Get Mystery Box with random crypto!

የቀጠለ.... እኛ ቀድሞ ወገን አልነበርንም፤ ኋላ ግን ወገን ሆንን፤ ምሕረት ያገኘን አልነበርንም፤ | ናዝራዊ Tube

የቀጠለ....
እኛ ቀድሞ ወገን አልነበርንም፤ ኋላ ግን ወገን ሆንን፤ ምሕረት ያገኘን አልነበርንም፤ ምሕረት ያገኘን ሆንን። እናንተ ቀድሞ ወገን አልነበራችሁም አሁን ግን የእግዚአብሔር ወገን ናችሁ፤ እናንተ ምሕረት ያገኛችሁ አልነበራችሁም አሁን ግን ምሕረትን አግኝታችኋል። 1ጴጥ. 2፥10። ወገን ያልነበርነው ወገን ከሆንን፥ ተደረግን ማለት ነው። ቀድሞም ወገን የነበረ ሰው ወገን አይደረግም። ለምሳሌ፥ ለአጎቶቼ እኔ የወንድማቸው ወይም የእኅታቸው ልጅ ነኝ። ስወለድ ጀምሮም ወገን፥ ዘመድ ነኝ። ሊያደርጉኝ አይችሉም ቀድሞም ነኝና። ያልሆነ፥ ያልነበረ ሲደረግ ግን ያ ሌላ ነገር ነው። ደግሞም ይቻላል። በተለያዩ ባህሎች አንድ ወይ ሌላ ሥርዓት ይፈጸምና ዝምድና ይፈጠራል። ይህ የጋብቻ ዝምድናን አይጨምርም። አንድ ምሳሌ ብንወስድ፥ በአገራችን የጡት ልጅ የሚባል ልጅነት አለ። በሥርዓቱ ጡት ሳይሆን ጣት ነው የሚጠቡት። ግን አንድ ጡት ጠብተው ያደጉ ወንድማማች ወይም ወንድምና እኅት ይሆናሉ። በአንዳንድ ባህሎች ጣትና ጣት ተበጥቶ ደም ይደማና ደምና ደም ተነካክተው የሥጋና ደም ዘመድ ሆኑ ይባላል። እነዚህ ልጅ ወይም ዘመድ ያልሆኑ ወገን ሲደረጉ ነው። ጉዲፈቻ ከነዚህ ዓይነቶቹ አንዱ ወገንነቶች ወይም ልጅነቶች ነው።

እኛ የእግዚአብሔር ልጆች ከመሆናችን በፊት ልጆች አልነበርንም። ሳንሆን ኖረን፥ ስንሆን ያልነበርነውን ነው የሆንነው። ልጅ ነው የሆንነው። የሆንነውም በመደረግ ነው። ልጅነት ማንነታችን ነው። መደረግ ደግሞ የተደረግንበት መንገድ ነው። በብሉይ ኪዳን ልጆች ሳይሆኑ እንደ ልጅ መቆጠርም ልጆች ሆነው እንደ ሌላ ልጅ መቆጠርም አለ። ለሁለቱም አንድ አንድ ምሳሌ ላሳይ፤ ኤፍሬምና ምናሴ የዮሴፍ ልጆች ናቸው፤ ያዕቆብ ግን እንደ ራሱ ልጆች አድርጎ ወሰዳቸውና ከ12ቱ ነገድ ጋር ተቆጠሩ፤ ዘፍ. 48፥5-6። ልጅ ሆኖ ስላለመሆን ምሳሌ ደግሞ፥ በብሉይ ኪዳን የዋርሳ ሕግ የሚባል አለ። ባል ሳይወልድ ከሞተ የባል ወንድም ሚስቲቱን የራሱ አድርጎ ይወስዳል። ቢወልድም ልጆቹ ወይም ልጁ በሞተው ስም ይጠራል፤ የሟቹ ስምና ርስትም አይቋረጥም፤ ዘዳ. 25። ልጅ ሆኖ ልጅ አለመሆንም፥ ልጅ ሳይሆኑ ልጅ መሆንም አለ።

ጴጥሮስ በ1ጴጥ. 2፥10 ወገን ሳይሆኑ ወገን መሆንን የጠቀሰው ከሆሴዕ ትንቢት (ሆሴ. 1-2) የተወሰደ አስገራሚ የፈረሰና የታደሰ ግንኙነት ምስልም ታሪክም ነው። ይህ የኛ ወገንነትም ምስል ሆኖ በአዲስ ኪዳን በጴጥሮስ የተጠቀሰው ነው። የኛ ታሪክ የኛ ልጅነት ነው። የኛ ልጅነት ድንቅና ግሩም ነው። የኛ ልጅነት ሥልጣን ነው፤ ወራሽነትም ነው። ከእግዚአብሔር ጋር በክርስቶስ በኩል የተመሠረተ ግንኙነት ነው። ይህም ሁሉ ሆኖ ግን ልጅነታችን በበጎነቱ የተሰጠን፥ የተቀበልነው ስጦታና ስጦታ ብቻ ነው እንጂ የተቀዳጀነው ድልና መብት አይደለም። አንዳንድ የሐሰት አስተማሪዎች ይህንን እኛ በበጎነቱ ልጆች የተደረግንበትን ቸርነት ከክርስቶስ ልጅነት ጋር እያነጻጸሩ፥ የኛ ልጅነት እና የእርሱ ልጅነት የመንትያ ያህል አንድ እንደሆነ ሲናገሩና የሰዎችን እምነት ሲገለብጡ ማየት ምንኛ አሳዛኝ ነው!

ቀድሞ አባታችን ያልሆነ አባት የሌላው ልጆች የነበርነውን ልጆች አድርጎ ከተቀበለን የምን ልጅ ትባላለህ? የባሕርይ ልጅ አይደለንም። የባሕርይ ልጅ የሚባል ስለኛ የተነገረ ቃል ከቶም የለም። 1ጴጥ. 1፥4 የባሕርይ ተካፋዮች እንድንሆን በተስፋ ቃል መደረጋችንን ይናገራል። ይህንን በቀጣዩ እንመለከታለን።

ይቀጥላል።

ዘላለም መንግሥቱ
@nazrawi_tube