Get Mystery Box with random crypto!

ሰኞ መርሃ ግብር / ማኅበረ ጽዮን

የቴሌግራም ቻናል አርማ mahberetsion — ሰኞ መርሃ ግብር / ማኅበረ ጽዮን
የቴሌግራም ቻናል አርማ mahberetsion — ሰኞ መርሃ ግብር / ማኅበረ ጽዮን
የሰርጥ አድራሻ: @mahberetsion
ምድቦች: ያልተመደበ
ቋንቋ: አማርኛ
ተመዝጋቢዎች: 1.85K
የሰርጥ መግለጫ

ሰኞ መርሃ ግብር / ማኅበረ ጽዮን:
✍የኢትዮጲያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተከርስቲያን ያከበረቻቸው ቅዱሳን ታሪክ
✍ የቤተክርስትያኗን ትክክለኛ አስተምህሮዋን የያዙ መዝሙራት
✍ አጭርና ተከታታይ ትምህርቶች
✍ ለመናፍቃን ጥያቄዎች መልስ
✍ ወቅታዊ መረጃዎችና ሌሎችንም የሚያገኙበት ቻናል
➾ሀሳብ አስተያየት ካላችሁ @Hailegebereal19አድርሱን

Ratings & Reviews

4.00

2 reviews

Reviews can be left only by registered users. All reviews are moderated by admins.

5 stars

1

4 stars

0

3 stars

1

2 stars

0

1 stars

0


የቅርብ ጊዜ መልዕክቶች 2

2022-09-01 07:19:28 #ወማየ_ብሔራሰ_ሕሙም_ውእቱ

#አንብቡኝ
።።።።።። የጣፈጠው ውሃ።።።።።።።።።።።።።።

በውዳሴ ማርያም ዘቀዳሚት ላይ እንደተማርነው ፣ አባቶቻችን አመሥጥረው እንደተረጎሙልን #ልሕኵት_ንጽሕት የሚለውን ሲያትቱ ከአቀረቧቸው የብሉይ ኪዳን ምሳሌዎች አንዱ #ልሕኵተ_ኤልሳዕ_አንቺ_ነሽ የሚል ነው።
ሐተታው እንዲህ ይላል
#አንድም ልሕኵተ ኤልሳዕ አንቺ ነሽ። ኤልሳዕ መምህሩ ኤልያስን ሸኝቶ ዮርዳኖስን ተሻግሮ ኢያሪኮ ደረሰ። "ሠናይ ንብረታ ለዛቲ ሀገር" "ይህቺ ሀገር እንደምን ናት?" ብሎ ጠየቀ። የሀገሪቱ ሰዎችም "ሀገሪቱማ ሀገር ትመስል "#የስንዴው_ዛላ_እፍኝ_ይመላ ፣ #የወይኑ_ዘለላ_ጽዋዕ_ይመላ" እንዲሉ #ሀገሪቱ_ደግ ናት። #ወማየ_ብሔራሰ_ሕሙም_ውእቱ ነገር ግን ውሃው (የሀገሪቱ ውሃ) ደህነኛ ቢጠጣው ይታመማል ፣ ወላድ ቢጠጣው ይመክናል" አሉት። እሱም "አምጽኡ ሊተ ልሕኵተ ፄው = ጨው ጨምራችሁ አዲስ ሸክላ (ማሰሮ፣ጓድ፣እንስራ፣ማድጋወዘተ) አምጡልኝ" አላቸው። እነሱም "ጨው ጨምረው ሸክላ አመጡለት። "ከመዝ ይቤ እግዚአብሔር ፈወስክዎ ወአጥዓምክዎ ለዝንቱ ማይ ወዘይሰቲ እምዝንቱ ማይ አልቦ ዘይመክን ወዘይደዊ = እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ ይህን ውሃ ፈወስኩት አጣፈትኩት ከዚህ ውሃ የሚጠጣ የሚመክን የሚታመም የለም አይኑር" ብሎ ከነቁ (ከምንጩ) ቢቀብርበት በሽተኛ (ሕመምተኛ) ቢጠጣው የሚድን፣ መካን ቢጠጣው የሚወልድ (መካን ብትጠጣው የምትወልድ) ሁኗል/ሁናለች። #ይህ_ምሳሌ_ነው ልሕኵት (አዲስ ሸክላ) የእመቤታችን ፣ ጨው የጌታችን ፣ ምረር የፍዳ የመርገም ምሳሌ። ፍዳ መርገም የጠፋልን ከእመቤታችን ወዲህ ነውና። ብለው አትተዋል።
ዕፁብ ድንቅ ምሳሌ ነው የእመቤታችን ምልጃ በረከት አይለየን!!!
#አሁን_ለማለት_የፈለግሁት
ኢትዮጵያ ኢያሪኮን መስላ ትታየኛለች #ፖለቲካዋ የኢያሪኮን መራር ውሃ መስሎ ይታየኛል። #ኤልሳዕ ቢመጣና ይህቺ ሀገር እንዴት ናት? ብሎ ቢጠይቀን #የእኛም መልስ እንደ ኢያሪኮ ሰዎች " #ሀገሪቱማ ሀገር ትመስል መሬቷ የዘሩበትን ያበቅላል ፣ የተከሉበትን ያጸድቃል፤ የውሃ ችግርም የለባትም በጋ ከክረምት ማልማት ይቻላል ፣ ሰውም ሃይማኖተኛ ነው ይጸልያል ፈጣሪውን በጧት በማታ ይጠራል #ነገር_ግን ፖለቲካው ደህነኛ ሰው ሲይዘው ዘረኛ ፣ አሳሪ ፣ ገዳይ ፣ ሕዝብን ከሕዝብ የሚያጋድል፣ የሚያለያይ፣ ሰዎችን የሚያፈናቅል ፣ ተዋደው ተዋልደው በአንድ ሰፈር የኖሩትን ሰዎች የሚያጣላ፣ ለእኔ ብቻ የሚል ያደርገዋል" ብለን በኀዘንና በለቅሶ የምንነግረው ይመስለኛል።
#እሱም "ከዚህ በኋላ በኢትዮጵያ በፖለቲካው የሚሳተፉ ሰዎች ሕዝባቸውን የሚያስቀድሙ ከዘረኝነትና ከጥላቻ የወጡ የመሪነትን ትርጉም የሚኖሩ ሰውን የማያሳዝኑ በአንፃሩ ግን ሰውን ሁሉ (ኢትዮጵያውያንን ሁሉ) የሚያስደስቱ ይሁኑ" ብሎ #ሸክላ የተባለ #ሰላምን እና #ጨው የተባለ #ፍቅርን ከምንጩ ፖለቲካችን የሚቀብርበት ማለት የሚያሳድርበት ይመስለኛል።
ከዚያ በኋላ የውሃው ምረት ጠፍቶ በሽተኛ ቢጠጣው የሚድን ፣ መካን ቢጠጣው የሚልድ እንደሆነ ሁሉ፤
በሀገራችንም ፖለቲካው ሰውን የማያፈናቅል ፣ እርስ በእርስ የማያገዳድል፣ ወንድሜ ወንድሜ እህቴ እህቴ የሚያስብል ከድህነት የሚያወጣ ሀገርን የሚያለማ የሚያበለጽግ ይሆናል።

#በሃይማኖት ተቋማትና በመንግሥት ተቋማትም ጥላቻን አውጥቶ ፍቅርን ፣ መለያየትን አውጥቶ አንድነትን ፣ ዘረኝነትን አውጥቶ ተባብሮ መሥራትን ፣ ያልተማሩትን አውጥቶ የተማሩትን ፣ ገፊዎችን አውጥቶ የተገፉትን ወዘተ የሚያስገባ የሚተክል እንደሚሆን አልጠራጠርም።

#ታላቁ_ነቢይ_ኤልሳዕ ሆይ እባክህ ኢያሪኮ ኢትዮጵያን ጎብኛት። የመረረ ውሃ ፖለቲካዋን አጣፍጠው። ሕዝቦቿም ጣፍጧቸው ይጠጡ።
#እኔም የሃይማኖት አባት ነኝ በጊዜዬ ሕያው የሆነ አገልግሎት አገልግዬ ሩጫየን ጨርሼ ወደ ሕያወ ባሕርይ ፈጣሪዬ እግዚአብሔር ሂጃለሁ። አሁን በረድኤት ካልሆነ በአካል መምጣት አልችልም።
#ዛሬም የሃይማኖት አባቶች አሉ እነሱ አያጣፍጡላችሁም ትለን እንደሆነ ዛሬስ ያሉ የሃይማኖት አባቶች እንኳን ውሃ ፖለቲካችንን ሊያጣፍጡልን ለእራሳቸውም በጣፈጡልን ማለት ከዘረኝነት በወጡልን ብለን ይምንመልስ ብዙዎች እንደምንሆን አልጠራጠርም።
ግን ግን ግን ተስፋ አንቁረጥ
ነቢዩ ኤልሳዕ "ከዚህ ውሃ የሚጠጣ የሚታመም የሚመክን የለም አይኑር" ብሎ ጸልዮ ከምንጩ ቢቀብርበት መራራው ውሃ እንደጣፈጠ፤
መምህሩ አልያስን (ብፁዕ አቡነ ቄርሎስን) የሚንከባከብ ነቢዩ ኤልሳዕ (ብፁዕ አቡነ ኤርምያስ) በኢትዮጵያ ኢያሪኮ ስላለ "#ይህ_ጦርነት_ይቆም_ዘንድ_እማጸናለሁ" በማለት በሌሊትም በቀንም እንደሚጸልይ ቃል ገብቶልናልና እንጽናና እንጸልይ እንበርታ።

እግዚአብሔር ሆይ መራሩን ፖለቲካ አጥፍተህ ለሕዝቡ የሚጣፍጠውን ፖለቲካ አምጣልን ከመጠፋፋት ሕዝቡን ጠብቅ ጎልበተኞችንም አንተ ውደቅባቸው ከፋፋዮችንም ከክፋታቸው መልስ!!! አሜን!

