2023-05-15 13:23:52
“ኢቮሊውሽን - ፬”
(Jan 14, 2020 የተጻፈ)
Theistic Evolution (Evolutionary Creationism)
አዝጋሚ ለውጥ እውነት ቢሆንስ? እውነትነቱ የክርስትናን እውነትነት ወይም የእግዚአብሔርን እውነት ያስቀራልን? በጭራሽ። ይህን የሚሉት ዕውቁ ሳይንቲስት ፍራንሲስ ኮሊንስ ናቸው፤ “The Language of God” በሚለው መጽሐፋቸው። ምክንያቱም እውነት ከእውነት ጋር አይጣረስምና! እውነት ከእውነት ጋር አይጋጭምና! እውነትና እውነትን አይቀዋወሙምና።
ፍራንሲስ ኮሊንስ ዕውቅ ሳይንቲስት ናቸው፤ ጥሩ ክርስቲያንም ናቸው። ስለ ዘረ መል ለማጥናት የተቋቋመው Human Genome Project መሪ ነበሩ። አስደናቂውን የዲኤንኤ ግኝት ለፕሬዚዳንት ቢል ክሊንተንና ለጠቅላይ ሚኒስትር ቶኒ ብሌየር ሲያስረዱ ከቢል ክሊንተን ያገኙትን “This is the language of God” የሚል አስደናቂ ንግግር ነው የመጽሐፋቸው ርእስ ያደረጉት። ዶ/ር ኮሊንስ ለእምነትና ለሳይንስ ባደረጉት በጎ አስተዋጽዖ የተከበረውን የቴምፕልተን ሽልማት ተቀብለዋል፤ BioLogos የተሰኘ በእምነትና በሳይንስ መካከል በሚኖረው ግንኙነት ላይ የሚሠራ ተቋምም መሥራች ናቸው። ፍራንሲስ ኮሊንስ ዝግመተ ለውጥ እውነት ስለ መሆኑ ባዮሎጂያዊ ማስረጃዎችን እያቀረቡ ያስረዳሉ። መላለሙ (ዩኒቨርሱ) ቢሊዮን ዓመታት ገደማ እንደ ሆነውም ይቀበላሉ። በሰዎች፣ በዓሣማ እና በዝንጀሮ መሰል እንስሳት ዲኤንኤ መካከል ያለውን ተመሳሳይነትም ያስረዳሉ።
በፍራንሲስ ኮሊንስ የቀረበው የኢቮሊውሽን ንድፈ ሐሳብ ማለትም Theistic Evolution ባለፈው ከተመለከትነው (በቁጥር 3) “ኢንተለጀንት ዲዛይን” ጋር የሚስማማበትም የማይስማማበትም ገጽታ አለው። የሁለቱ ስምምነት የእግዚአብሔርን ፈጣሪነት መቀበላቸው ላይ ነው። የሕይወት አስገኝ እግዚአብሔር ነው። ይህኛው የዝግመተ ለውጥ ክርስቲያናዊ ትንተና ግን፣ እግዚአብሔር ሕይወትን ከመፍጠሩና ለዝግመተ ለውጥ የሚያስፈልጉትን ነገሮች ሁሉ አሟልቶ ሂደቱን ከማስጀመሩ ውጭ በየመካከሉ እየገባ ሂደቱን እንዳልመራ ነው የሚናገረው። በዚህ አመለካከቱ ከኢንተለጀንት ዲዛይን አስተሳሰብ ጋር ይለያያል።
በፍራንሲስ ኮሊንስ አቀራረብ፣ ስለ ፍጥረትም ሆነ ስለ ሕይወት አመጣጥ የሚቀርበው ሳይንሳዊ ትንተና የተሟላ የሚሆነው እግዚአብሔር ሲታከልበት ነው። ለምሳሌ መላለሙ የተገኘው በBig Bang (ታላቁ ቡልቅታ) ንድፈ ሐሳብ መሠረት ከሆነ፣ የፍንዳታው አስጀማሪ እግዚአብሔር መሆን አለበት። ሳይንስም ቢሆን፣ ታላቅ ቡልቅታ/ፍንዳታ በመካሄዱ መላለሙ ስለ መገኘቱ እንጂ የሚፈነዳው ነገር ከየት እንደ መጣ፣ ማን እንዳፈነዳው፣ ሲፈነዳም ሕይወትን ለማኖር አስፈላጊ የሆነው ልከኛ ከባቢያዊ ሁናቴ እንዴት ሊፈጠር እንደ ቻለ መልስ አይሰጥም። የሰዎች፣ የእንስሳትና የተክሎች ሕይወት ከአንድ ሕይወት ጀምሮ እያዘገመ እዚህ ስለ መድረሱ እንጂ “ሕይወት” የተባለው ነገር በመጀመሪያ ከየት እንደ መጣ አይናገርም። ይህ ሁሉ ግን “የእግዚአብሔር ያለህ!” የሚል ጩኸት የያዘ ነው።
