፥ ከሲኦል ዳር ኑሮ
እንዴት ነው መሻገር
ከመርፌ ቀዳዳ ፥ በጠበበ አይምሮ።
ከምስኪን ዘመን ላይ
የማይኖሩበትን ፥ ዕድሜ መበዳደር
ለአንዲት ማምሻ ደስታ
በአያት እስትንፋስ ላይ ፥ ቁማር መደራደር
ያሳፍራል አይደል?
እያደጉ ማነስ ፥ እያነሱ መዝቀጥ
አጎንብሶ ያፀናን
የድሃ እናት ጉልበት ፥ በጭካኔ መርገጥ
ያሳምማል አይደል?
መንገስ ከሚያባላስ
መጥገብ ከሚያቃቅር ፥ ማግኘት ከሚያጎለን
ማጣት ውሎ ይግባ
ባርነት ይሰንብት ፥ ድህነት ይግደለን፡፡
ከረፈደ ፀፀት
ደረት እየደቁ ፥ ከእግዜር ቢዋቀሱ
ትርጉሙ ምንድነው ?
ሲኖር ተቃቅሮ ፥ ሲሞት መላቀሱ።
በእናታችን አድባር ፥ በፍቅሯ ይሁንብን
መድመቅ ካጋደለን ፥ ቆሽሸን ይመርብን
በመጠማት ሲቃ
እስትንፋስ እስኪያንቃት ፥ ነፍሳችን ትርበትበት
ብቻህን ከመጥገብ
አብሮ መራብህ ነው ፥ ሰው የመሆን ውበት፡፡
በድፍን ግልብ እሚያጋድል
ህዝብ የመሆን መንጋ ፥ አይንዳን
በማሰብ ስር እንፈወስ ፥ በሰውነት ፀበል እንዳን።
አየህ! ሰው ስትሆን
ከመንጋነት ሚያግድ
እረኛ አያሻህም ፥ ከህሊናህ በላይ
ስታስብ መሪ ነህ
በብስለት ከፍታ ፥ በማስተዋል ሰማይ፡፡
አየህ! ሰው ስትሆን
የጎጥ አረም ነቅለህ
በአንድነት መስክ ላይ ፥ ፍቅር ትዘራለህ፣
በወረወሩብህ የጥላቻ ድንጋይ
ትውልድ የሚያፋቅር ፥ ድልድይ ታበጃለህ፡፡
አየህ! ሰው ስትሆን
ዝምታህ ኃያል ነው
ጀግና የሚያንበረክክ
ከፈሪ ቀረርቶ ፥ ከባዶ ሰው ጩኀት
ሀገር ላምስ ከሚል
በመንደር አጀንዳ ፥ በአሽኮለሌ ተረት፡፡
አየህ! ሰው ስትሆን
ነጻ ነህ እያሉህ
መታሰር ያምርሃል
መቀመቅ መበስበስ
የኖርክለት እውነት ፥ ሀገር እስኪፈታ
በሀቁ እስኪመዘን
ስለ በርባን ክብር
የቆሸሸው ፍቅር ፥ የታሰረው ጌታ
ከድል ታሪክ ሰማይ
ከሥልጣኔ ዳር ፥ ከጥበብ ከፍታ
እንሻገራለን
ህዝብነትን ትተን ፥ ሰው የሆንን ለታ፡፡

በትረ ጥበበ ቢካን
ዓለም ሊያንቀጠቅጥ ፥ ድል ሥልጣን ቢሰጠው
ጀግና መሪ አይደለም
ብርቱ ተመሪ ነው ፥ ሀገር ሚለውጠው፡፡
አስተውል ወዳጄ
ጠልተን ላንጣላ
ችለን ላንጋደል ፥ ነደን ላንፋጀው
የኛው ትርምስ ነው
በልቶ ለሚያባላ ፥ ጠላት ሚበጀው፡፡
ስጋና ደም እንጂ
የአንድነታችን ውል ፥ የፍቅራችን ቀለም
ያሰመርነው ክልል
የታጠርንበት ዘር ፥ ቋንቋችን አይደለም፡፡
ከመዋሃድ መቅደስ
ትውልድ እናስተምር ፥ ዘመን ይመርቀን
ፍቅራችን ምን ጎድሎት ፥ ደማችን ያስታርቀን፡፡
በልጆቿ አጥንት
በደም ኪዳን ምለን ፥ የገባንላት ቃል
ከጩኀት ያለፈ
ዘመን የሚሻገር ፥ ተግባር ይጠይቃል፡፡
በአንድ ሃሳብ ተጋምደን
በድል ድር እናብር
ውድቀታችን ያንቃን ፥ ሠርተን እናሳምን
ሆነን ድል እንንሳ ፥ የአፍ ጀግንነት ይብቃን፡፡