Get Mystery Box with random crypto!

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በሥርዓቱ መሠረት የበዓላቱና የአጽዋማቱ መደብ የሚታወቅበትና የዘመናቱ ሂደት | ማኅበረ ቅዱሳን ( Mahibere Kidusan)

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በሥርዓቱ መሠረት የበዓላቱና የአጽዋማቱ መደብ የሚታወቅበትና የዘመናቱ ሂደት ተቀምሮ የሚታወጅበት ዕለት መስከረም አንድ ቀን ርእሰ ዐውደ ዓመትን ታከብራለች፡፡ የኢትዮጵያ የወራት ሁሉ መጀመሪያ መስከረም ነው፡፡ በዚህ ወር የመጀመሪያው ቀን የተለያዩ መጠሪያዎች አሉት፡፡ እነርሱም ዘመን መለወጫ፣ ዕንቁጣጣሽ፣ ቅዱስ ዮሐንስ እየተባለ ይጠራል፡፡

አዲስ ዓመት መስከረም አንድ ቀን ለምን ይከበራል?

በኢትዮጵያ (ርእሰ ዐውደ ዓመት) ዘመን መለወጫ በመስከረም ወር የሆነበትን ምክንያት ሊቃውንቱ ሲያትቱ ብርሃናት ፀሐይ፣ ጨረቃ፣ ክዋክብት የዓመት ዑደታቸውን በጳጉሜ አጠናቀው በመስከረም ወር ስለሚጀምሩ ነው፡፡ ያን ጊዜ ሌሊቱ ከቀኑ ጋር እኩል ፲፪ ሰዓት ይሆናል፡፡ ዓመቱን ጠንቅቀው ሲቆጥሩ ፫፻፰፬ ቀናት ይሆናል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ “ለዘመን መታወቂያው ይሆን ዘንድ ፀሐይና ጨረቃ ከዋክብትንም ፈጠረ” ይላልና (ሄኖክ. ፳፩፥፵፱)፡፡ በሌላ በኩልም በዘመነ ኖኅ ከንፍር ውኃ ምድር የተገለጠችበት ወር ነው፡፡ (ኩፋሌ. ፯፥፩)፡፡ “በመጀመሪያው ወር ምድር ታየች የንፍር ውኃም ከምድር ደረቀ” የሚለውን መጽሐፍ ቅዱሳዊ ቃል መሠረት አድርገው የአቡሻኸር ሊቃውንት የዘመን መለወጫን ታሪካዊ አመጣጥን አብራርተው አስቀምጠዋል፡፡

የቤተ ክርስቲያንን ቀኖናዊ ሥርዐት ያጠኑ ሊቃውንት ደግሞ አዲስ ዓመት መስከረም አንድ ቀን መሆኑን አስመልክተው በጽሑፋቸው ዘመኑን በአራቱ ወንጌላውያን ይከፍሉታል፡፡ ምክንያቱም በዘመነ ዮሐንስ ተፀንሶ በዘመነ ማቴዎስ ተወልዶአል፡፡ የጌታን መጠመቅ፣መሰቀልን፣ ዓለምን ከፍዳና ከመርገም ነጻ ማውጣትን አራቱ ወንጌላውያን እያወሱ ዘመናትን ተከትለው ያለ እንቅፋት እንደሚጓዙ ያስረዳሉ፡፡ ወንጌላዊውን ወይም ዘመኑን ለማወቅ ዓመተ ፍዳ(ኩነኔ) አምስት ሺህ አምስት መቶ እና ዓመተ ምሕረት (አሁን ያለንበትን ዓመት) በመደመር ውጤቱ ለአራቱ ወንጌላውያን ማለትም ማቴዎስ፣ ማርቆስ፣ ሉቃስና ዮሐንስ በማካፈል የምናገኘው ነው፡፡ ይህም የአንዱ ወንጌላዊ ድርሻ ማለት ነው፡፡ በዚህም መሠረት ቀሪው አንድ ከሆነ ዘመኑ ማቴዎስ፣ ሁለት ከሆነ ዘመነ ማርቆስ፣ ሦስት ከሆነ ዘመነ ሉቃስ ምንም ቀሪ ባይኖር ደግሞ ዘመነ ዮሐንስ ነው፡፡ ስሌቱም ከዚህ በታች የተቀመጠውን ምሳሌ መነሻ አድርጎ ወንጌላዊውን ማን እንደሆነ ማወቅ ይቻላል፡፡ስለ አዲስ ዓመት በተለያየ ስም የመጠራቱ ታሪካዊ አመጣጥና ስያሜ መነሻ አሳቡ ምን እንደሆነ እንደሚከተለው እንመለከታለን፡፡

አዲስ ዓመት ለምን ቅዱስ ዮሐንስ ይባላል...?