በመምህር ዳንኤል አለባቸው
68 viewsⓋⓐⓣⓛⓚⓐⓝⓐ, 04:19
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-09-01 07:19:09 ✞✞ የቤተክርስቲያን ጉባኤያት ✞✞

ዓለም አቀፍ የቤተክርስቲያን ጉባኤያት
በዓለም አብያተ ክርስቲያናት ዘንድ ተቀዳሚና ተቀባይነት ያላቸው
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያንም የምትቀበላቸውና
ለሥርዓተ ቤተክርስቲያን ምንጭነት ከፍተኛ ድርሻ ያላቸው አበይት
ጉባኤያት 3 ናቸው፡፡
እነዚህም
1- ጉባዔ ኒቅያ በ325 ዓም
2- ጉባዔ ቁስጥንጥንያ በ381 ዓም እና
3- ጉባዔ ኤፌሶን በ431 ዓም ናቸው፡፡
1) ጉባኤ ኒቅያ (በ325 ዓ.ም)
የኒቂያ ጉባኤ የተጠራው የአርዮስን ክህደት ለመቃወም ነው፡፡
የአርዮስ ክህደት መነሻ ያደረገው በምሳ. 8፡22 ያለውን ቃል ነው
ማለትም ‹‹እግዚአብሔር ዓለማትን ሳይፈጥር አስቀድሞ
ፈጠረኝ›› የሚለውን በማንሳት ‹‹ወልድ ፍጡር ነው›› እያለ
ማስተማር ጀመረ፡፡ በዚህ አካሄዱ ብዙዎችን ማሳሳት ጀመረ
የእስክንድርያ ሊቀጳጳስ አለ እስክንድሮስ ከክህደቱ እንዲመለስ
ብዙ ጣሩ ነገር ግን እርሱ ሊመለስ አልቻለም እንደውም ከ320
ጀምሮ ክህደቱን ማስፋፋት ጀመረ፡፡ በዚህ ጊዜ ሊቀ ጳጳሳቱ እለ
እስክንድርዮስ 100 የሚያህሉ ኤጲስ ቆጶሳትን ሰብስቦ ክህደቱን
አስረዳቸው፡፡ ጉባኤውም የአርዮስን ክህደት ከመረመሩ በኋላ
አወገዙት ጉዳዩ በእስክንድርያ ብጥብጥና ሁከታን እያስከተለ
በመሄዱ ንጉሱ ቆስጠንጢኖስ የስፔንኑን ኤጲስ ቆጶስ ሆስያስን
ወደ እስክንድርያ ላከው፡፡ ከኤጲስ ቆጶሳት ጋር ሲወያይ ሰንብቶ
ወደ ንጉሱ ተመለሰ፡፡ ጉዳይ በሽምግልና መፍታት እንደማይቻል
ለንጉሱ አስረዳው፡፡ ከዚህ በሁዋላ ጉባኤው እንዲደረግ
ተወስኗል፡፡
ጉባኤው በአርዮስ ክህደት ላይ ተወያይቶ አርዮስና ተከታዮቹ
የወልድን የባህርይ አምላክነት በመቃወም የጠቀሳቸው ጥቅሶች
የተሳሳቱ እንደሆኑ አስረድቷል፡፡በዚህም መሠረት በምሳሌ 8÷22
የተጠቀሰው ጥቅስ ቃለ እግዚአብሔር ወልድ ዓለም ከመፈጠሩ
በፊት ከአብ ባህርይ መገኘቱን (መወለዱን) እንጂ እንደፍጡራን
ሁሉ ያልተፈጠረ መሆኑን አርዮስ እንዲረዳው የጉባኤው አባቶች
ብዙ ደክመዋል፡፡ ከቅዱሳት መጽሐፍትም ቃል እየጠቀሱ ቃለ
እግዚአብሔር ወልድ የባህርይ አምላክ መሆኑን አስረድቷል፡፡
ወልድ የአብ የባህርይ ልጅ አንጂ ያልተፈጠረ መሆኑን ለማስረዳት
የተጠቀሱትም (ዮሐ 1÷1-14 እና 14÷30 ሮሜ 9÷15 ፤ 1ዮሐ
5÷20) እና እነዚህን የመሳሰሉት ናቸው፡፡
አርዮስ ከክህደቱ ሊመለስ ባለመቻሉ 318 ቅዱሳን አበው
በመንፈስ ቅዱስ ‹‹እንደ አንድ ልብ መካሪ እንደ አንድ ቃል
ተናጋሪ›› በመሆን አርዮስን አውግዘው የወልድን አምላክነት
የሚገልጽ የሃይማኖት አንቀጽ አፀደቁ፡፡ ቤተ ክርስቲያንም በ318
ሊቃውንት በ325 ዓ.ም በኒቅያ ጉባኤ የተወሰነውን ውሳኔ ተቀብላ
ታስተምራለች፡፡
2) የቁስጥንጥንያ ጉባኤ (381 ዓ.ም)
የቁስጥንጥንያ ጉባኤን የተሰበሰቡት በ381 ዓ.ም ነው፡፡ ጉባኤውን
የተሰበሰቡበት ምክንያቶች የመቅዶንዮስን፣ የአቡሊናርዮስንና
የአውሳብዮስን ክህደቶች በመስማት ነው፡፡
የመቅዶንዮስ ክህደትም የመንፈስ ቅዱስን ከአብና ከወልድ ጋር
በባህርይ በመልክ አንድ አይደለም፡፡ መንፈስ ቅዱስ ከአብ ከሰረፀ
አብ እና ወልድም መንፈስ ቅዱስን ከላከና መልዕክተኛ ከሆነ
ከእርሱ ጋር ትክክል አይደለም ከእነርሱ በታች (ህፁፅ) ነው
የሚል ነበር፡፡ ይህ ትምህርቱም በምስራቅ አብያተ ክርስቲያናት
መዛመት ስለጀመረ አንድ መቶ ሃምሳ (150) ኤጲስቆጶሳት
በቁስጥንጥንያ በ301 ዓ.ም ተሰብስበው ዐቢይ ጉባኤ አደረጉ፡፡
በዚህ ጉባኤ ከብሉያትና ከሐዲሳት እየጠቀሱ መንፈስ ቅዱስ
ከአብ ቢሰርፅም ከአብና ከወልድ ጋር በባህርይ በመለኮት አንድ
መሆኑን ከእነርሱ ጋር ትክክል መሆኑን (መዝ. 33፡6፤ ኢሳ. 6፡3፤
የሐዋ. 28፡28) በመጥቀስ ትምህርቱን አውግዘዋል፡፡
በኒቂያ 318 ቅዱሳን አበው የወሰኑትንም አንቀጸ ሃይማኖት
በማጠናከር የመንፈስ ቅዱስን አምላክነት በሚገባ ገልጸው
‹‹ከአብ የሰረፀ ጌታ ሕይወት ሰጭ በሚሆን በመንፈስ ቅዱስ
እናምናለን ከአብ እና ከወልድ ጋር እንሰግድለታለን እርሱም
በነቢያት አድሮ የተናገረው ነው›› ብለው በኒቂያ የሃይማኖት ውሳኔ
ላይ ጨምረው ወሰኑ፡፡
3) የኤፌሶን ጉባኤ (431 ዓ.ም)
- ጉባኤ ኤፌሶን በ431ዓ.ም በኤፌሶን ከተማ በ200 ሊቃውንት
የተካሄደ ነው፡፡ የስብሰባው መሪ ቄርሎስ ነበር፡፡
- የስብሰባው ዋና ምክንያት የንስጥሮስ ክህደት ነው፡፡
- ንስጥሮስ የተማረው በአንጾክያ ሲሆን ክህደቱም ለክርስቶስ
ሁለት ባህሪያት አሉ፡፡ አምላክም ሰው የሆነው በንጽረት ነው፡፡
ንጽረት ማለትም እመቤታችን የወለደችው ሰውን ብቻ ነው፡፡
ስለዚህ እርሱአም ወላዲተ አምላክ አትባልም የሚል ነው፡፡
- ንስጥሮስን ተከራክሮ የረታውና መልስ ያሳጣው
እስክንድርያዊው ሊቀጳጳስ ቄርሎስ ነው፡፡ ቅዱስ ቄርሎስ
"የእግዚአብሔር ልጅ በማርያም አደረ፡፡ በመከራም ጊዜ ተለየው"
የሚሉ ንስጥሮስንና ወገኖቹን የተጠቀሰውን የማርያም ልጅ ብቻ
ከሆነ ጥያቄ በክህደትና በድፍረት የተከፈተ አፋቸውን አስይዞ
ይመልሳቸው እንደነበር የቤተክርስቲያን ፀሐፊዎች ዘግበውታል፡፡
የአባቶቻችን በረከት በሁላችን ላይ ይደር፡፡
ምንጭ፡- የቤተክርስቲያን ታሪክ በዓለም መድረክ በብጹዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ በከፊል የተወሰደ
66 viewsⓋⓐⓣⓛⓚⓐⓝⓐ, 04:19
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-09-01 07:18:51 + ድንገት የተበጠሰ ገመድ +

የደብረ ዳሞ ገዳም በገመድ ብቻ የሚወጣ እጅግ ጥንታዊ ገዳም ነው:: ይህንን አቡነ አረጋዊ በዘንዶ የወጡትን ታላቅ ገዳም ለመውጣት በግንባታው ወቅት በአፄ ገብረ መስቀል የተሠራ ደረጃ ነበረው:: ሆኖም አቡነ አረጋዊ ደረጃውን ዳህምሞ (አፍርሰው) ብለው በማዘዛቸው እስከ አሁን ድረስ በገመድ የሚወጣበት ገዳም ሆኖአል::

የደብረ ዳሞ መውጫ ገመድ እጅግ ወፍራም ሲሆን እስከ አሁን ድረስ በብዙ ሺህዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ተንጠላጥለው ወጥተው ወርደውበታል:: ይህ እጅግ ወፍራም ገመድ ለዘመናት ሲያገለግል ተበጥሶ ሰው ጥሎ አያውቅም:: በታሪክ የማይዘነጋና መሃል ላይ የተበጠሰበትና ሰው የጣለበት ቀን አለ:: (የዲያቢሎስ መተናኮል ነው የሚል አለ)

በዚያ ቀን በተበጠሰው ገመድ ላይ የወረደው መንገደኛ ጻድቁ አባ ተክለ ሃይማኖት ነበሩ:: መነኮሳቱን ተሰናብተው በዚያ ገመድ ሲወርዱ ተበጥሶ የማያውቀው ገመድ ድንገት ተበጠሰ:: ከላይ የሚያዩት አባቶች ቁልቁል እያዩ በድንጋጤ ጮኹ:: ሆኖም እግዚአብሔር ለጻድቁ የብርሃን ክንፍ ሠጥቶአቸው ከተበጠሰው ገመድ ተለይተው እንደ መልአክ በርረው ሁለት ሺህ ክንድ ያህል ወርደው መሬት ላይ አረፉ:: ባረፉባት ሥፍራም ቤተ ክርስቲያን ተሠራባት::

ወዳጄ በሕይወትህ ድንገት የተበጠሰ ገመድ የለም? ሳትጠብቀው የተበጠሰ ገመድ ማንም ላይ ሳይበጠስ አንተ ላይ የጨከነ ገመድ የለም? ምን ዓይነት ገመድ አትበለኝ:: የእንጀራ ገመድ የኑሮ ገመድ የትምህርት ገመድ የፈለግኸው ገመድ በለው:: እሱን ተጠምጥመህ ይዘህ ወደ አንዳች ቦታ ለመድረስ የተማመንክበት ተስፋህን ሙሉ በሙሉ የጣልክበት ገመድ የለም? ድንገት ተበጥሶ ዙሪያው ገደል አልሆነብህም? ሰዎች ማንም ላይ ያልተበጠሰ ገመድ አንተ ላይ ሲበጠስ አይተው "ምኑ ዕድለ ቢስ ነው?" ብለው የተደነቁብህ እንደ ቅዱስ ጳውሎስ "ከባሕር አደጋ ተርፎ ዕባብ የነደፈው እንዴት ኃጢአተኛ ቢሆን ነው?" ብለው በትዝብት ዓይን እንዲያዩህ ያደረገ በሕይወትህ ሳታስበው ተበጥሶ ዙሪያው ገደል የሆነ ሥፍራ ላይ የጣለህ የሕይወት ገመድ ይኖር ይሆናል::

