Get Mystery Box with random crypto!

የመለኮት ባሕርይ ተካፋዮች ነን? እንዴት? የእግዚአብሔር ልጆችስ ነን? እንዴት? ክፍል አራት 2. | ናዝራዊ Tube

የመለኮት ባሕርይ ተካፋዮች ነን? እንዴት? የእግዚአብሔር ልጆችስ ነን? እንዴት?
ክፍል አራት

2. የባሕርይ ተካፋዮች

የልጅነታችን ሂደትስ እንዴት ነው የተከናወነው? የእግዚአብሔር ልጆች የሆንነው በተፈጥሮአችን ወይም በፍጥረታችን ሳይሆን እግዚአብሔር እንደ ልጆች አድርጎ ተቀብሎን ነው። ልጅነት የተሰጠን ስጦታ ነው እንጂ ከወላጆቻችን ስንወለድ በተፈጥሮ እንዳገኘነው ያለ መወለድ አይደለም። ቀደም ሲል ካየናቸው ጥቅሶች አንዱ በገላ. 4 የሚገኘው ነው። ነገር ግን የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ከሴት የተወለደውን ከሕግም በታች የተወለደውን ልጁን ላከ፤ እንደ ልጆች እንሆን ዘንድ፥ ከሕግ በታች ያሉትን ይዋጅ ዘንድ። ልጆችም ስለ ሆናችሁ እግዚአብሔር አባ አባት ብሎ የሚጮኽ የልጁን መንፈስ በልባችሁ ውስጥ ላከ። ስለዚህ ከእንግዲህ ወዲህ ልጅ ነህ እንጂ ባሪያ አይደለህም፤ ልጅም ከሆንህ ደግሞ በክርስቶስ የእግዚአብሔር ወራሽ ነህ። ገላ. 4፥4-7።

ይህ ጥቅስ እንደ ልጆች እንሆን ዘንድ እና ልጆች እንደሆንን በግልጽ ይናገራል። የእግዚአብሔር ቃል በማያሻማ መንገድ ልጆች መሆናችንን ይመሰክራል። ልጆች ነን። ልጆች የሆንነው ደግሞ ምንም የራሳችን ፍሬ ኖሮን ሳይሆን እግዚአብሔር ልጁን እንዲዋጀን ልኮት በእርሱ የዎጆ ሥራ በኩል ነው ልጆች የሆንነው። እርሱን ስንቀበል ልጆች ሆንን። ልጆች የሆንነው እግዚአብሔር ልጆቹ አድርጎን ነው። እንጂ በልጁ በኩል ከራሱ ጋር ባያስታርቀን ኖሮ፥ በራሳችንማ ጠላቶች ነበርን። ቃሉ ልጆች መሆናችንንም ልጆች የሆንነው በመደረግ መሆኑንም ይነግረናል። እነዚህ ሁለቱ እርስ በርስ የሚጋጩ አይደሉም።

ልጆች የሆንነው ልጆች ተደርገን ተወስደን ነው። ከሆንን እና ከተደረግን፥ አድርጎ የወሰደን አለ ማለት ነው። ልንሆን ተወስነን ከሆነ የወሰነ አለ ማለት ነው። በበጎ ፈቃዱ እንደ ወደደ፥ በኢየሱስ ክርስቶስ ሥራ ለእርሱ ልጆች ልንሆን አስቀድሞ ወሰነን። ኤፌ. 1፥5። ይህ ቃል አዲስ ኪዳን በተጻፈበት ቋንቋ υἱοθεσία ሁዮቴሲያ መሆኑንም አይተናል። ልጅ መሆን፥ ልጅ መደረግ፥ እንደ ልጅ መወሰድ ማለት ነው። እኛ በክርስቶስ በኩል የእግዚአብሔር ልጆች ተደርገናል። ታዲያ ተደርገናል የሚለው ያልበቃቸው ሰዎች ከክርስቶስ ጋር እኩያ የሆኑ ልጆች እንደሆኑ ራሳቸውን ያሳብጣሉ። ልጅነት ሥልጣን ቢሆንም (ዮሐ. 1፥12) በሥልጣናችን የተቀዳጀነው ሥልጣን ሳይሆን የተሰጠን ሥልጣን ነው። ይህንን υἱοθεσία ሁዮቴሲያ የሚለውን ቃል ብዙዎቹ የእንግሊዝኛ ትርጉሞች the adoption of sons ወይም the adoption of children ብለው ተርጕመውታል። ትክክለኛ ትርጉም ነው። አንዳንድ ሰዎች ማደጎ እና ጉዲፈቻ የሚለውን ቃል ይጠቀማሉ። ይህ ቃል በአገራችን አሉታዊ የሆነ ምስል ስለሚቀርጽ ለአንዳንዶች ግራ ያጋባል። ያጋባ እንጂ ነገሩ ግን ያ ነው።