የቅዱስ ዮሐንስ ተግባር በቕዱስ ዮሐንስ አወርቅ የተጠቀሰ ሲሆን ቅዱስ ዮሐንስ ደግሞ ለዘመነ ወንጌል በር ወይም መነሻ እንዲሆን ለኢትዮጵያ ዐውደ ዓመት መስከረም አንድ ቀን እንዲከበር አባቶች ወስነዋል፡፡ (ድርሳነ ዮሐንስ አፈወርቅ ገጽ ፩-፫)፡፡ መጽሐፈ ስንክሳር “የመስከረም ወር የተባረከ ነው፡፡ እርሱም የግብጽና የኢትዮጵያ ዓመቶች መጀመሪያ ነው፡፡ የዚህ ወር ቀኑና ሌሊቱ እኩል ፲፪ ሰዓት ነው፡፡ ከዚህ በኋላ ቀኑ እየጎደለ ይሄዳል” እንዲል፡፡ በአጠቃላይ ዘመን መለወጫ ከላይ ባየናቸው የተለያየ ስያሜ ይጠራ እንጂ ዘመኑ አዲስ እየተባለ ቢጠራም አዲስ መሆን ያለበት ወርና ወቅቱ ብቻ ሳይሆን የእኛ የክርስቲያኖች ሥርዓት ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰውነታችሁን አታርክሱ የእግዚአብሔር ማደሪያ ነውና እያለ በመዋዕለ ሥጋዌው ያስተምር ነበር፡፡ አዲስ ዓመት ሲመጣ በኃጢኣት፣ በተንኮል፣ በክፋት የቆሸሸው ሰውነታችን በንስሓ፣ በቅዱስ ቊርባን፣ በመልካም ተግባር አዲስ ልናደርገው ይገባናል፡፡

ዘመነ ማቴዎስም፣ ዘመነ ማርቆስም፣ ዘመነ ሉቃስም ሆነ ዘመነ ዮሐንስ፤ በአራቱም ዘመናት አስቀድሞ ርእሰ ዐውደ ዓመት ቅዱስ ዮሐንስ ይዘከራል፡፡ ዮሐንስ የስሙ ትርጉም «ጸጋ እግዚአብሔር» ማለት ነው፡፡ ዘመናት ዘመናትን እየወለዱ፣ ሰዓታት ደቂቃን ቅጽበትን (ሰኮንድን) ሳይቀር እየሰፈሩ(እየቆጠሩ) ዕለታት ሳምንታትን፣ ሳምንታት ወራትን፣ ወራት ዓመታትን አሁን ላለንበት ዘመን ደርሰናል፡፡

ዕንቁጣጣሽ

ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እንደሚያስረዱት ዕንቁጣጣሽ የሚለው ስያሜው አመጣጥ ወይም ጥንተ ታሪክ በመጀመሪያ ኖኅ ለሦስቱ ልጆቹ አህጉራትን በዕጣ ሲያካፍላቸው አፍሪቃ ለካም ደረሰችው፡፡ በአፍሪቃ ምድርም ሲገባ በመጀመሪያ ያረፈው በሀገረ ኢትዮጵያ በወርኀ መስከረም ነበር፡፡ ሀገሪቱም በአደይ አበባ አሸብርቃ ነበር፡፡ ወሩ ወርኃ መስከረም በመሆኑ ደስ ብሎት «ዕንቁ ዕጣ ወጣሽልኝ» ይህችን ወቅት ዕንቁጣጣሽ ብሏታል፡፡ በመቀጠል የሀገራችን ንግሥት ንግሥተ ሳባ የንጉሥ ሰሎሞንን ዜና ጥበብ በጆሮዋ የሰማችውን በዓይኗ ዓይታ ለመረዳት ስለፈለገች ወደ ኢየሩሳሌም ገባች፡፡ ንግሥተ ሳባም ከንጉሡ ሰሎሞንም ተገናኝተው ቤተ መንግሥቱንም አስጎበውኝቶ ሲያበቃ «ዕንቁ ለጣትሽ ጌጥ ይሁንልሽ» ሲል እጅግ በጣም የከበረ ዕንቁ አበረከተላት/ሰጣት/፡፡ ወሩም ወረኃ መስከረም ነበር፡፡

ንግሥቷ ጠቢቡ ሰሎሞንን ለመጎብኘት በሔደችበት ወቅት ፀንሳ ቀዳማዊ ምኒልክን በወለደች ጊዜ ሕዝቡ ንጉሥ ተወለደ እልል እያሉ «አበባ ዕንቁ (አብረቅራቂ ድንጋይ) ጣጣሽ (ገጸ በረከት)» እያለ ገጸ በረከት ለንግሥቲቱ አበረከቱ፡፡ ያ የዘመን መለወጫ በዓልም ልጃገረዶች የአበባ ገጸ በረከት የሚያቀርቡበት ስለሆነ ዕንቁጣጣሽ ተባለ፡፡ ከዚህ በመነሣት እንቁጣጣሽ የሚለው መጥቷል፡፡ አሁን ከሚፈጸመው ሥነ ሥርዓት ደርሶ በመፈጸም ላይ ይገኛል፡፡ የሚከበረውም መስከረም አንድ ቀን ነው፡፡ አንድም «ዕንቁ ዕፅ አወጣሸ»ብሎ የአበባውን መፈንዳትን ያስረዳናል፡፡ የዘመን መለወጫ (ርእሰ ዐውደ ዓመት) ዕንቁጣጣሽ ተብሎም እንደሚጠራ ታሪክ ያወሳናል፡፡ ስያሜውም ለበዓሉ የተሰጠው በንግሥተ ሳባ ዘመነ መንግሥት ነበር፡፡

አዲሱ ዓመት የሰላም፣ የአንድነትና የመተሳሳብ ዘመን እንዲሆንልን የእግዚአብሔር ቸርነት የቅደስት ደንግል ማርያም አማላጅነት ከሁላችን ጋር ይሁንልን አሜን፡፡