2022-07-14 21:13:23
ውኃ እንዲጠጣ ቢነግሩት በልቡ ‹‹ለምን በመቅጃው ውስጥ ካለው ከጥሩው ውኃ አይሰጡኝም›› ብሎ አሰበና ሳይጠጣው ቀረ፡፡ ለሁለተኛም ጊዜ ጠጣው ብለው ታዛዥነቱንም እንዲያሳያቸው ቢለምኑት እምቢ አላቸው፡፡ ለ3ኛ ጊዜ ግድ ጠጣ ብለውት ደቀ መዝሙራቸው ውኃ ወዳለበት ኩስኩስት ቢሄድ ውኃው ዐይኑ እያየው ከኩስኩስቱ ላይ ደረቀና ጠፋበት፡፡ የጌታችን እግር እጣቢ መሆኑንም በነገሩት ጊዜ በድንጋጤ እንደበድን ሆነ፡፡ እንዲያረጋጋው በማሰብ ራሱን እብድ በማስመሰል ይኖር ወደነበረ አንድ ትልቅ ጻድቅ ጋር ልከውት አበረታው፡፡ ድንጋጤውም ባልተሸለው ጊዜ አባ ብሶይ ድጋሚ ወደዚያ አባት ላኩትና ሲሄድ ያንን ዕብድ መሳይ ቅዱስ አባት ዐርፈው አገኛቸው፡፡ አባ ብሶይም በትራቸውን ሰጥተው በአስክሬናቸው ላይ እንዲያኖረው ለረድኡ ሰጡትና ሄዶ በትራቸውን በአስክሬኑ ላይ አኑሮት ‹‹ተነሥተህ እንድታነጋግረኝ አባቴ አዞሃል›› ቢላቸው ከሞት አፈፍ ብለው ተነሥተው ‹‹አንተም ለአባትህ ታዛዥ ብትሆን ኖሮ የጌታችንን በረከት አጥተህ እንደዚህ ዓይነቱ ድንጋጤ ላይ ባልወደክ ነበር›› ብለውት ተመልሰው ዐረፉ፡፡
ጻድቁ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስም ለአባ ብሶይ በአካለ ነፍስ ተገልጦላቸው በሰማያት የመነኮሳትን ክብር አይቶ ቀድሞ የምንኩስናን ክብር እንዲህ መሆኑን ቢያውቅ ኖሮ ይመነኩስ እንደነበር ሲነግራቸው እሳቸውም ‹‹አንተስ ምን ጎደለህ የጣዖት አምልኮን አጥፍተህ የቀናች ሃይማኖትን አጽንተሃል›› አሉት፡፡ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስም ‹‹ክብርንስ እግዚአብሔር አብዝቶ ሰጥቶኛል ነገር ግን የመነኮሳትን ክብር ያህል አይሆንም፣ እነርሱ በእሳት ክንፎች እየበረሩ ኢየሩሳሌም ሰማያዊት ሲገቡ አይቻቸዋለሁ›› ብሏቸዋል፡፡
ክብርና ምስጋና ይግባውና ‹‹መንፈስ ቅዱስ የለም›› እያለ የሚያስተምር አንድ የካደ መነኩሴ በእንዴና አገር መኖሩን በመንፈስ አውቀው አባ ብሶይ እጅግ አዘኑ›፡ መስሚያ ጆሮዎቻቸውንም ሦስት አድርገው ሄደው ከሚያስተምርበት ደርሰው ተገናኙት፡፡ ሕዝቡም አባታችንን ሰላምታ ሰጥተው ከእሳቸው ከተባረኩ በኋላ ስለ ሦስቱ ጆሮዎቻቸው ቢጠይቋቸው ‹‹እኔ ልዩ ሦስት አካላት አሉኝ፣ ሥራዬ ሁሉ በእነርሱ አምሳል ነው›› በማለት ሰለ ሥሉስ ቅዱስ አንድነትና ሦስትነት ቅዱሳት መጻሕፍትን እየጠቀሱ ሕዝቡን አስተምረው ከስሕተት ትምህርት ታድገዋቸዋል፡፡ ሕዝቡም ንስሓ ገብተው ወደ ቀናች ሃይማኖት ተመለሱ፡፡ አባ ብሶይን ደቀመዛሙርቶቻቸው ‹‹ጌታችን ለእኛም እንዲገለጥልን ጸልይልን›› አሏቸው፡፡ አባም በጸሎታቸው ጌታችንን ሲጠይቁት ‹‹ነገ በጠዋት ወደ ተራራው ይውጡ በዚያ እገለጥላቸዋለሁ›› አላቸውና ለመነኮሳቱ ሁሉ ይህንን ተናገሩ፡፡ በጠዋትም ተነሥተው ሁሉም ጌታን ለማየት እየተቻኮሉ ወጡ፡፡ በተራራው ግርጌም አንድ የደከሙ ሽማግሌ መነኮሳቱን ‹‹ወዴት ትሄዳላችሁ?