በአገራችን ባህል ቃሉ አሉታዊነት የተጫነው ይሁን እንጂ፥ አዲስ ኪዳን በተጻፈበት ዘመንና ዐውድ ይህ ቃልና ልማድ ግን ድንቅ ነገር ነው። በአገራችን ማደጎ ተደርገው የሚወሰዱ ልጆች፥ ችግረኞች፥ አሳዳጊ ያጡ፥ ምስኪኖች፥ ድሀ አደጎች፥ ወላጅ አልባዎች ናቸው። እንደዚህ ብቻ ብንወስደውም እንኳ ትርጉሙ ያስኬዳል። እኛም እኮ በክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጆች ከመሆናችን በፊት ምስኪኖችና ከጸጋ የራቅንና ከክብሩ የጎደልን፥ የወደቅን፥ የሞትን ሙታን ነበርን! ጳውሎስ ይህንን በጻፈበት የግሪክ ወሮሜ ባህልና በአዲስ ኪዳን ዘመን ችግረኛ ሕጻናት ብቻ ሳይሆኑ ትልልቅ ሰዎችም ልጆች ተደርገው ይወሰዳሉ። ወሳጁ ሰው ደግሞ ልጆች የሌሉት ወይም ያሉትም ሊሆን ይችላል። ልጆች ከሌሉት ያንን ልጅ አድርጎ የወሰደውን ሰው ወራሹ ሊያደርገው ከመፈለጉ በጎነት የተነሣ ብቻ ነው ልጅ የሚያደርገው። ልጆች ካሉትም አብሮ ወራሽ እንዲሆን፥ የልጆቹ ወንድም እንዲሆን፥ ቸርነቱ እንዲበዛ ሲል ልጁ ያደርገዋል፤ እኩል መብትም ያቀዳጀዋል። ልጁም በስሙ ይጠራል። ይህ የበጎነት ምልክት ነው።

እግዚአብሔር እኛን ልጆቹ ያደረገን የጸጋው ክብር ይመሰገን ዘንድ ነው። በበጎ ፈቃዱ እንደ ወደደ፥ በኢየሱስ ክርስቶስ ሥራ ለእርሱ ልጆች ልንሆን አስቀድሞ ወሰነን። በውድ ልጁም እንዲያው የሰጠን የጸጋው ክብር ይመሰገን ዘንድ ይህን አደረገ። ኤፌ. 1፥5-6።

የመለኮት ባሕርይ ተካፋይነትስ?

የመለኮት ባሕርይ ተካፋይ ወደሚለው አሳብ እንምጣ። የመለኮት ባሕርይ ተካፋይነት ጥቅስ በ2ጴጥ. 1፥4 የሚገኘው ነው። ስለ ክፉ ምኞት በዓለም ካለው ጥፋት አምልጣችሁ ከመለኮት ባሕርይ ተካፋዮች በተስፋ ቃል እንድትሆኑ፥ በእነዚያ ክብርና በጎነት የተከበረና እጅግ ታላቅ የሆነ ተስፋን ሰጠን። 2ጴጥ. 1፥4

