Get Mystery Box with random crypto!

ሐጀተል ወዳእ (የመሰናበቻው ሐጅ) . . ᴛᴇᴀᴍ ʜᴜᴅᴀ . በወርሀ ዙልሒጃ ከሚነሱ እውነታ | TEAM HUDA

ሐጀተል ወዳእ
(የመሰናበቻው ሐጅ)
.
.
ᴛᴇᴀᴍ ʜᴜᴅᴀ
.
በወርሀ ዙልሒጃ ከሚነሱ እውነታዎች አንዱ የሆነው የኢስላም አምስተኛው ማእዘን ሐጅ ነው። በነብዩላህ ኢብራሂም አለይሒሰላም እና በልጃቸው ኢስማኢል አማካኝነት በተገነባው ካእባ ዙሪያ የሚደረግ አምልኮ! የቆዳ ቀለም፣ ፆታ፣ ጎሳ፣ ብሔር፣ የሰውነት ገፅታ ሳይለያያቸው አቤቱ ጌታችን የሚሉበት የእኩልነት ማሳያ ኢባዳ!

ወቅቱ አስረኛው አመተ ሒጅራ ወርሀ ዙልቃኢዳ ሐያ ስድስተኛው ቀን ቅዳሜ ነበር። ረሱሉ ሰለላሁ አለንሒ ወሰለም በይፋ ለሐጅ መነሳታቸውን ካወጁ በኋላ የመዲና ነዋሪዎች (የቻሉት በሙሉ) ከረሱሉ ሰለላሁ አለይሂ ወሰለም ጋር በመጣመር ስንቃቸውን ቋጥረውና ለጉዞ ተዘገጃጅተው ወደ መካ ጉዞ ጀመሩ። አቡበከር አስሲዲቅ እየመሩ በዘጠነኛው የሒጅሪያ አመት ወደ መካ ካቀኑ በኋላ ቀጣዩ የጉዞ ቅፍለት መሆኑ ነው። እኚህ መቶ ሺህ የሚደርሱ አስሐቦች ገላቸውን ተጣጥበውና ሐርመው (ኢህራም አድርገው) ጉዞ ተጀመረ።

ረሱሉ ሰለላሁ አለይሒወሰለም ውድ ግመላቸው የሆነችው ቀስዋህ ላይ ከወጡ ጀምሮ መዲና በተልቢያ ተናወጠች።

<<ለበይከላሁመ ለበይክ ለበይከ ላሸሪከ ለከ ለበይክ ኢነል ሐምዳህ ወንኒእመተህ ለከወልሙልክ ላሸሪከለክ>>
<<አላህ ሆይ! (ታዛዥ ሆኜ መጥቻለሁ) አቤት። አንተ ተጋሪ የለሕም አቤት ምስጋናና ፀጋ ያንተ ነው። ንግስናም ያንተ ነው። ተጋሪ የለህም።" ሲሉ በአንድ ድምፅ ያስተጋባሉ።

የመጀመሪያው የጉዞ ማረፊያ አል አሪጅ ሆነ። ቀጣይ አል አብዋእ፣ አስፋን፣ ዚጡዋህ በቅደም ተከተል የሰፈሩባቸው ስፍራቸው ናቸው። ዚጡዋህ ሲደርሱ ዙልሒጃህ አራተኛው ቀን ነበር። ገላቸውን ተጣጥበው በሰሜን የመካ መግቢያ ወደ ካእባ አቀኑ።

ከነብይነታቸው በፊት ወደቦታው እንዲመልሱ የተመረጡለትን ሐጀር አል አስወድን ስመው ወደ ጠዋፍ ስነስርአት አመሩ። የመጀመሪያዎቹ ሶስት ዙሮች በፍጥነት ቀጣዮቹን አራት ዙሮች ደግሞ እየተራመዱ ካእባን ዞሩ። ከዚህ በኋላ መቃሙ ኢብራሒም ላይ ቆመው የበቀራህን መቶ ሐያ አምስተኛ አያ (አንቀፅ) አነበቡ።
<<ቤቱንም ለሰዎች መመለሻና ጸጥተኛ ባደረግን ጊዜ (አስታውስ)፣ ከኢብራሂምም መቆሚያ መስገጃን አድርጉ፤ ወደ ኢብራሂምና ወደ ኢስማዒልም ቤቴን ለዘዋሪዎችና ለተቀማጮቹም ለአጎንባሾች ሰጋጆቹም አጥሩ ስንል ቃልኪዳን ያዝን፡፡” [አል-በቀራህ፡ 125]