በዕድልህ አትማረር በሕይወትህ ድንገት የሚበጠስብህ ገመድ የምትወድቅበት ሳይሆን ክንፍ አውጥተህ የምትበርበት ነው:: ፈጣሪ የተማመንክበትን የምታየውን ገመድ እንዲበጠስብህ ከፈቀደ ያላየኸውን ክንፍ ሊሠጥህ እንጂ ሊጥልህ አይደለም:: የሕይወትህን ገመድ የተበጠሰበትን ቀን "እግዚአብሔር ለመልካም አሰበው" ብለህ እንደ ዮሴፍ ታመሰግንበታለህ::
ገመድህን የሚበጥሰው ከገደል ሊጥልህ ሳይሆን በክንፍ አብቅሎ ሊተክልህ ነው:: የሚተክልህ በበረሃ ሳይሆን በእግዚአብሔር ቤት ውስጥ ነው:: ተራ ተክል የምትሆን እንዳይመስልህ:: የሃይማኖት ተክል (ተክለ ሃይማኖት) ትሆናለህ:: ተክለ መንፈስ ቅዱስ ተክለ ወልድ ተክለ አብ ትሆናለህ:: አብ የተከለው ደግሞ አይነቀልም!

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
ታኅሣሥ 24 2013 ዓ ም
92 viewsⓋⓐⓣⓛⓚⓐⓝⓐ, 04:18
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-08-27 22:15:52 እዚህ ላይ የሚያስደንቀው የማርያም ዝምታ ነው፡፡ ማርታ ስትከስሳት ጌታችን መልስ ሠጠላት እንጂ ማርያም አንድም ቃል አልተነፈሰችም፡፡ ‹ቃሉን መስማት ይበልጣል ብዬ ነው!› ብላም አልተመጻደቀችም፡፡ ዝም አለች፡፡ በእርግጥ እኅትዋ ስትከስሳት ምን ተሰምቷት ይሆን? በአፍዋ ዝም ብላ በልብዋ እየተሳደበች ይሆን እንዴ? አባ ሕርያቆስ በቅዳሴው ‹የለም በውስጥዋም ክፉ ሃሳብ አልነበረም› ይላል፡፡ ‹እንግዲህ እንደ ማርያም አርምሞና ትዕግሥትን ገንዘብ እናድርግ› (ናጥሪ እንከ አርምሞ ወትዕግሥተ ከመ ማርያም) በማለት በአፍዋ አርምሞን (ዝምታን) ብቻ ሳይሆን በልብዋም ትዕግሥትን ገንዘብ አድርጋ እንደነበር ይመሰክራል፡፡

ያስደንቃል! እጅግ በምታከብረው ጌታ ፊት የገዛ እኅትዋ ስትከስሳት ማርያም እንዴት አልተበሳጨችም? ቢያንስ በልቧ እንኳን እንዴት አላጉረመረመችም? መልሱ ግልጽ ነው፡፡ ማርያም ሌላ ዓለም ውስጥ ስለነበረች ነው፡፡ ከጌታችን አንደበት የሚወጣውን አምላካዊ ቃል ሰምታ ልቧ ተሰውሯል ፤ አካልዋ በቤት ውስጥ ቢሆንም ኅሊናዋ ወደ ሰማያት ከፍ ብሏል፡፡ በጌታችን ቃል ልቡ የተሰበረ ሰው ደግሞ እንኳን ቢሰድቡት ቢደበድቡትም አይሰማውም፡፡ ቅዱስ እስጢፋኖስ በድንጋይ መወገሩ ገለባ የመሰለው ጌታችንን እያየ ስለነበር ነው፡፡ ቅዱስ ያሬድ የአፄ ገብረ መስቀል ጦር እግሩ ላይ ተሰክቶ ምንም ያልታወቀው በእግዚአብሔር ቃል ልቡ ስለተመሠጠ ነው፡፡ ማርያምም ልቧ በቃሉ ስለተመሰጠ በእኅቷ ንግግር ምንም አልተሰማትም፡፡

★ ★ ★

ከብዙ ወራት በኋላ ጌታችን ዳግመኛ ወደነማርታ ሀገር ወደ ቢታንያ ተመልሶ መጣ፡፡ በዚህ ጊዜ ግን እንግዳ ሆኖ የሔደው ወደነማርታ ቤት ሳይሆን ወደ ለምጻሙ ስምዖን ቤት ነበር፡፡ የቢታንያው ስምዖን ለጌታችን የራት ግብዣ አዘጋጅቶ ነበር፡፡ በዚህ ዕለት ታዲያ የቢታንያ ነዋሪዎች እንደመሆናቸው ማርታ ፣ ማርያምና አልዓዛርም በስምዖን ቤት ተገኝተው ነበር፡፡

ማርያም ጌታችን ባስተማራት ትምህርት ልቧ ተሰብሮ ፣ የምትኖርበትን የኃጢአት ኑሮ ተጸይፋ ነበር፡፡ ስለዚህ ዋጋው እጅግ ውድ የሆነ የአልባስጥሮስ ሽቱ ገዝታ ወደ ስምዖን ቤት ገሰገሰች፡፡ ከጌታችን እግር ሥር ተደፍታም በዕንባዋ አጠበችው ፣ በፍጹም ጸጸት ወደ ፈጣሪዋ ተመለሰች፡፡ የአስቆሮቱ ይሁዳ ‹ይህ ጥፋት ምንድር ነው?› ብሎ ለሽቱው ብክነት ተቆጨ ‹ለድሆች ቢሠጥ ይጠቅም ነበር› የሚል የውሸት ምክንያትም አቀረበ፡፡

ማርያም ፈተናዋ ብዙ ነው ፤ ቃሉን ስትማር እኅትዋ ተቸቻት ፤ ንስሓ ስትገባ ደግሞ ይሁዳ ተነሣባት፡፡ ማርታ ቃሉን ከመስማት ይልቅ ‹ለምግብ ሥራ ቅድሚያ እንሥጥ› ብላ እንደነበር ይሁዳም ‹ለነዳያን አገልግሎት ቅድሚያ ይሠጥ› አለ፡፡ (ይሁዳ ጌታችን ሲያስተምር ‹እናትህና ወንድሞችህ መጥተዋል እያለ ትምህርት እንዲቋረጥ የሚታገል ሰው እንደነበር ልብ ይሏል› ማቴ.12፡46 ትርጓሜ)

ይሁዳ ሲናገር ማርያም እንደ ልማዷ ዝም አለች ፤ ጌታችንም እንደ ልማዱ መልስ ሠጠላት፡፡ እርስዋንም ‹ኃጢአትሽ ተሰርዮልሻል› ብሎም አሰናበታት፡፡ ማርያም በተማረችው ቃል የንስሓ ፍሬ አፈራች ፤ የኃጥኡን መመለስ ለሚወደው ጌታ ዕንባዋ አቀርባ ከማርታ በላይ አስተናገደችው፡፡ መስተንግዶዋም ከማርታ ብቻ ሳይሆን ታላቅ ግብዣ ካደረገለት ከለምጻሙ ስምዖንም የበለጠ ሆነ፡፡ ጌታችንም ለለምጻሙ ስምዖን ከእርሱ መስተንግዶ የእርስዋ መስተንግዶ ምን ያህል የበለጠ እንደሆነ አነጻጽሮ ነግሮታል፡፡ (ሉቃ. 7፡44-46)

ከላይ እንደተገለጸው ማርያም እንዲህ ስትጸጸትና ኃጢአትዋ ሲሰረይላት ማርታ በለምጻሙ ስምዖን ቤት ውስጥ በእንግድነት ተገኝታ ነበር፡፡ ምን እያደረገች ይሆን? የእኅትዋን መመለስ በመገረም እያየች ይሆን? ወይስ በቤትዋ ያመለጣትን ትምህርት ከጌታችን እግር ሥር ቁጭ ብላ እየሰማች ይሆን? ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ መልሱን እንዲህ ሲል ጽፎልናል፡፡ ‹‹በዚያም እራት አደረጉለት፤ ማርታም ታገለግል ነበር›› (ዮሐ. 12፡2)

ለማመን ያስቸግር ይሆናል፡፡ አዎን ማርታ በሰው ቤትም እንኳን አላረፈችም፡፡ በቤትዋ እንዳደረገችው በስምኦን ቤትም በአገልግሎት ላይ ነበረች፡፡ እኅትዋ ስትማር ጓዳ የነበረችው የዋኋ ማርታ ምንም እንኳን ጌታችን አገልግሎቷን ሳይነቅፍ የሚበልጠው ከእግሩ ሥር መገኘት እንደሆነ የነገራት ቢሆንምም አሁንም መልካሙን ዕድል አልመረጠችም፡፡ እኅትዋ ስትማር ታገለግል እንደነበረች ፣ የእኅትዋ ኃጢአት ሲሰረይም እስዋ አገልግሎት ላይ ናት፡፡ ማገልገል መልካም ነው ፤ እኛ በአገልግሎት ስንባክን ፣ ሌሎች ወደ እግዚአብሔር ሲቀርቡ ኖረዋል፡፡

ንስሓ ገብተው ወደ ሥጋ ወደሙ ሲቀርቡም እኛ አገልግሎት ላይ ከሆንን እንደ ማርታ ዕድላችንን ያልተጠቀምን ምስኪኖች ነን፡፡ የሚያሳዝነው ማርታ አላወቀችም እንጂ የስምዖን ቤት ግብዣ ከጌታ እግር ስር ለመቀመጥ የመጨረሻ ዕድሏ ነበር፡፡ ምክንያቱም ጌታችን ከዚያች ቀን በኋላ በጥቂት ቀናት ልዩነት ተሰቅሎ ሞቶአል፡፡ ከዚያም ሞትን ድል አድርጎ ተነሥቶ በአርባኛው ቀን አርጓል፡፡ ማርያም የመጀመሪያ ዕድሏን ለመማር ፣ የመጨረሻ ዕድሏን ደግሞ ለንስሓ ተጠቀመችበት፡፡ ማርታ ግን ‹ታገለግል ነበር›፡፡

"ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ"
34 viewsⓋⓐⓣⓛⓚⓐⓝⓐ, 19:15
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-08-27 22:15:34 +++ ማርታም ታገለግል ነበር+++