የአማርኛው ትርጉም ገና ሲጀምር በዓለም የሚገኝ ጥፋትን የሚያመጣ ክፉ ምኞትን በመግለጥና ከዚያ ማምለጥን በመናገር ይጀምራል። መለኮት መለኮት መጫወት የሚያምራቸውን ሰዎች ስናይ መጀመሪያ የምናስተውለው ነገር፥ ከዚህ ክፉ ምኞትና ዓለማዊ ጥፋት የራቁ ሳይሆኑ የተጣበቁ መሆናቸውን ነው። ከዓለምና የዓለም ከሆነ ነገር ጋር እየተጫወቱ የመለኮት ባሕርይ ተካፋይነትን ማውራት ይመቻል? አይመችም። ዓለምን እንደ ሙጫ ተጣብቀውባት፥ ስጋዊነትን ተላብሰው፥ ገንዘብን እንደ ውኃ እየተጠሙና እየጠጡ የባሕርይ ልጆች ነን ሲሉ ያስደነግጣል።

የመለኮት ባሕርይ በሚለው ሐረግ ውስጥ፥ ‘መለኮት’ ግልጽ አሳብ ስለሆነ፥ ‘ባሕርይ’ የሚለውን ቃል እንመልከት። መለኮት አምላክነት ነው። አምላክ አንድ ብቻ ነውና እኛ በፍጥረታችን አምላክነት የለንም። ባሕርይ የሚለው ቃል በተጻፈበት በግሪክ ቋንቋ φύσις ፉሲስ ወይም ፊሲስ የሚል ነው። ቃሉ ምን ማለት እንደሆነ በሌሎች የተጠቀሰባቸው ቦታዎች ማየት ተገቢ ነው። ቃሉ በአዲስ ኪዳን ወደ 11 ጊዜያት ተጽፎአል። አራቱ ጥቅሶች ባሕርይ ሲሉ የቀሩት ፍጥረት ይሉታል። ፍጥረት የሚለው ቃልም አሳቡን ይገልጠዋል።

2ጴጥ. 1፥4 ስለ ክፉ ምኞት በዓለም ካለው ጥፋት አምልጣችሁ ከመለኮት ባሕርይ ተካፋዮች በተስፋ ቃል እንድትሆኑ፥ በእነዚያ ክብርና በጎነት የተከበረና እጅግ ታላቅ የሆነ ተስፋን ሰጠን።

ሮሜ 1፥26-27 ስለዚህ እግዚአብሔር ለሚያስነውር ምኞት አሳልፎ ሰጣቸው፤ ሴቶቻቸውም ለባሕርያቸው የሚገባውን ሥራ ለባሕርያቸው በማይገባው ለወጡ፤ ስለምንድር ነው የሚናገረው? ሴቶች ፍጥረታቸውን ወይም ሴትነታቸውን ትተው ከሴትነታቸው ሌላ፥ የሴትነት ባሕርይ ወይም ተፈጥሮ ያልሆነውን ሌላ ለመሆን መሞከራቸውን ነው። ባሕርይ የተባለው የተፈጠሩበት ነገር ወይም ፍጥረታዊ ማንነት ወይም ውስጣዊ ማንነት ነው።

ሮሜ 2፥14 ሕግ የሌላቸው አሕዛብ ከባሕርያቸው የሕግን ትእዛዝ ሲያደርጉ፥ እነዚያ ሕግ ባይኖራቸው እንኳ ለራሳቸው ሕግ ናቸውና፤ ይህም የሚያሳየው ሰዎች ሰዎች ብቻ ስለሆኑ መለኮታዊውን ተሻጋሪ ሕግ ወይም የሕሊና ሕግ ሊኖሩት ሊታዘዙት በውስጣቸው እንደሚያውቁት ይገልጣል። ይህ ባሕርይ የተሰኘው ነገር የውስጥን ማንነት ገላጭ ቃል ነው። ለምሳሌ፥ አትግደል የሚለውን አምላካዊ ትእዛዝ ያልሰማና ያልተማረ ሰው፥ በፍጥረቱ መግደል መጥፎ መሆኑን ያውቃል።