ከዚያም ከመቃሙ ኢብራሒም ትይዩ ሑለት ረከአ ሰላትን ሰግደው ለሁለተኛ ጊዜ ሐጀር አል አስወድን ሳሙት። ሶፋና መርዋ ጋር የሔዱት ከዚህ በኋላ ነበር። ሰፋ ተራራ አጠገብ ሲደርሱ የሚቀጥለውን የቁርአን አንቀፅ አነበቡ።

<<ሰፋ እና መርዋህ ከአላህ ትእዛዝ መፈፀሚያ ምልክቶች ውስጥ ናቸው። ቤቱን (ከእባን) በሐጅ ወይም በኡምራህ ስራ የጎበኘ ሰው በሁለቱ መሀከል በመመላለሱ በርሱ ላይ ሐጢአት የለበትም። መልካምንም ስራ በፈቃደኝነት የሰራ ሰው አላህ ይመነዳዋል። አላህ አመስጋኝ አዋቂ ነውና።>>
[አል በቀራህ:158]

በሰፋና መርዋ መሐል ሰዕይ ካደረጉ በኋላ መስዋእት ያመጡ ሲቀሩ ከኢህራማቸው እንዲፈቱ አዘዙ። መስዋእት ያላመጡት ፀጉራቸውን በማሳጠር ኡምራ ብቻ እንዲያደርጉ ሲታዘዙ ቀሪዎቹ በኢህራማቸው ቆዩ። ረሱሉ ሰለላሁ አለይሒ ወሰለምና ባልደረቦቻቸው መካ ውስጥ ከእሑድ ጀምሮ አራት ቀናትን ቆይተው ሐሙስ ጠዋት ሚና ሰፈሩ። በማግስቱም ከዚህ በፊት ቁረይሾን ከሌላው ተነጥለው ከሚያርፉበት መእሸር አል ሐረምና ሙዝደሊፋ በተቃራኒ ከአረፋህ ተራራ በደቡብ በኩል ባለው ነሚራህ የተሰኘው ቦታ ላይ ቁባ የሚመስል ድንኳን አስተክለው አረፉ።

ነብያችን ሰለላሁ አለይሒ ወሰለም ፀሐይ ወደ ምእራብ ስትገሰግስ ወደ ኡረናህ ሸለቆ አመሩና ከ120 ሺህ ለሚልቀው የሐጅ ታዳሚ ኹጥባ ማድረግ ጀመሩ።

<<ሰዎች ሆይ ንግግሬን አድምጡ። ምናልባት ከዚህ አመት በኋላ በዚህ ቦታ ላይ ዳግም ላንገናኝ እንችላለን። በዚህ በሀገራችሁ በዚህ ወራችሁ የዛሬው ቀን ክቡር እንደሆነ ሁሉ ደማችሁና ሐብታችሁ የተከበረና የማይደፈር ነው። የመሐይምነት ዘመን የደም ብቀላ ውድቅ ሆኗል። መጀመሪያ ውድቅ የሚደረገው የኢብን ረቢአ ኢብን አል ሐሪስ ደም ነው። እርሱ በበኑ ሰዕድ ጎሳ ውስጥ የገባ ሲሆን በሁዘይል ጎሳ ተገድሏል። የቅድመ ኢስላም አራጣ ውድቅ ተደርጓል። መጀመሪያ ውድቅ የተደረገው የዐባስ ኢብኑ አብዱልሙጠሊብ አራጣ ነው።

★በሴቶች ጉዳይ አላህን ፍሩ። የወሰዳችኋቸው በአላህ አደራ ሲሆን ብልቶቻችሁንም ሐላል ያደረጋችሁት በአላህ ቃል ነው። እናንተ በነርሱ ላይ የምትጠሉትን ሰው በፍራሻችሁ ላይ እንዳያስቀምጡ የማድረግ መብት አላችሁ። ይህን ከጣሱ የማይጎዳ ምት ምቷቸው። እነርሱ በእናንተ ላይ ያላቸው መብት ቀለባቸውንና አልባሳታቸውን ልታቀርቡላቸው ነው።