›› እያሉ ሲጠይቋቸው ‹‹ጌታችን በተራራው ላይ ሊገለጥልን ነውና እርሱን ለማየት እንሄዳለን›› እያሉ እየተቻሉ ሲሄዱ ሽማግሌው ‹‹እኔንም ይዛችሁኝ ሂዱና ጌታችንን ልየው›› አሏቸው፡፡ ነገር ግን ሁሉም መነኮሳት ትተዋቸው ሄዱ፡፡ አባ ቢሶይ ከሁሉም መጨረሻ ሆነው ወደ ተራራው ሲወጡ ሽማግሌውን አይተው ‹‹አባቴ ወዴት መሄድ ፈልገው ነው?›› ሲሏቸው ሽማግሌውም ‹‹ወደ ተራራው መውጣት ፈልጌ ነበር›› አሏቸው፡፡ አባ ቢሶይ ሽማግሌውን ተሸክመዋቸው ተራራውን መውጣት ጀመሩ፡፡ በመጀመሪያ በጣም ቀለዋቸው ነበር ነገር ግን ተራራውን እየወጡ በመጡ ቁጥር እጅግ እየከበዷቸው መጡ፡፡ የተሸከሟቸውንም ሽማግሌ ሁለቱንም እግራቸውን ሲመለከቷቸው በችንካር ተቸንክረዋል፡፡ መልካቸውም እየተለወጠ መጣ፡፡ ያ ሽማግሌ ግን ራሱ ጌታችን ነበር፡፡
ወደ ተራራውም ወጥተው ጌታችንን ለማየት ሲጠባበቁ የነበሩት መነኮሳት ‹‹ጌታችን የታለ? መች ተገለጠልን?›› ብለው ጠየቋቸው፡፡ አባ ብሶይ ‹‹ጌታችንም ከተራራው ግርጌ ተገልጦላችሁ ነበር ነገር ግን እናንተ ትታችሁት መጥታችኋል›› በማለት የሆነውን ሁሉ ነገሯቸው፡፡ አባ ብሶይ እጅግ ብዙ ተአምራት በማድረግ በታላቅ ተጋድሎ ኖረው ሐምሌ 8 ቀን በታላቅ ክብር ዐርፈዋል፡፡ ረድኤት በረከታቸው ይደርብን በጸሎታቸው ይማረን።
ቅዱሳን ሰማዕታት አቤሮንና አቶም
አቡነ ዮሐንስና ማርያም የተባሉት ደጋግ ወላጆቻው በሃይማኖት በምግባር አሳደጓቸው፡፡ አቤሮንና አቶምም መጻተኞችን በፍቅር በመቀበል በትሩፋትና በበጎ ሥራ ሁሉ ፍጹማን ሆኑ፡፡ እነዚህ ሁለት ወንድማማቾች ለንግድ ፈርማ ወደሚባለው አገር በሄዱ ጊዜ በዚያ ብዙ ሰማዕታት እንዳረፉና በእስርም ላይ እንዳሉ ተመለከቱ፡፡ ከንጉሡም ጭፍሮች የሰማዕቱን የቅዱስ አንያኖስን ሥጋ በብዙ ገንዘብ ገዝተው ወደ አገራቸው ወስደው በክብር አስቀምጠው በፊቱ ሁልጊዜ መብራቶችን አበሩ፡፡ ከሰማዕቱም ሥጋ ብዙ ተአምራት ተገለጡ፡፡ በዚህም ጊዜ ቅዱሳን የሆኑ አቤሮንና አቶም የዚህችን ዓለም ከንቱነት ተረድተው ዘላለማዊውን ሕይወት በመመኘት እነርሱም ምስክር ይሆኑ ዘንድ ተመካከሩ፡፡