ማርያምና ማርታ እኅትማማቾች ናቸው፡፡ ‹ኢየሱስም ማርታንና እኅትዋን ፣ አልዓዛርንም ይወድ ነበር› (ዮሐ. 11፡5) ስለዚህም በቢታንያ በሚገኘው ቤታቸው እንግዳ ሆኖ ተገኘ፡፡ እጅግ ለሚወዱት ጌታ ፍቅራቸውን ለመግለጽ እኅትማማቾቹ ይሻላል ብለው ያሰቡትን ሁለት የተለያየ ዓይነት አቀባበል አድርገውለት ነበር፡፡ ማርታ ለምትወደው እንግዳዋ ምግብ ለማቅረብ ብዙ ተጨንቃ በጓዳ ሥራ ላይ ተወጠረች፡፡ ‹ለታላቁ ጌታ ምን ላቅርብለት ይሆን?› ብላ ተጠበበች፡፡
መቼም የምናከብረው ሰው እንግዳ ሆኖ ሲመጣ ሙያውም ሊጠፋብን ይችላል፡፡

ማርታም የገጠማት ይኼው ነው ፣ ምኑን ከምኑ አድርጋ እንደምታቀርብ ግራ ገባት ፤ ጌታችን እንዳለው ‹በብዙ ነገር ተጨነቀች ታወከች›፡፡

እኅትዋ ማርያም ግን ሃሳቧን ጥላ ቃሉን ልትሰማ ከጌታ እግር ሥር ቁጭ አለች፡፡
ማርያምን በማርታ ዓይን ሆነን ስናያት እንግዳ ሲመጣ ሥራ ላለመሥራት ከእንግዳ ጋር ከሚቀመጡ ሥራ ጠል እኅቶች አንድዋን ትመስለናለች፡፡

እኅትዋ ከጭስ ጋር ስትታገል ፣ ምን ልሥራ ብላ ስትርበተበት እስዋ በቤትዋ እንደ እንግዳ መቀመጥዋን ስናይ ‹ምን ዓይነቷ ግፍ የማትፈራ ናት› ብለን መታዘባችን አይቀርም፡፡

ማርታ ግን ታዝባ ዝም አላለችም፡፡ ‹‹ጌታ ሆይ፥ እኔ እንድሠራ እኅቴ ብቻዬን ስትተወኝ አይገድህምን? እንኪያስ እንድታግዘኝ ንገራት አለችው። ጌታችንም ኢየሱስም መልሶ፦ ማርታ፥ ማርታ፥ በብዙ ነገር ትጨነቂአለሽ ትታወኪማለሽ፥ የሚያስፈልገው ግን ጥቂት ወይም አንድ ነገር ነው፤ ማርያምም መልካም ዕድልን መርጣለች ከእርስዋም አይወሰድባትም አላት።››

ሉቃ. 10፡38-42 በእኛ ግምገማ ማርታ የበለጠ ለጌታ ፍቅር ያላት ቢመስለንም ጌታችን ግን የማርታን በፍቅር ለሥራ መድከም ሳይነቅፍባት የማርያም ምርጫ ግን ‹የማይቀማ በጎ ዕድል› መሆኑን ተናገረ፡፡ እንዴት ሊሆን ይችላል?

በእኅትማማቾቹ ቤት የተገኘው ሌላ እንግዳ ቢሆን ኖሮ ማርያም ያደረገችው የሚያስወቅስ ይሆን ነበር፡፡ በእነርሱ ቤት የተገኘው ግን የሰማይና የምድር ፈጣሪ ነው፡፡

እርሱ ደግሞ የሚቀበሉት እንጂ የሚሠጡት እንግዳ አይደለም፡፡ ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ እንዳለው ‹‹ማርታ ጌታ ራሱ የፈጠረውን ምግብ በገበታ ልታቀርብለት›› ተጨነቀች፡፡(Martha gave him to eat: viands which He had created she placed before Him)
@deaqonhanok
የዋኋ ማርታ ያላወቀችው ነገር እርሱ ደስ ብሎት የሚበላው ምግብ እርስዋ የምትሠራው ዓይነት ምግብ እንዳልሆነ ነው፡፡

እንደ ሐዋርያቱ ቀርባ ብትጠይቀው ኖሮ ፡- ‹‹አንቺ የማታውቂው የምበላው መብል ለእኔ አለኝ›› ይላት ነበር፡፡

(ዮሐ. 4፡32) ምን ትጠጣለህ? ብትለው ለሙሴ እንደነገረው ‹ኃጢአተኛ ሲጸጸት ዕንባውን እጠጣለሁ› (ኃጥእ አመ ይኔስሕ ዕንባሁ እሰቲ) ብሎ ይመልስላት ነበር፡፡

አልጠየቀችውም እንጂ መራራ ሐሞት እስኪጠጣ ድረስ በሰው ልጅ ፍቅር ስለተጠማው ጕሮሮው ይነግራት ነበር፡፡

(‹ሰላም ለጕርዔከ በጽምአ ፍቅረ ሰብእ ሐማሚ፡፡ እስከ ስቴ ሐሞት ጥዕመ ወዘወይነ ትፍስሕት ከራሚ› እንዲል) የእርሱ ምግብና መጠጥ የሰው ልጅ ልቡን ሠጥቶ ወደ እርሱ መመለሱ ነው፡፡

ማርያም ግን የማይቀሟትን በጎ ዕድል መረጠች፡፡ ከራሱ ከጌታችን እግር ሥር ቁጭ ብሎ ከመማር በላይ ምን ዕድል አለ? ፈጣሪ ሲናገር መስማትስ እንዴት መታደል ነው? እርሱ የሚናገረው ቃል እኮ መለኮታዊ ቃል ነው! ከጌታ የሚወጣው ቃል የሚሠራና ሕያው የሆነው የራሱ የእግዚአብሔር ቃል ስለሆነ

‹ነፍስንና መንፈስንም ጅማትንና ቅልጥምንም እስኪለይ ድረስ ይወጋል፥ የልብንም ስሜትና አሳብ ይመረምራል› (ዕብ. 4፡12) እርሱ የሚናገረው ቃል ሙቱን አፈፍ አድርጎ ያስነሣል ፣ ለምጻሙን ያነጻል፡፡

አስረው እንዲያመጡት ከአይሁድ የተላኩት የሮም ወታደሮች እንኳን ከትምህርቱ ጣዕም የተነሣ ተደንቀው ‹‹እንደዚህ ሰው ማንም እንዲሁ ከቶ አልተናገረም›› ብለው ባዶ እጃቸውን ተመልሰዋል፡፡

(ዮሐ.7፡46) የኤማሁስ መንገደኞችም ‹በመንገድ ሲናገረን ልባችን ይቃጠል አልነበረምን?› ብለዋል፡፡(ሉቃ. 24፡32) ይህ የጌታችን ድንቅ ትምህርት ማርታ ማድቤት ሆና አመለጣት፡፡

‹ብዙ ነቢያት ሊሰሙት ወድደው ያልሰሙትን› ቃል የመስማት ዕድል ቤቷ ድረስ መጥቶላት እርስዋ ግን ሥራ ላይ ነበረች፡፡ እንደ ሙሴ ወደ ተራራ ሳትወጣ ፣ በደመና ሳትከበብ ቤቷ ድረስ እግዚአብሔር መጥቶ ሊያናግራት ሲል እስዋ ግን ምግብ እየሠራለች ነው፡፡

‹ማርታ ግን አገልግሎት ስለበዛባት ባከነች› ይላል፡፡ ይህ ቃል በእግዚአብሔር ቤት ለምናገለግል ፣ የማርታ ችግር ላለብን ሰዎች ምንኛ ከባድ ቃል ነው? ለመቅደሱ ቀርበን ከፈጣሪ ለራቅን ፣ ጠዋት ማታ በሥራ ፣ በዕቅድ ፣ በስብሰባ ተወጥረን እንደ ማርታ ብዙ ድስት ለጣድን ለእኛ ምንኛ ከባድ ቃል ይሆን? አቡነ ሺኖዳ ‹‹እስከ ዛሬ የእግዚአብሔርን ቤት አገለገልሁ ፤ የቤቱን ጌታ የማገለግለው መቼ ይሆን?›› ብለው ነበር፡፡

ቤቱን እያገለገልን የቤቱን ጌታ ማገልገል ያቃተን ፣ በአገልግሎት ተወጥረን ከጸሎት ፣ ከንስሓ ፣ ከሥጋ ወደሙና ቃሉን ለራስ ብሎ ከመስማት ለተለየን ሰዎች እጅግ ከባድ ቃል ነው፡፡

እያገለገሉ ከፈጣሪ መራቅ እጅግ ከባድ ነው፡፡ እንደ ማርታ ፈጣሪ ባለበት ቤት እየኖሩ ከፈጣሪ መለየትም እጅግ የከፋ ነው፡፡

ማርያም የምትማርበትን ክፍል አጽድተን ፣ በኋላም ገበታውን አቅራቢ ሆነን የምንወደውን ፈጣሪ ሳንሰማው መቅረት እንዴት ያሳዝናል? ለሰብአ ሰገል ወደ ቤተልሔም ሔደው እንዲሰግዱ የጠቆሟቸው አይሁድ ነበሩ ፤ እነርሱ ግን ሔደው አልሰገዱለትም፡፡ ቅዱስ አምብሮስ እንዳለው ኖኅ መርከብ ሲሠራ የረዱት የቀን ሠራተኞች ነበሩ ፤ እነርሱ ግን ከጥፋት ውኃ አልዳኑም፡፡ ለፍቶ ደክሞ አገልግሎ ፣ ሌላውን አስተምሮ ፣ ቤተ እግዚአብሔርን ሠርቶ መኮነን እንዴት ያሳዝናል? እንደ መርፌ የሌላውን ቀዳዳ እየሠፋን የራሳችንን መስፋት ያቃተን ፣ እንደ መቋሚያ ለሌላው ድጋፍ እየሆንን ራሳችንን ማቆም ያቃተን ‹አገልግሎት ስለበዛብን የባከንን› ብዙዎች ነን፡፡

ማርታ ከቃሉ በመራቋ ምክንያት አገልግሎትዋን እንኳን በጸጥታ ማገልገል አልቻለችም፡፡ ብቻዋን መሥራትዋም አስቆጫት፡፡ ‹‹ጌታ ሆይ፥ እኔ እንድሠራ እኅቴ ብቻዬን ስትተወኝ አይገድህምን? እንኪያስ እንድታግዘኝ ንገራት አለችው።›› ይህ ንግግርዋ ብዙ ጉድለት እንዳለባት ያሳያል፡፡ እኅትዋ እስከሆነች ድረስ ቀስ ብላ ጠርታ ‹ምን ማድረግሽ ነው? ነይና አግዢኝ እንጂ› ልትላት ትችል ነበር፡፡ አልዓዛር በሞተ ጊዜ በለቅሶ ቤት ‹ማርያምን በስውር ጠርታ፦ መምህሩ መጥቶአል ይጠራሽማል› ብላ እንደተናገረችው አሁንም በስውር ጠርታ ልትወቅሳት ትችል ነበር፡፡

