2022-06-30 08:41:35
"በውኑ ከናዝሬት ደግ ሰው ሊወጣ ይቻላልን?" ዮሐ ፩፥፵፯
ይኽንን ቃል የተናገረው እንደ ዮሐንስ ወንጌል አዘጋገብ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በመከተል አራተኛው ሰው የኾነው ናትናኤል ነው። ነገሩ እንዲኽ ነው። ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዮርዳኖስ ወንዝ ሲያልፍ መጥምቁ ዮሐንስ "እነሆ የዓለም ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ" ዮሐ፩፥፴፮ ብሎ ለደቀ መዛሙርቱ ለእንድርያስና ጴጥሮስ ለተባለው ስምዖን እርሱን እንዲከተሉ ይነግራቸዋል። አስቀድሞ "የእግሩን ጫማ ጠፍር መፍታት የማይቻለኝ"ዮሐ፩፥፳፯ ብሎ በተከበረበት ሀገር "ክርስቶስ ይበልጠኛል" ብሎ ተናገረ።ይኽንን ባለ በነጋታው ደግሞ ለዓመታት ሲያገለግሉት ለነበሩት ደቀ መዛሙርቱ "ሂዱ ከእኔ ይበልጣልና ተከተሉት" ብሎ በፍጹም ልቡ አምኖ አዘዛቸው።
ዮሐንስ ሆይ በዘመናችን ሥልጣን አለን የምንል ሰዎች አንተን ባየን፣ ቃልኽን በሰማን ጊዜ ኃፍረታችን ብዙ ነው። የበረሃው ኮከብ ሆይ በዘመናችን በታዋቂነታችን የምንመካ ሰዎችን ስራኽን በተመለከትን ጊዜ ወዮልን ወዮታ አለብን። ልክን ማወቅ በልክ መኖርን አልቻልንምና፤ የማይገባንን ስንሻ፣ ታላላቆቻችንን ስንንቅ እየኖርን ነውና።
ከእንድርያስና ከጴጥሮስ ቀጥሎ ጌታችን ፊልጶስን አግኝቶ "ተከተለኝ" አለው። በዚኽ ጊዜ ፊልጳስ "ባልንጀራኽን እንደራስኽ ውደድ"ማቴ፲፱፥፲፱ የሚለውን ቃል በተግባር ሲኖረው ተመለከትን። ፊልጶስ ጌታችንን ብቻውን ሊከተለው አልወደደም። የመሲሑን መምጣት ወዳጁ ናትናኤል እንዲጠብቅ ያውቃልና "ሙሴ በኦሪት ነቢያትም ስለእርሱ የጻፉለትን የዮሴፍን ልጅ የናዝሬቱን ኢየሱስ አገኘነው"ዮሐ፩፥፵፯ ብሎ ነገረው።
ይኽ መሲሕ እስራኤላውያን ካሉበት መካራ እንዲያወጣቸው እጅግ የሚጠብቁት ነው። አንዳንዶቹ የመሲሑ ንግሥና በዚኽ ዓለም እንደኾነ አስበው ቀኝ ጌታና ግራ ጌታ መኾንን ሲሹ አማላጅ ሲልኩም ተመልከተናል። ፊልጶስ መልካም ወዳጅ ባይኾን ወደዚኽ መሲሕ ናትናኤልን እንዲመጣ ባልጋበዘው ነበር። ዛሬ ብዙዎች ጥቂት ነገር ሲያገኙ አልያም ደግሞ ጓደኞቻቸው ጥሩ ነገር ሲገጥማቸው ከመደሰት ይልቅ የሰይጣን ባሪያ በመኾን በጓደኞቻቸው ላይ የክፋት ስራን ሲሰሩ ማየት የተለመደ ኾኖአል። ፊልጶስ ግን እኔ ያየኹትን መልካም ነገር ወዳጄም ይየው ብሎ ወደ ናትናኤል ሮጠ።
ፊልጶስ ሆይ መልካም ዜና ለመንገር ፍቅረ ቢጽን ለመተግበር የተፋጠነች እግርኽ የተባረከች ናት።
ነገር ግን ፊልጶስ እንደጠበቀው አላገኘም። ናትናኤል "እግዚአብሔር ይመስገን መሲሑ የት ነው? ውሰደኝ እባክኽ ጓደኛዬ "አይደለም ያለው። "በውኑ ከናዝሬት ደግ ሰው ሊወጣ ይቻላልን?" አለ እንጂ። ብዙዎቻችን በተለያየ መንገድ የምንጠይቃት ናትናኤላዊ ጥያቄ ናት። አንደ ሰው መልካም የሚባል ደረጃ እንደደረሰ በሰማን ጊዜ "የእንትን ሰፈር የነበረው አይደል እንዴ?" "እንትን ትሰራ የነበረችው አይደለች?" "እንዴት እንዴት እዚኽ ደረሰች" መሰል ጥያቄዎችን እናዘንበዋለን። ናዝሬት በወንበዴዎች የምትታወቅ ቦታ ነበረች በጊዜው። ስለዚኽ በአብዛኛው ሰው የናዝሬት ልጆች ወንበዴዎች ስለመኾናቸው ነው የሚገምቱት። ፊልጶስ ግን "መጥተኽ እይ" አለው። እንዴት የሚደንቅ ነገር ነው! ሰዎች ስራኽን ሰምተው ባይቀበሉኽ፣ መለወጥኽን ሰምተው ባያምኑ ጉዳዩ ያንተ አለመስራትና አለመለወጥ ሳይኾን የእነርሱ አለመቀበልና አለማመን ብቻ ነው። ስለዚኽ መጥተው ይዩኽ። አንድም ለሰዎች ስለእግዚአብሔር ፍቅር ስትነግራቸው፣ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስለተትረፈረፈው ሰላምና ጸጋ ስትመሰክር አንዳንዶች በማፌዝ አንዳንዶች በሚሰሙትና ያላግባብ ሲያገለግሉ ባዩአቸው አገልጋዮች ላያምኑኽና ላይቀበሉኽ ይችላሉ። ቁም ነገሩ መምጣታቸው እግዚአብሔርን እንዲያዩ እንጂ ሰዎችን እንዲያዩ አለመኾኑን ገና ስትጠራቸው ልትነግራቸው ይገባል። መጥታችኹ እግዚአብሔርን እዩ ልትላቸው ይገባል። ወዳጄ ናትናኤል ጌታችንን መጥቶ ሲያየው ምን ያለ ይመስልኻል? ወንበዴው? ደካማው? በፍጹም ይልቁንስ እንዲኽ አለው "መምህር ሆይ በእውነት አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ነኽ፤ የእስራኤልም ንጉሥ አንተ ነኽ"። ስለዚኽ በእውነት ከናዝሬት መልካም ነገር ይወጣልና ናዝሬት በተባለች ከኃጢአት መንደር ነጽተን እንውጣ። በእውነት ከናዝሬት መልካም ነገር ይወጣልና ከናዝሬት የወጡ ሰዎችን ከቦታቸው አንጻር ሳይኾን ከስራቸው አንጻር በማየት ልንቀበላቸው ይገባል።
ስብሐት ለእግዚአብሔር
ዲ/ን ሳሙኤል በላቸው
"ወአንቢበክሙ አንትሙ ለዘኢያንበበ አይድኡ እናንተ አንብባችሁ ላላነበበው ንገሩ"
https://t.me/getseseb
3.6K views05:41