መላለሙ ጅማሬ እንዳለው ሳይንሱም ይቀበላል። ጅማሬ ያለው ነገር ሁሉ የተጀመረ መሆኑ ደግሞ አመክንዮታዊ ነው። ይህም የእግዚአብሔርን ተሳትፎ ይጋብዛል። ስለዚህ ክርስቲያኖች የአዝጋሚ ለውጥን ንድፈ ሐሳብ ተቀብለው ከእምነታቸው ጋር ሊያዛምዱት ይችላሉ። የዝግመተ ለውጥ አቀንቃኞችም እግዚአብሔር የፍጥረቱ አስጀማሪ መሆኑን ቢቀበሉ ነው የሚበጃቸው። በዚህም ላይ የአዝጋሚ ለውጥ ትንታኔ ራሱን በየጊዜው እያረመ የሚሄድ በመሆኑ፣ በሁለቱ መካከል ያለው ልዩነት እየጠበበ ሊሄድ እንደሚችል ይታሰባል፤ ትንታኔው ወደ እውነት እየተጠጋ የሚሄድ ከሆነ! በዚህ ትንተና መሠረት ሲታይ፣ ኢቮሊውሽን አምላክ የለሻዊ (atheistic) ብቻ ሳይሆን፣ አምላክ አለሻዊ (theistic) ሆኖ ሊቀርብ እንደሚችል መረዳት ይቻላል።
አዝጋሚ ለውጥ ከክርስትና ጋር ሊስማማ የሚችልበት መንገድ መኖሩ ለበርካታ ክርስቲያኖች ግርታ ይፈጥርባቸው ይሆናል። ነገር ግን የዝግመተ ለውጥ ንድፈ ሐሳብን ጀማሪው ቻርልስ ዳርዊንም ፍጥረት ከእግዚአብሔር መገኘቱን ያምን ነበር። የእርሱ ሙግት ከሕይወት ጅማሬ በኋላ ያለውን ሂደት የሚመለከት ብቻ ነበር። በወቅቱ ከነበሩ ዕውቅ የነገረ መለኮት ሰዎችም የዝግመተ ለውጥ ንድፈ ሐሳቡን የተቀበሉ ነበሩ። በተለይም አንዳንድ ጥብቅ ካልቪኒያውያን የሰውን ልጅ አጠቃላይ ውድቀትና የመሳሰሉትን አስተምህሮቻቸውን ስለሚደግፍላቸው የአዝጋሚ ለውጥ ትንታኔው ተመችቷቸው ነበር። እናም የክርስትና እና የአዝጋሚ ለውጥ ዝምድና ከመጀመሪያም የነበረ ነው።
Theistic Evolution በእግዚአብሔር ሚና ላይ ያለው ትንታኔ ግን ከጥያቄ አያመልጥም። እግዚአብሔር ሕይወትን ከመፍጠርና አዝጋሚውን የለውጥ ሂደት ከማስጀመር በቀር በሂደቱ ላይ መቼም ያልተሳተፈ ከሆነ፣ ፍጥረቱን በሕያውነትና በንቃት የሚያስተዳድር ሳይሆን፣ የፈጠረውን ዓለም በተለያዩ ሕግጋትና አሠራሮች አጥሮ ከፍጥረቱ ገለል ያለ አምላክ ያስመስለዋል፤ ዓለምን እንደ ሰዓት ሞልቶ የተወ አምላክ። ይህ ደግሞ መጽሐፍ ቅዱሳዊው የእግዚአብሔር አሠራር አይደለም።
* * *
እንደ ክርስቲያን አንድ ልንክደው የማንችለው እውነት ቢኖር፣ እግዚአብሔር መኖሩንና የሚታየውንና የማይታየውን ሁሉ የፈጠረው እርሱ መሆኑን ነው። ከእርሱ በቀር አምላክ፣ ከእርሱ ሌላ ፈጣሪ የለም!
አዝጋሚ ለውጥንን በሚመለከት አማኞች ሁልጊዜም ሊጠይቁ የሚገባቸው ሌላኛው ጥያቄ ደግሞ፣ “አዝጋሚ ለውጥ እውነት ነው ወይ?” የሚለው ነው። ይህኛው ዋነኛው ጥያቄም ሁለት የመልስ አማራጮች አሉ።
የመጀመሪያው የመልስ አማራጭ፣ አዝጋሚ ለውጥ እውነት ነው የሚለው ነው። አዝጋሚ ለውጥ እውነት ከሆነ ደግሞ፣ እውነት ሁሉ የእግዚአብሔር ነውና የመቀበል ግዴታ አለብን። ከዚያ ግን የእግዚአብሔርን ፈጣሪነትና አዝጋሚ ለውጥን አስተቃቅፈው ከሚጓዙ ንድፈ ሐሳቦች መካከል አንዱን መቀበል አይቀሬ ይሆናል። (ይህ ሁሉ ግን የዘፍጥረት የመጀመሪያ ምዕራፎች ምን ዐይነት የሥነ ጽሑፍ ዘውግን እንደሚከተሉ በመረዳት ላይ ይወሰናል!) ነገር ግን ንድፈ ሐሳቡ የእግዚአብሔርን ፈጣሪነት ተቀብሎ እንዲጓዝ፣ ክርስቲያን የሳይንስ ባለሞያዎች ጥረትና ተሳትፎ ያስፈልጋል።
አዝጋሚ ለውጥ እውነት ነው ወይ? ለሚለው ጥያቄ ሁለተኛው አማራጭ የሚሆነው ደግሞ፣ በጭራሽ እውነት አይደለም የሚለው ምላሽ ነው። አዝጋሚ ለውጥ እውነት ካልሆነ ግን እስካሁን ስንዳስሳቸው የነበሩት የማስታረቅ ሙከራዎች ሁሉ ፋይዳ አይኖራቸውም። እግዚአብሔርና አዝጋሚ ለውጥን በአንድ ላይ መያዝም አቋም የለሽነት ይሆናል። እውነት ያልሆነን ነገር ከእውነት ጋር ቀይጦ የመጓዝ ጥረት ለእውነት ካለመታመን ተለይቶ አይታይምና።
ታዲያ አዝጋሚ ለውጥ እውነት ነውን? ጥያቄው ሁለት የመልስ አማራጮች ቢኖሩትም፣ ትክክለኛው መልስ ግን አንድ ነው። የትኛው ይሆን?
ጨርሻለሁ።
https://t.me/PaulosFekadu
489 viewsedited 10:23