(ዮሐ. 11፡28) እርስዋ ግን በቀጥታ ለእኅትዋ ከመናገር ይልቅ እኅትዋን በጌታ ፊት አሳጣቻት ፣ ከእኅትዋ ይልቅ እርስዋ ለጌታ የበለጠ ፍቅር ያላት እንደሆነች የሚያሳይ ንግግር ተናረች፡፡ ሰው ቃለ እግዚአብሔር ሲጎድለው ጠበኛ ይሆናል፡፡ እርሱ እየሠራ የሌሎች አለመሥራት ያበሳጨዋል ፣ በቀጥታ ሔዶ ለሰው ችግሩን ከመናገር ይልቅ በተዘዋዋሪ መናገር ይቀልለዋል፡፡ የዋኋ ማርታ ለአገልግሎት ስትባክን የገጠማት ፈተናም ይኼው ነው፡፡
26 viewsⓋⓐⓣⓛⓚⓐⓝⓐ, 19:15
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-08-27 22:15:03 + ለምን ትቀናለህ? +

በዜና አበው ላይ አጋንንት አንድን መነኩሴ ለማሰናከል ሲማከሩ የሚያሳይ ታሪክ ተጽፎአል፡፡ መነኩሴው ለብዙ ዘመናት በተጋድሎ አሳልፎ ከብቃት የደረሰ መናኝ ነበር፡፡ የአጋንንቱ ጭፍራ በአለቃቸው ተመርተው ይህንን መነኩሴ ለማሳት ዘመቱ፡፡ ተራ በተራ ወደ እርሱ እየሔዱ የፈተና ወጥመዳቸውን ዘረጉበት፡፡ በዝሙት ሊፈትኑት ሞከሩ፡፡ አልተሳካም፡፡ በምግብም ሞከሩ ድል ነሣቸው፡፡ የሚያውቁትን የፈተና ስልት በተለያየ መንገድ እየተገለጹ አንዴ ሰው አንዴ መልአክ እየመሰሉ ሊጥሉት ቢሞክሩም አልቻሉም፡፡

አለቃቸው ይኼን ጊዜ በሉ እኔ የማደርገውን ተመልከቱ አላቸውና መንገደኛ መስሎ ወደ መነኩሴው ቀረበ፡፡ በጆሮው የሆነ ነግሮት ወዲያው ተሰናብቶት ወጣ፡፡ ይህንን ጊዜ አጋንንቱ እያዩት መነኩሴው መንፈሳዊ ገጽታው ተገፍፎ ፊቱ በቁጣና በንዴት ሲለዋወጥ ተመለከቱት፡፡ በዚህም ተደንቀው ምን ብለህ ነው ያሸነፍከው? ብለው አለቃቸውን ጠየቁት፡፡ እርሱም እንዲህ አላቸው፦ ‘ከአንተ ጋር ያደገውና ከአንተ ጋር የተማረው ጓደኛህ እኮ የእስክንድርያ ፓትርያርክ ሆኖ ተሾመ’ ብዬ ነገርኩትና ወጣሁ፡፡ አሁን ልቡ በቅናት እየነደደ ነው አላቸው፡፡ አጋንንቱ በደስታ ጨፈሩ፡፡

ሰይጣን የቅናትን ኃይል ጠንቅቆ ያውቃል፡፡ መጽሐፈ ቅዳሴ ሞትን ሲገልጸው ‘በሰይጣን ቅናት ወደ ዓለም የገባ’ ይለዋል፡፡ ሰይጣን በሰው ልጅ ጸጋ ቀንቶ አዳምና ሔዋንን በፈጣሪያቸው እንዲቀኑና አምላክ መሆን እንዲመኙ አድርጎ ዓለምን ያመሰቃቀለ ነውና ይህንን መነኩሴ ለመጣል ለሺህ ዓመታት ብዙዎችን ወግቶ የጣለባትን ሰይፉን መዘዘበት፡፡ መነኩሴው የእኩያውን መሾም ሲሰማ ቅናቱን መቋቋም አቃተው::

ቅናት እጅግ ክፉ ኃጢአት ነው፡፡ ሰው ቢዘሙት ቢሰክር በሥጋው ነው:: ቅናት ግን በምታስተውል ነፍሱ ውስጥ የሚበቅል መርዝ ነው፡፡ ቃየልን በየዋህ ወንድሙ ላይ ያስጨከነው ቅናት ነበር፡፡ የአቤል ስኬት ለቃየል ውድቀት መስሎ ስለተሰማው በግፍ ሊገድለው በቃ፡፡

ዮሴፍ የለበሳት ቀለምዋ ብዙ የሆነ ጌጠኛ ቀሚስ በወንድሞቹ ዘንድ የመረረ ጥላቻን አትርፋለት ነበር፡፡ አንዱ አጊጦ አምሮ ሲታይ ቢሞትና ቢገላገሉት ደስ የሚላቸው የዮሴፍ ወንድሞች በየዘመኑ አሉ፡፡

ዮሴፍም አርፎ አልተቀመጠም፡፡ እየሔደ ሕልሙን ይነግራቸው ነበር፡፡ ስለ ሕልሙም የበለጠ ጠሉት ይላል፡፡ ወዳጄ ሕልምህን ዝም ብለህ ለሰዎች አትዝራ፡፡ ሕልም ስልህ ተኝተህ የምታየውን ብቻ ማለቴ አይደለም፡፡ ራእይህን ፣ ተስፋህን ዕቅድህን ሲያውቁ የሚንገበገቡ የዮሴፍ ወንድሞች በየዘመኑ አሉ፡፡ ፍቺው ባይገባቸውም ባልተፈታ ሕልም ይጠሉሃል፡፡ ምንም ነገር ሳታደርግ እንኳን "ለምን አለምከው?" ብለው ጥርስ ይነክሱብሃል፡፡ ዮሴፍ ግን ይኼ ስላልገባው ነገራቸው፡፡ ወዳጄ አንተም ሕልምህን እንደ ዮሴፍ በየዋህነት የምትዘራ ከሆንህ እንግዲህ የዮሴፍ አምላክ ይጠብቅህ፡፡

ቅናት እጅግ ከባድ ነው፡፡ እረኛው ዳዊት ጎልያድን የገደለ ዕለት የተዘፈነለት መዘዘኛ ዘፈንም ነበረ፡፡ ‘ሳኦል ሺህ ገደለ ዳዊት እልፍ ገደለ’ ብለው ዘፈኑለት፡፡ ይህች ዘፈን በሳኦል ጆሮ ስትደርስ ዳዊት ላይ ብዙ ጦር አስወረወረች፡፡ ሳኦሎች ሌላ ሰው ከእነርሱ በላይ ሲመሰገን የሰሙ ዕለት በቅናት ታውረው ገበታ ላይ ሳይቀር ሰይፍ ይመዛሉ፡፡

የጠፋው ልጅ ወንድምን አስበው፡፡ (ሉቃ 15:20) ወንድሙ ከጠፋበት ተመልሶ ደስታ ሲደረግ እርሱ ግን ከፍቶት ውጪ ቁጭ አለ፡፡ ወዳጄ ቅናት ከቤተ ክርስቲያንና ከእግዚአብሔር መንግሥት ያስወጣል፡፡ የሌላው ስኬት ካበሳጨህ እንደጠፋው ልጅ ወንድም ውጪ ቁጭ ብለህ አፈር እየጫርክ ‘እምቢየው አልገባም’ እያልክ እያልጎመጎምክ ትቀራለህ፡፡

ክርስቶስ ላይ አይሁድ ያቀረቡት ትችት ሁሉ ለሕግ ከመቆርቆር ሳይሆን ከቅናት ነበር፡፡ ጲላጦስ እንኳን ‘በቅናት አሳልፈው እንደሠጡት ያውቅ ነበር’ ይላል፡፡ አንዳንዴ ሰዎች ቅናታቸውን በሌላ ነገር እንደ አይሁድ ሸፍነው ትችት ያቀርባሉ፡፡ ለእግዚአብሔር ሕግ እንደተቆረቆሩ ፣ ለሥርዓቱ እንዳዘኑ መስለው ውስጣቸው ያለውን ቅናትና ጥላቻ ያንጸባርቃሉ፡፡

የሰንበት መሻር ፣ ለቄሣር ግብር መከፈል ፣ የመቅደሱ በሦስት ቀን ፈርሶ መሠራት እንዳንገበገባቸው እርር እያሉ ቢናገሩም እውነታው ግን ቅናት ነው፡፡ ‘የቤትህ ቅናት በላኝ’ እንዳለው ጌታ በየዘመኑ የሰዎች ቅናት ብዙ ንጹሐንን ትበላለች፡፡

ወዳጄ በሌላው ትቀና እንደሆን አሁኑኑ ከዚህ ውስጥን በልቶ ከሚጨርስ ካንሰር ራስህን አድን፡፡

ራስህን ከሌሎች ጋር አታወዳድር፡፡ በምድር ላይ እግዚአብሔር የፈጠረው አንተን የሚመስል ሌላ ሰው የለም፡፡ ካንተ ቀድሞም በትክክል አንተን የሆነ ሰው አልተፈጠረም ለወደፊትም አይፈጠርም፡፡ እግዚአብሔር ቀድሞ ያልሠራው ደግሞም የማይሠራው ምርጥ ዕቃው ነህና ራስህን ከሌላ ጋር አታወዳድር፡፡

ለአንተ ብቻ የሠጠው ጸጋ አለና ሌሎችን መመልከት ትተህ ውስጥህ ያለውን ውድ ማንነት ቆፍረህ አውጣ፡፡ ያንተ ሕይወት ቁልፍ የተቀበረው አንተው ውስጥ ነው፡፡ ሌሎችን ረስተህ ወደ ራስህ ጠልቀህ ግባ፡፡ መብለጥ ከፈለግህም አሁን ያለውን ራስህን ብለጠውና ሌላ ትልቅ አንተን ሁን፡፡

በቅናት እንዳትቃጠል ሌሎችን ሰዎችንም ውደዳቸው፡፡ ከወደድሃቸው ‘ፍቅር አይቀናም’ና የእነርሱ ስኬት የደስታህ ምንጭ ይሆናል፡፡ የቅናት ስሜት ሲሰማህም ‘ቀናተኛ ልቤን ፈውስልኝ’ ብለህ ለምነው፡፡

‘በአገባብ እንመላለስ፤ በዘፈንና በስካር አይሁን፥ በዝሙትና በመዳራት አይሁን፥ በክርክርና በቅናት አይሁን’ ሮሜ 13፡13

ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
አለታ ወንዶ ኢትዮጵያ
ጥር 5 2013 ዓ.ም.