በሚገባ ከያዛችሁት የማትጠምሙበትን ነገር ትቼላችኋለሁ። የአላህን መፅሐፍ! ስለኔ ብትጠየቁ ምን ብላችሁ ትመልሳላችሁ?>> ሲሉ ንግግራቸውን በጥያቄ አሳረጉ።
ሰሐቦችም <<መልእክቱን በሚገባ ማድረስዎትንና እኛንም ከልብ መምከርዎን እንመሰክራለን።>> አሉ። ረሱላችን አለይሒሰላምም እጃቸውን ከፍ አድርገው ወደ ህዝቦቻቸው እየተመለከቱ <<አላህ ሆይ ምስክሬ ሁን፣ አላህ ሆይ ምስክሬ ሁን፣ አላህ ሆይ ምስክሬ ሁን>> በማለት ተናገሩ።

ንግግራቸውን ሲቋጩ የሚከተለው የቁርአን አያ ወረደ።
<<ዛሬ ሐይማኖታችሁን ሞላሁላችሁ።ጸጋዬንም በናንተ ላይ ፈፀምኩ። ለእናንተም ኢስላምን ከሐይማኖት በኩል ወደድኩ።>> [አል-ማኢዳህ:3]

ቢላል አዛን አድርጎ ነብያችን ሰለላሁ አለይሒ ወሰለም እና ባልደረቦቻቸው የዙህርን ሁለት ረከአ ሰላት ሰገዱ። ከዚያም ቢላል ሌላ ኢቃም አድርጎ የአስርን ሁለት ረከአ ሰገዱ። ፀሐይ ከገባች በኋላ ወደሙዝደሊፋ በማቅናት በሁለት ኢቃም የመግሪብንና የኢሻን ሰላት ሰግደው ተኙ። ከሱብሒ ስግደት በኋላ ወደ መእሸረል ሐረም ጋለቡ። ወደቂብላ ዞረው ዱአ አደረጉ። ለፀጋው አመሰገኑ።

ከዚህ በኋላ የነበረው ጀምረተል ኩብራ (የጠጠር ውርወራ) ነበር። በእያንዳንዱ ጠጠር ተክቢራ እያደረጉ ሰባቱንም ጠጠር ወረወሩ። የእርድ ስርአቱ ቀጠለ። ስልሳ ሶስቱን ረሱላችን ሰለላሁ አለይሒ ወሰለም ሲያርዱ ሰላሳ ሰባቱን ሰይዱና አሊይ ረዲየላሁ አንሁ አርደው ለሚቀርቧቸው ሰዎች አከፋፈሉ።

ጠዋፈል ኢፋዳን(የመጨረሻ ጠዋፍ) ለመፈፀም ሲሉ ወደመካ ተመለሱ። በዚያው 'ለት ወደሚና ተመልሰው ካደሩ በኋላ ማግስቱን ጀመራት ላይ ጠጠር ጣሉ። በዚህ መልኩ ለተከታታይ ሶስት የዙልሒጃ ቀናት ጠጠር እየወረወሩ ከቆዩ በኋላ ወደ መዲና ጉዞ ጀመሩ። ጁሕፋ አቅራቢያ ሲደርሱ እንዲህ ሲሉ ተናገሩ፣
<<ሰዎች ሆይ እኔ ሰው ነኝ። ምናልባትም የጌታዬ መልእክተኛ(መለከል መውት) ወደኔ ይመጣና መልስ እሰጥ ይሆናል። በመካከላችሁ ሁለት ከባድ ነገሮችን ትቻለሁ። የመጀመሪያው የአላህ መፅሀፍ ነው። ሁለተኛው ደሞ የኔ ቤተሰቦች(አህሉል በይት) ናቸው። የእኔን ቤተሰብ በተመለከተ አላህን እንድትፈሩ እጠይቃችኋለሁ።>>

የመዲና ድባብ ከሩቅ በታያቸውም ጊዜ እንዲህ አሉ።
<< ከአላህ በስተቀር ሌላ አምላክ የለም። ብቸኛ ነው። አጋርም የለውም። ንግስና የርሱ ነው። ምስጋና የሚገባውም ለርሱ ነው። እሱ በሁሉም ነገር ላይ ቻይ ነው። ንስሐ ገብተን ለአላህ ተገዢዎች፣ ሰጋጆችና አመስጋኞች ሆነን ተመልሰናል። አላህ ቃሉን አረጋገጠ። ባሪያውን ረዳ። ብቻውንም አህዛብን ድል ነሳ።>>

ይህ ነበር የረሱሉ ሰለላሁ አለይሒ ወሰለም የመጨረሻ ሐጅ፣ ለኡማው ፈር የቀደዱለት ከጃሒሊያ በኋላ የነበረ የመጀመሪያው ሐጅ። ሐጀተል ወዳእ!