ባለሃብቶች በኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ለመሳተፍ ገና ካሁኑ ፍላጎታቸውን እያሳዩ ነው ተባለ
የሀገር ውስጥና የውጭ ባለሃብቶች በ2016 ዓ.ም በጀት ዓመት በሚጀመረው የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ውስጥ ለመሳተፍ ከወዲሁ ፍላጎታቸውን እያሳዩ መሆኑን የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለስልጣን አስታውቋል።
የካፒታል ገበያ ባለሃብቶች፣ ድርጅቶች፣ ግለሰቦች ወይም መንግስት ለሚያስፈልጋቸው ኢንቨስትመንት ካፒታል በጥሬ ገንዘብ አልያም በአይነት የሚያሰባስቡበትና የሚያገኙበት ገበያ ነው፡፡
በተለይም በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ባሉበት ሆነው በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች እንዲሳተፉ ሰፊ እድል ይፈጥራል የተባለ ሲሆን ይህም ካፒታል በማሰባሰብ፣ የገንዘብ ሥርዓቱን በአዲዲስ ፈጠራዎች በመደገፍ እና ኢንቨስትመንትን በማስፋፋት የአገሪቱን ኢኮኖሚ ልማት ያግዛል ተብሏል፡፡
በተጨማሪም በቀላሉ ቢዝነስ ለመጀመር፣ ለማስፋፋት እና የሚያስፈልጉ ጥሬ እቃዎችን በአፋጣኝ ለማግኘት እንዲሁም የውጭ ኢንቨስተሮችን በቀላሉ ለመሳብና ከትናንሽ ቢዝነሶች እስከ ትላልቅ ኮርፖሬሽኖች ለመመስረት እድል ይፈጥራል፡፡
ምንጭ - ኢዜአ