መነሻ ሃሳብ:- የአንድ በቅናት ጦስ ሊያበሩ ሲችሉ ብዙ ዋጋ የከፈሉ ቤተሰቦች ታሪክ

ለተጨነቀች ነፍስ ዕረፍት የሆነው የእግዚአብሔር ቃል ለሁሉ ይዳረስ ዘንድ :: እኔም ለእናንተ ከሰበክሁ በኁዋላ የተጣልሁ እንዳልሆን ስለ እኔ ጸልዩ
31 viewsⓋⓐⓣⓛⓚⓐⓝⓐ, 19:15
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-08-26 21:40:47 ††† እንኳን ለቅዱሳት አንስት ኄራኒ ሰማዕት: ንግሥተ ሳባ እና ንግሥት ዕሌኒ ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። †††

††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †††

††† ቅድስት ኄራኒ ሐዋርያዊት ሰማዕት †††

††† ይህቺ ቅድስት ወጣት መልክ ከደም ግባት: ምግባር ከሃይማኖት: ስም ከመልካምነት የተባበረላት ሰማዕት ናት:: #ኄራኒ ማለት "ሰላማዊት: የተወደደች" ማለት ነው:: አንድም በጥሬው "ሰላምና ፍቅር" ማለት ነው::

ቅድስት ኄራኒ በመጀመሪያው መቶ ክ/ዘመን በታናሽ እስያ የንጉሥ #ሉክያኖስ ልጅ ናት:: ከተወለደች ጀምሮ ስለ ክርስትና ሰምታ አታውቅም:: ምክንያቱም አባቷ ጣዖት አምላኪ ከመሆኑ ባለፈ ክርስቲያኖችን ይቀጣ ስለ ነበር ነው::

ልጁን ማንም እንዳያገኛት ሲል ንጉሡ ለቅድስት ኄራኒ ቤተ መንግስት ሠራላት:: ማንም እንዳይገባ በዙሪያው 12 አጥር አጠረበት:: ጣዖቶቹን እንድታጥን አገልጋዮችንም ሾመላት::

ምናልባት አጥር ሰውን ሊከለክለው ይችላል:: #እግዚአብሔር ግን እግዚአብሔር ነውና ምንም አይከለክለውም:: ጌታ ደግሞ ይህቺን ወጣት ለወንጌል አገልግሎት ይፈልጋታል:: አንድ ቀን አባቷ: ልጁ ምሑር እንድትሆንለት አለ የተባለ ሽማግሌ ፈላስፋ ቀጠረላት::

ጥበበ እግዚአብሔር ማለት ይሔ ነው:: አባቷ ይሕ ሽማግሌ ማንን እንደሚያመልክ አልተረዳም:: አረጋዊው እጅግ የተዋጣለት ክርስቲያን ነው:: ግን ማንም አያውቅበትም:: አረጋዊው ቅድስት ኄራኒን ዝም ብሎ ሊሰብካት አልወደደም::

መጀመሪያ በስነ ምግባር አነጻት:: ቀጥሎ ግን "ጌታ ሆይ! ጐዳናህን ምራት" እያለ ይጸልይላት ገባ:: ጌታችን ልመናውን ሰምቶታልና ቅድስቷ አንድ ቀን ግሩም ራዕይን አየች::

እርሷ ለማዕድ ተቀምጣ ሳለ: የምሥራቅና የምዕራብ መስኮቶቿም ተከፍተው ሳሉ: በምሥራቁ መስኮት ነጭ ርግብ በአፏ የወይራ ዝንጣፊ (ቆጽለ ዘይት) ይዛ ገባችና ማዕዷ ላይ አኑራው ሔደች:: እርሷን ተከትሎ ደግሞ ንስር በአፉ አክሊል ይዞ ገብቶ ማዕዷ ላይ ጥሎት ሔደ::

በ3ኛው ግን ቁራ: እባብ በአፉ ይዞ በምዕራቡ መስኮት ገብቶ ማዕዷ ላይ ጥሎት ወጣ:: ቅድስት ኄራኒ ያየችው ራዕይ ቢጨንቃት ሽማግሌ መምሕሯን "ተርጉምልኝ" አለችው::

እርሱም "ልጄ ሆይ! ለዘመናት ስጠብቀው የነበረ ምኞቴን ነው ጌታ ያሳየሽ:: የሕልምሽ ትርጉም እንዲህ ነው:- ነጭ ርግብ የመንፈስ ቅዱስ (የሃይማኖት) ምሳሌ ናት:: የወይራ ዝንጣፊው ደግሞ #ማሕተመ_ጥምቀት( #ሜሮን) ነው:: ቁራ የክፉ ነገሥታት ምሳሌ ሲሆን እባብ የመከራ ምሳሌ ነው::

ንስር ድል የመንሳት ምልክት ሲሆን አክሊል ደግሞ የመንግስተ ሰማያት ምሳሌ ነው:: ልጄ! ክርስቲያን ሆነሽ የሚደርስብሽን ሁሉ ጌታ አሳይቶሻል" ብሎ ተርጉሞላት ተሰናበታት::

እርሷም ወደ ምሥራቅ ዙራ ጸለየች:- "የማላውቅህ አምላክ ሆይ! ወደ እውነትህ ምራኝ" ስትል ለመነች:: በዚያች ሰዓት የእግዚአብሔር መልአክ መጥቶ አጽናናት:: የሚያጠምቃትም እንደሚልክላት ነገራት::

በዚያን ጊዜ አባቷ ገብቶ "ልጄ! ከመሣፍንቱ ላንዱ ልድርሽ ስለሆነ ምን ትያለሽ?" አላት:: "3 ቀን ስጠኝ" አለችውና ሰጣት:: ወደ ጣዖቶቹ ዕለቱኑ ወርዳ "ላግባ ወይስ ይቅርብኝ?" አለቻቸው:: ከቀድሞም በወርቅ የተለበጡ ድንጋዮች ናቸውና ዝም አሉ:: በሙሉ ቀጥቅጣ ሰባብራቸው ተመለሰች::

በዘመኑ #ቅዱሳን_ሐዋርያት(በተለይ እነ #ቅዱስ_ዻውሎስ) በሕይወተ ሥጋ ነበሩና ከቅዱስ ዻውሎስ ደቀ መዛሙርት አንዱ ቤቷ እንደ ተዘጋ ገባ:: ክርስትናን ከጥንቱ እስከ ተፍጻሜቱ አስተምሮ አጠመቃት::

በ3ኛው ቀን አባቷ "ምን መከርሽ?" ቢላት "የእኔ ምክር #መርዓተ_ክርስቶስ(ሰማያዊ ሙሽራ) መሆን ነው" አለችው:: አባቷ ደነገጠ:: እጅግ ስለ ተናደደ ወደ አደባባይ አውጥቶ: አስሮ መሬት ላይ ጣላትና በመቶ የሚቆጠሩ ፈረሶች እንዲረግጧት አደረገ::

በወቅቱ ሰው የሚጠብቀው የአካሏን ቁርጥራጭ ነበር:: ነገር ግን ጌታ ከእርሷ ጋር ነበርና ልብሷ እንኩዋ ጭቃ አልነካም:: አባቷ ንጉሥ ሉክያኖስና ሠራዊቱ ያዩትን ማመን አልቻሉም:: ሁሉም ድምጻቸውን ከፍ አድርገው "ከክርስቶስ በቀር ሌላ አምላክ የለም" አሉ:: ቅድስት ኄራኒ ምንም ሳትናገር ይህንን ሁሉ ሰው ማረከች::

ወዲያውም ንጉሡ መልእክተኛ ልኮ: የቅዱስ ዻውሎስ ደቀ መዝሙርን አስጠርቶ: ከነ ቤተሰቦቹ ተጠመቀ:: የዚህን ዓለም ክብር ንቆም ንግሥናውን ተወ:: የጸሎት ሰውም ሆነ:: የቅድስት ኄራኒ ተጋድሎ ግን ቀጠለ::

በአካባቢው የነበረ ንጉሥ መጥቶ የአባቷን መንግስት ቀማ:: እርሷንም እጅግ አሰቃያት:: እርሱ አልፎ አርማንዮስ የሚባል ንጉሥ እንዲሁ አሰቃያት:: እርሱም አለፈ:: ከእርሱ ቀጥሎ የመጣው ንጉሥ ብዙ መከራዎችን በእርሷ ላይ አደረሰ:: በጦርም ጐኗን ወግቶ ገደላት::

ከጥቂት ሰዓታት በሁዋላ ግን ልክ ከእንቅልፉ እንደሚነቃ ሰው ተነስታ ጠራችው:: በጣም ደንግጦ "አምላክሽ አምላኬ ነው" ሲል አመነ:: ከ30,000 በላይ ሠራዊቱን ይዞም ተጠመቀ::

ቅድስት ኄራኒ በቀረ ሕይወቷ በስብከተ ወንጌል እስያን አድርሳለች:: ጌታ አብርቶላት: እርሷም አብርታ: እልፍ ፍሬን አፍርታ: በዚህች ቀን ዐርፋለች:: የሐዋርያትንም: የሰማዕታትንም አክሊል ተቀዳጅታለች::

††† ንግሥተ ሳባ †††

††† ይሕቺ ኢትዮዽያዊት ከ3 ሺ ዘመናት በፊት የነበረች ደግ እናት ናት:: በሥጋዊ ደረጃ ከታንዛንያ እስከ #የመን ያስተዳደረች ስመ ጥር ንግሥት ስትሆን በመንፈሳዊው ደረጃ ደግሞ እግዚአብሔር የቀባውን ሰው ፍለጋ ወደ #ኢየሩሳሌም ተጉዛለች::

ከዚያውም አምልኮተ እግዚአብሔርን ከሥርዓተ ኦሪት ጋር አምጥታለች:: ድንግልናዋን ለታላቁ #ንጉሥ_ሰሎሞን ሰጥታ #ምኒልክን ወልዳለች:: ይህቺ ንግሥት በጌታችን (በፈጣሪ) አንደበትም ተመስግናለች:: (ማቴ. 12:42) በስምም " #ሳባ: #አዜብና #ማክዳ ተብላ ትታወቃለች:: ዛሬ ዕለተ ልደቷ ነው::

††† ቅድስት ዕሌኒ ንግሥት †††

††† ይሕቺ ቅድስት የቅዱስ #ቆስጠንጢኖስ እናቱ: የመስቀሉ ወዳጅ: የቤተ ክርስቲያን ባለውለታ የሆነች ክብርት እናት ናት:: ይህቺም ቅድስት የተወለደቺው በዚሁ ዕለት ነው::

††† የቅዱሳት እናቶቻችን አምላክ እህት እናቶቻችንን ከክፋትም: ከጥፋትም: ይሠውርልን:: ለሃገርም: ለሃይማኖትም የሚጠቅሙ ሴቶችንም ጌታ አይንሳን:: በረከታቸውም ይደርብን::

††† ነሐሴ 21 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.ተዝካረ ፍልሠታ ለማርያም ድንግል (6ኛ ቀን)
2.ቅድስት ኄራኒ ሐዋርያዊት (ሰማዕት)
3.ቡርክት ንግሥተ ሳባ (ልደቷ)
4.ቅድስት ዕሌኒ ንግሥት (ልደቷ)

††† ወርኀዊ በዓላት
1.ቅድስት ድንግል እግዝእትነ ማርያም ወላዲተ አምላክ
2.አበው ጎርጎርዮሳት
3.አቡነ ምዕመነ ድንግል
4.አቡነ አምደ ሥላሴ
5.አባ አሮን ሶርያዊ
6.አባ መርትያኖስ ጻድቅ

††† " #ንግሥተ_አዜብ በፍርድ ቀን ከዚህ ትውልድ ጋር ተነስታ ትፈርድበታለች:: የሰሎሞንን ጥበብ ለመስማት ከምድር ዳር መጥታለችና:: እነሆም ከሰሎሞን የሚበልጥ ከዚህ አለ::" †††
(ማቴ. 12:42)

††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††
81 viewsⓋⓐⓣⓛⓚⓐⓝⓐ, 18:40
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-08-26 20:28:53 እሺ ብትሉ…

ልጆቼ! እስኪ ምላሴን ላሰናብትባችሁና እናንተም በትዕግሥት አድምጡኝ! የቤት ሠራተኛ አላችሁ እንበል፡፡ ይህቺ የቤት ሠራተኛችሁ የለበሰችውንና በወጥ፣ በአመድ እንዲሁም በሌላ ቆሻሻ እድፍ ያለ ልብሷን ትለብሱ ዘንድ ትፈቅዳላችሁን? በእርግጠኝነት አትፈቅዱም፡፡ ግን የብዙዎቻችን ሰውነት ከዚህ ልብስ በላይ መቆሸሽዋስ ታውቃላችሁን?