ከዚህም በኋላ ወደ እስክንድርያ ከተማ ሄደው በከሃዲው መኮንን ፊት የጌታችን አመላክነት መሰከሩ፡፡ መኮንኑም ደማቸው እንደውኃ እስኪፈስ ድረስ ጽኑ ግርፋት አስገረፋቸው፡፡ እሳት ውስጥም እንዲጨምሯቸው አዘዘ፡፡ ዳግመኛም ስለታምና ረጃጅም በሆኑ ችንካሮች ሥጋቸውን ቸንክረው ከታች በእሳት አቃጠሏቸው፡፡ ጌታችንም መልአኩን ልኮ አዳናቸው፡፡ ዳግመኛም ዛፍ ላይ ዘቅዝቀው ሰቀሏቸውና በአፍ በአፍንጫቸው ብዙ ደም ፈሰሰ፡፡ በዚህም ጊዜ ጌታችን መላእክቱን አስከትሎ ተገለጠላቸውና አበረታቸው፡፡ መኮንኑም አቤሮንና አቶም ደግመው በፊቱ ቆመው ሲመሰክሩ ሲያይ እጅግ አደነቀ፡፡ ወደ ፈርማ አገርም ላካቸው፡፡
በዚያ ያለው መኮንንም ለአማልክት እንዲሰግዱ ሲያዛቸው እነርሱ ግን ጣዖታቱን አቃለሉበትና እውነተኛውን አምላክ ሰበኩለት፡፡ እርሱም ኮምጣጤ፣ ሙጫና ጨው ደባልቆ አፍልቶ በአፍና በአፍንጫቸው ጨመረ፡፡ በብረት አልጋ ላይም አስተኝቶ ከታች እሳት አነደደባቸው፡፡ የእጅና የእግር ጥፍሮቻቸውን አውልቀው በብረት በትር ደበደቧቸው፡፡ በዚህም ወቅት የመኮንኑ ሚስት ሞተች፡፡ ቅዱሳን አቤሮንና አቶምም ወደጌታችን ጸልየው ከሞት አሥነሷት፡፡ መኮንኑም ከሕዝቡ ሁሉ ጋራ በጌታችን አመነ፡፡ ቅዱሳኑንም አክብሮ በሰላም ወደ አገራቸው ላካቸው፡፡
ሀገራቸው ገምኑዲ በደረሱም ጊዜ የቀረ ገንዘባቸውን በሙሉ አውጥተው ለድኆችና ጦም አዳሪዎች ሰጡ፡፡ የሰማዕቱን የቅዱስ አንያኖስንም ሥጋ ሰረባሞን ለሚባል አንድ ጻድቅ ሰው በአደራ ሰጥተው በፊቱም መብራት እንዲያበራ ነግረው እነርሱ ዳግመኛ ወደ ሰማዕትነት አደባባይ ሄዱ፡፡ በርሙን ወደሚባል አገርም ሄደው በከሃዲው መኮንን ፊት የጌታችንን አምላክነት ስመሰክሩ መኮንኑ ይዞ በእጅጉ አሠቃያቸው፡፡ ከጽኑ ግርፋት የተነሣ ደማቸው እንደውኃ ፈሰሰ፡፡ ደንቆና ድዳ የሆነች አንዲት ሴትም መጥታ ከቅዱሳኑ ደም ወስዳ ጆሮዎቿንና አፏን ብትቀባው ወዲያ መናገርና መስማት ቻለት፡፡ በዚህም ብዙዎች በጌታችን አመኑ፡፡
ከዚህም በኋላ መኮንኑ ማሠቃየት በሰለቸው ጊዜ የቅዱስ አቤሮንና የቅዱስ አቶምን ራሶቻቸውን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘ፡፡ እነርሱም ራሶቻቸውን ተሰየፉና የሰማዕትነታቸው ፍጻሜ ሆነ፡፡ በመንግሥተ ሰማያትም የክብር አክሊልን ተቀዳጁ፡፡ አባ ሰረባሞንም ከሕዝቡ መጥቶ ቅዱስ ሥጋቸውን ወደ አገራቸው ገምኑዲ ወሰደው፡፡ ከከተማዋም ውጭ በደረሱ ጊዜ የቅዱሳኑን ሥጋ የተጫነበት ሠረገላ የማይንቀሳቀስ ሆነ፡፡ ሰዎቹም በድንጋጤ ቆመው ሳሉ ‹‹ሥጋችን በውሰጡ ይኖር ዘንድ እግዚአብሔር የመረጠው ቦታ ይህ ነው›› የሚልን ቃል ከሰማይ ሰሙ፡፡ በዚያም
15 viewsᴍᴇsᴇʟᴇ ɴɪɢᴀᴛᴜ, 18:13