ልጆቼ! ንግግሬ በጣም እንደሚያሳምም አውቃለሁ፤ ግን ምን ላድርግ? የተስተካከለ ሕይወት ቢኖረን እንዲህ የምናገር ይመስላችኋልን? በፍጹም! አንድ የቆሰለ የሰውነት ክፍል ቢኖራችሁ ሐኪሙ ይህን ቁስላችሁ በጣቱ ሳይነካካ ማከም ይችላልን? አይችልም! እኔም እንዲህ ቁስላችሁን ካልነካካሁት በስተቀር ማከም አልችልም፡፡ ለነገሩ ሰው ሰውነትህን አትንካ ማለት ይቻላልን አይቻልም! ታድያ እኔና እንናተ እኮ አንድ አካል ነን፡፡ በክርስቶስ አንድ ኾነን የለምን? እንግዲያውስ ንግግሬን አትጥሉት፤ ክፉ ግብራችሁን እንጂ፡፡

ችግሩ ከማን ነው ከእኛው ወይስ ከቆሻሻው? አንድ ወደ ትዕይንት (ቲያትር) ቤት የሄደ ወጣት ገላዋን ገላልጣ የምትተውን ተዋናይትን አይቶ ዝሙትን መፈጸም የማያስብ ማን ነው? ደጋግሞ የዝሙት ዘፈንን የሚሰማ ሰው ዝሙትን ከመፈጸም መቋቋም እችላለሁ የሚል ማን ነው? ቀኑን ሙሉ የዝሙት ጽሑፎችን ሲያነብ የሚውል ሰው ዝሙትን ከመፈጸም መጠበቅ እችላለሁ የሚል ማን ነው?

ልጆቼ! ትዕይንቱን እያየነው፣ ዘፈኑን እየዘፈንነው፣ መጽሐፉንም እያነበብነው ኾኖም ግን መፍትሔ ካላገኘንበት ችግሩ እየባሰ የሚሄድ አይደለምን? እኛ ፈቃደኞች ከኾንን ግን መፍትሔው በሥጋችን ላይ ካለው ደዌ በላይ በጣም ቀላል ነው፡፡ ምክንያቱም የሥጋችን ቁስል ሐኪም፣ መድኃኒት፣ ጊዜ ያስፈልጓል፡፡ የነፍሳችንን ቁስል ግን ፈቃድ በቂ ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜ እግዚአብሔርን የማያውቁ አሕዛብ ከእኛ በላይ በንጽሕና ሲኖሩ ሳይ በጣም አፍራለሁ፡፡ እንግዲያውስ ልጆቼ እንመለስ፡፡ ያቆሸሹንን ነገሮች እንጣላቸው፤ እንቁረጣቸው፤ እናስወግዳቸው፡፡ ሰነፎች አንሁን፡፡

ውሳኔው የእኛው ነው፡፡ መጽሐፍ ሲናገር “እሺ ብትሉ ለእኔም ብትታዘዙ የምድርን በረከት ትበላላችሁ፤ እምቢ ብትሉ ግን ብታምፁም ሰይፍ ይበላችኋል” ይላል /ኢሳ.1፡19-20/፡፡ ስለዚህ ሁሉም ነገር በእኛ እሺታና እምቢታ የተወሰነ ነው ማለት ነው፡፡ የምንኮነነውም የምንመሰገነውም በዚሁ መሠረት ነው ማለት ነው፡፡ መድኃኒዓለም በመንግሥቱ በመጣ ጊዜ ኑ እናንተ የአባቴ ብሩካን ከሚላቸው ጋር በቸርነቱ ይደምረን አሜን፡፡

ምንጭ፦ ሰማዕትነት አያምልጣችሁ መጽሐፍ በ ገብረ እግዚአብሔር ኪደ
65 viewsⓋⓐⓣⓛⓚⓐⓝⓐ, 17:28
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-08-26 20:28:39 ለመጸለይ ትጋት ላለመጸለይ ምክንያት ለሌለኝ ለእኔ ጸልዩልኝ!
━━━━━━━༺✞༻━━━━━━

ሰው "የማትጸልየው ለምንድነው?" ሲባል ቀዳሚ መልሱ "ጊዜ ስለሌለኝ" የሚለው ነው። በጎውን መንገድ የሚያሳዩት ግን ይህን ይላሉ "የማንጸልየው ጊዜ ስለሌለን ሳይሆን ጊዜው የሌለን ስለማንጸልይ ነው!"

ምስጋናው ክቡር ልመናው ሥሙር የሆነለትማ ጸሎቱ ውኩፉ ኃጢዓቱ ግዱፍ ጊዜውም ትሩፍ ነው! ከሰዎች ጋር የሚያወራበትን ጊዜ የሚያሳጥር ፡ ከአምላኩ ጋር ለመነጋገር የሚጥር ሰው እንዴት ያለው "ዕድላም" ነው እናንተ! ከንግግሩ የሚቀንስ ከኃጢዓቱ ይቀንልና

☞ ወዘይጸልእ ብዙኃ ነቢበ ያሐጽጻ ለኃጢዓቱ ⇨ አብዝቶ መናገርን የሚጠላ ሰው ኃጢዓቱን ያሳንሳታል【ሲራ ፱፥፮】

የበረሐ አባቶችን ጥበብ የሚነግረን መጽሐፍ እንዲህ ስላለው ንግግር የመቀነስ ዝምታን የማብዛት ሕይወት የሚከተለውን አስተማሪ የቅዱስ አርሳንዮስ ታሪክ ያስቀምጣል።

ቅዱስ አርሳንዮስ ሁል ጊዜ ተሐራሚ ሆኖ በመዓልትና በሌሊት ይጸልይ ነበር:: ሰዎች ሲያነጋግሩት እንኳ ከአምላኩ ከእግዚአብሔር ጋር ያለውን ግንኙነት ላለማቋረጥ ጸጥ ይል ነበር:: ለዚህም በኣቱን ከገዳመ አስጤክስ አስር ምዕራፍ ያህል ርቆ ያለ ሲሆን አንድ ቀን አባ መቃርዮስ "ከእኛ ርቀህ የምትኖረው ስለምነው?" ቢለው "ለእኔስ ከሰውና ከእግዚአብሔር ጋር አንድነት መኖር ባይቻለኝ ነው:: የእግዚአብሔር ፈቃድ አንዲት ስትሆን የሰው ፍፈቃዱ ግን ልዩ ልዩ ብዙም ነው"ብሎታል:: ሌሎችም አኃው ሄደው በአርምሞ እንዲህ ጸንቶ ስለመኖሩ ቢጠይቁት "I have often regretted the words I have spoken, but I have never regretted my silence ⇨ በተናገርኳቸው ቃላቶች ብዙ ጊዜ ተጸጽቼ አውቃለሁ፣ በዝምታዬ ግን በፍጹም ተጸጽቼ አላውቅም" አላቸው:: 【+ St. Arsenios the Great 】

ሰው ከሰው ጋር ከመጨዋወት እና አብሮ ከመኖር የራቀ ያህል ከእግዚአብሔር ጋር በጸሎት ለመነጋገርና አንድ ለመሆን የበቃ ይሆናልና::

ጌታችንን በምናወድስበት ጸሎትም በልቡናው ንጽሕና ተወዳጅነቱ የተመሰከረለትን አበ ልሳናት ባህረ ጥበባት ቅዱስ ዮሐንስን የሚያነሳ ይህን እጅግ ጠቃሚ ተማጽኖ እናገኛለን ፦

ሰላም ለአፉከ ለዮሐንስ ዘሰዐሞ፣
ንጽሐ ሕሊናሁ ወልቡ ለዓይነ ፍትወትከ ሶበ አደሞ፣
ኢየሱስ ክርስቶስ መፍቀሬ የዋሃት እምተቀይሞ፣
ጸግወኒ ማዕፆ አፍ እንተ ይእቲ አርምሞ፣
ለትዕግሥትከ ከመ አእምር ዐቅሞ።

ጌታዬ ኢየሱስ ሆይ፤ ዮሐንስን ለሳመው መለኮታዊ አፍህ ሰላምታ ይገባል። የልቡናው ንጽሕና በፊትህ ተወዳጅነትን አግኝቷልና። ፈጣሪዬ ክርስቶስ ሆይ፤ ቅያሜ በአንተ ዘንድ ቦታ የለውም ቸርነት ግን የባሕርይህ ነው። ስለዚህ የትዕግሥትህን መጠን (ጥቅም) አውቅ ዘንድ። አፌም ክፉ ከመናገር ይቆጠብ ዘንድ የዝምታ ቁልፍ ስጠኝ።【መልክአ ኢየሱስ】

እንግዲህ በጎ ዘመን፡ መልካም ቀን፡ የተሻለ ጊዜ ለማየት አሁን ክፋትን እንቢኝ ተንኮልን ወዲያልኝ ብለን ብዙ እንጸልይ ብዙ ዝም እንበል፤ ባለቅኔው ሎሬት ከቆቃ የላኩትን ምክር እየሰማን እንደው ዝም ብለን እስኪ አብረን ዝም እንበል።

አብረን ዝም እንበል
·
·
·
ከሰው ኳኳታ እንነጠል
ለአንድ አፍታ እንኳ እንገለል
በእፎይታ ጥላ እንጠለል
ዝም ብለን አብረን ዝም እንበል።【ጸጋዬ ገብረመድኅን 1961 ቆቃ。】

✧ "ሕይወትን ሊወድ መልካሞችንም ቀኖች ሊያይ የሚፈልግ ሰው፥ መላሱን ከክፉ ከንፈሮቹንም ተንኰልን ከመናገር ይከልክል፤" 【፩ጴጥ· ፫፥፲】

በመጨረሻውም መጨረሻ የምናገረው ነገር ቢኖር አለመናገርን ነው።

"አርምሞሰ ተፍፃሜተ ፍፃሜ ውእቱ" ይላል መጽሐፈ መነኮሳት፤ ይሔን ሁሉ ለመናገር ጊዜ የነበረኝ ለመጸለይ ግን ጊዜ አጠረኝ፤ ለመጸለይ ትጋት ላለመጸለይ ምክንያት ለሌለኝ ለእኔ ጸልዩልኝ! ◆ ክፍለ ሥላሴ

【 የማስታውሰው ፎቶው ገዳመ ቆሮንጦስ ጌታችን የጾመበትና የጸለየበት ታላቁ ሥፍራ የተነሳሁት ነው። ከመታወሻነቱ ባለፈ ወደ ሥዕሉ ዞሮ ለመጸለይ ጊዜ እንዳጠረኝ ከሥዕሉ ዞሮ ፎቶ ለመነሳት ግን በቂ ሠዓት እደነበረኝ አስታውሶኛል 】

————————————————————
በቴዎድሮስ በለጠ ⟟ ከደብረ ብርሃን [ በተወለድኩበት ቀን ነሐሴ ገብርኤል ፳፻፲፬ ዓ.ም ]
————————————————————
48 viewsⓋⓐⓣⓛⓚⓐⓝⓐ, 17:28
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-08-26 20:27:58 ++ ራሷን እብድ ያደረገች አንዲት መነኲሲት ++
❖❖❖

ቅዱስ ጳጉሚስ ከመሠረታቸው የታቤኔዝ( ታቤኔሲዮት ) ገዳማት መካከል ከወንዶቹ ገዳማት ራቅ ብሎ የተመሠረተ የሴቶች ገዳም ነበር፡፡ በዚያም ውስጥ አራት መቶ ሴቶች መነኰሳያት ይኖሩ ነበር፡፡ በዚያ ገዳም ውስጥ ራሷን እንዳበደችና ርኩስ መንፈስ እንደያዛት የምታስመስል ድንግል ነበረች፡፡ ሌሎቹ እርሷን ከመፀየፋቸው የተነሳ አብረዋት እንኳ አይበሉም ነበር፡፡ እርሷ ግን ይህን ወደደችው ፡፡ በምግብ ማዘጋጃ ቤት ውስጥ ወዲያ ወዲህ ትንከራተታለች፡ ሌሎች የተውትንና የተናቀውን ማንኛውንም ሥራ ትሠራለች ፡ እነርሱ እንደሚሉት " የገዳሙ ቆሻሻ አስወጋጅ "ነበረች፡፡

ብጣሽ ጨርቅ ራሷ ላይ አሠር ታደርጋለች፡፡ በሕይወት ዘመኗ ሁሉ ከእህቶች መነኰሳይያት መካከል ማንም በአፏ ስታላምጥ አይተዋት አያውቅም በማዕድም ተቀምጣ አታውቅም ነበር፡፡ ከማዕድ የሚወድቀውን ፍርፋሪና የማዕድ ቤት እቃዎችን ስታጥብ ከዚያ በሚገኘው ነገር ብቻ ትኖር ነበር፡፡ ማንንም ተሳድባ ወይም ትንሽም ሆነ ብዙ አውርታ አታውቅም ምንም እንኳ ብዙ ትሰደብ ፡ ትነቀፍና ትረገም የነበረች ብትሆንም፡፡

የእግዚአብሔር መልአክ ፒተሮአም ለሚባለው ታላቅና ታዋቂ ለነበረ ታላቅ ባሕታዊ ተገለጠለትና እንዲህ አለው ፡- " እንዲህ ባለ ቦታ ስለመኖርህና ስለ ሃይማኖተኛነትህ ለምን በራስህ ትመካለህ ? ካንተ የበለጠ ሃይማኖተኛና ፍጹም የሆነችን ሴት ማየት ትፈልጋለህ ? ወደ ታቤኔሲዮት ገዳም ሴቶች ሂድ በዚያም በራሷ ላይ ዘውድ የደፋች ሴት ? ገኛለህ ፡፡ እርሷ ከአንተ የበለጠች ናት ፡ በብዙዎች መካከል ብትሆንም ልቧ ከፈጣሪዋ ከእግዚአብሔር ውጭ እንዲሄድ ፈጽሞ ፈቅዳለት አታውቅምና ፡ አንተ ግን እዚህ ተቀምጠህ በሃሳብ በተለያዩ ቦታዎች ትዞራለህ ፡፡"

ይህን ሲሰማ ከበዓቱ ወጥቶ የማያውቅ የነበረ ባሕታዊ ወደዚያ ገዳም ሄደና ወደ ገዳሙ ለመግባት ጠየቀ ፡፡ የታወቀና በእድሜው የገፋ አረጋዊ ባሕታዊ ስለነበር ወደ ሴቶቹ ገዳም እንዲገባ ፈቀዱለት ፡፡ በዚያም ሁሉንም መነኰሳይያት ያያቸው ዘንድ ጠየቀ ፡፡ ሆኖም እርሷ ግን አልመጣችም በመጨረሻም " የቀረች አንዲት አለችና ሁሉንም አምጡልኝ " አላቸው፡፡ እነርሱም " በማዕድ ማዘጋጃ ያለች አንዲት እብድ ብቻ ናት የቀረች " አሉት፡፡ እርሱም " እሷንም ጭምር አምጡልኝና ልያት " አላቸው ፡፡ ሊጠሯት ሄዱ እርሷ ግን ነገሩን አውቃው ይሁን ወይም ምናልባት ጉዳዩ ተገልጦላት መልስ አልሰጠቻቸውም ፡፡

በግድ ጎተቱና " ታላቁ አባት ፒተሮአም ሊያይሽ ይፈልጋል " አሏት ፡፡ በመጣችም ጊዜ ከራሷ ላይ ያለውን ብጣሽ ጨርቅ አሰበና ከእግሯ ላይ ወድቆ " ባርኪኝ " አላት ፡፡ እርሷም እንዲሁ ከእግሩ ላይ ወደቀችና " አባቴ ሆይ አንተ ባርከኝ " አለችው ሁሉም መነኰሳይያት ተገረሙና " አባ እንዳትሰድብህ ተጠንቀቅ እብድ ናት " አሉት :: አባ ፒተሮአምም ሁሉንም " እብዶችስ እናንተ ናችሁ እርሷ ግን የኔም የእናንተም እናት ናት ፡፡ በፍርድ ቀንም እንደ እርሷ የተዘጋጀሁና የተገባሁ ሁኜ እገኝ ዘንድ ምኞቴ ነው " አላቸው፡፡

እነዚህን ነገሮች ከዚህ አባት ሲሰሙ ሁሉም ያደረጉባትን ነገር እየተናዘዙ ከእግሩ ላይ ወደቁ ፡፡ አንዲቱ የውኃ እጣቢ አፍስሼባታለሁ ትላለች ፡ ሌላዋ ደግሞ ሌላ ነገር እንደፈጸሙባት በመናዘዝ ይናዘዙ ጀመር፡፡ እርሱም ከጸለየላቸው በኋላ ሄደ ፡፡ ከጥቂት ቀናት በኋላ በእህቶች መነኰሳይያት የሚደረግላትን ክብር መሸከም ስለከበዳት ፡ እንዲሁ ፊት በበደሏት ነገር ሁሉ ይቅርታ አድርጊልን የሚሉት ነገራቸው ስለ በዛባት ገዳሙንጥላ ጠፋች፡፡ ወዴት እንደሄደች ሆነ የት እንደ ተሰወረች ወይም እንዴት እንደሞተች ግን ማንም ያወቀ የለም፡፡
____

ዳግመኛም ቅድስት መነኩሴ ሆና ሳለ እርሷ ግን ራሷን እብድ አስመስላ ስለኖረችው ቅድስት አናሲማ እንነግራችኋለን፦ ይኽችም ቅድስት አናሲማ በደናግል ገዳም መንኩሳ በታላቅ ተጋድሎ የምትኖር ስትሆን እርሷ ግን ራሷን እብድ አስመስላ ኖረች፡፡ በሌሊትም በጾምና በጸሎት ሥጋዋን በመቅጣት ራሷን ታሠቃያለች፡፡ ሰዎችም በሚያዩዋት ጊዜ አእምሮዋን ያጣች እንደሆነች ታስመስላለች፡፡ መበለቶችም ይሰድቧታል፡፡ እጅግ ገድላኛው የሆነው ጻድቁ አባ ዳንኤል በአንዲት ዕለት ከደናል ገዳም ደርሶ ደጁን አንኳኳ፡፡ እነርሱም የከበረ አባ ዳንኤል መሆኑን ዐውቀው ከፈቱለት፡፡ ይኽችም ቅድስት አናሲማ በዚያ ራሷን እብድ አስመስላ በደጅ የምትተኛ ሴት ነበረች፡፡ የከበረ አባ ዳንኤልም እብድ መስላ በደጅ ስለተቀመጠችው ቅድስት አናሲማ እመ ምኔቷን ሲጠይቃት እብድ መሆኗን ነገረችው፡፡ አባ ዳንኤል ግን እብድ የመሰለቻቸው አናሲማ እብድ ሳትሆን በድብቅ በታላቅ ተጋድሎ የምትኖር የከበረች ቅድስት መሆኗን ነገራት፡፡

እብድ መስላ ትኖር ነበረችውና በሁሉም ዘንድ እብድ የተባለችው ቅድስት አናሲማም አባ ዳንኤል ምሥጢሯን እንደገለጠባት በጸጋ አውቃ ወዲያው ደብዳቤ ጽፋ ይኸውም ‹‹የተከበራችሁ እኅቶቼ ስላስቀየምኳችሁና ስላሳዘንኳችሁ ይቅር በሉኝ›› ብላ ጽፋ ደብዳቤውን አስቀምጣ ከንቱ ውዳሴን በመሸሽ ጥላቸው ጠፋች፡፡ እነርሱም ከዚያ በኋላ ዳግመኛ አላዩአትም፡፡ ቅድስት አናሲማም በዚያው በበረሃ ሳለች በሰላም ዐረፈች፡፡

በረከቷ ለእኛም ይድረሰን አሜን !
( @ ከበረሃውያን ሕይወትና አንደበት )

ሼር በማድረግ ለሌሎቹ አዳርሱ ፡፡

ፔጁን ላይክ ያላደረጋችሁ በማድረግ ተከታተሉ
42 viewsⓋⓐⓣⓛⓚⓐⓝⓐ, 17:27
ክፈት / አስተያየት ይስጡ