2022-08-26 18:17:58
እንኳን ለቅዱሳት አንስት ኄራኒ ሰማዕት፣ ንግሥተ ሳባና ንግሥት ዕሌኒ ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን።
†††በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
ወንድሞቻችሁ እና እህቶቻችሁ እንዲያነቡት ተጋሩት(share it)
<3 ቅድስት ኄራኒ ሐዋርያዊት ሰማዕት <3
ይህቺ ቅድስት ወጣት መልክ ከደም ግባት፣ ምግባር ከሃይማኖት፣ ስም ከመልካምነት የተባበረላት ሰማዕት ናት። ኄራኒ ማለት "ሰላማዊት፣ የተወደደች" ማለት ነው። አንድም በጥሬው "ሰላምና ፍቅር" ማለት ነው።
ቅድስት ኄራኒ በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን በታናሽ እስያ የንጉሥ ሉክያኖስ ልጅ ናት። ከተወለደች ጀምሮ ስለ ክርስትና ሰምታ አታውቅም። ምክንያቱም አባቷ ጣዖት አምላኪ ከመሆኑ ባለፈ ክርስቲያኖችን ይቀጣ ስለ ነበር ነው።
ልጁን ማንም እንዳያገኛት ሲል ንጉሡ ለቅድስት ኄራኒ ቤተ መንግሥት ሠራላት። ማንም እንዳይገባ በዙሪያው አሥራ ሁለት አጥር አጠረበት። ጣዖቶቹን እንድታጥን አገልጋዮችንም ሾመላት።
ምናልባት አጥር ሰውን ሊከለክለው ይችላል። እግዚአብሔር ግን እግዚአብሔር ነውና ምንም አይከለክለውም። ጌታ ደግሞ ይህቺን ወጣት ለወንጌል አገልግሎት ይፈልጋታል። አንድ ቀን አባቷ ልጁ ምሑር እንድትሆንለት አለ የተባለ ሽማግሌ ፈላስፋ ቀጠረላት።
ጥበበ እግዚአብሔር ማለት ይሔ ነው። አባቷ ይህ ሽማግሌ ማንን እንደሚያመልክ አልተረዳም። አረጋዊው እጅግ የተዋጣለት ክርስቲያን ነው። ግን ማንም አያውቅበትም። አረጋዊው ቅድስት ኄራኒን ዝም ብሎ ሊሰብካት አልወደደም።
መጀመሪያ በሥነ ምግባር አነጻት። ቀጥሎ ግን "ጌታ ሆይ! ጐዳናህን ምራት።" እያለ ይጸልይላት ገባ። ጌታችን ልመናውን ሰምቶታልና ቅድስቷ አንድ ቀን ግሩም ራእይን አየች።
እርሷ ለማዕድ ተቀምጣ ሳለ የምሥራቅና የምዕራብ መስኮቶቿም ተከፍተው ሳሉ በምሥራቁ መስኮት ነጭ ርግብ በአፏ የወይራ ዝንጣፊ (ቆጽለ ዘይት) ይዛ ገባችና ማዕዷ ላይ አኑራው ሔደች። እርሷን ተከትሎ ደግሞ ንስር በአፉ አክሊል ይዞ ገብቶ ማዕዷ ላይ ጥሎት ሔደ።
በሦስተኛው ግን ቁራ እባብ በአፉ ይዞ በምዕራቡ መስኮት ገብቶ ማዕዷ ላይ ጥሎት ወጣ። ቅድስት ኄራኒ ያየችው ራእይ ቢጨንቃት ሽማግሌ መምህሯን "ተርጉምልኝ" አለችው።
እርሱም "ልጄ ሆይ! ለዘመናት ስጠብቀው የነበረ ምኞቴን ነው ጌታ ያሳየሽ። የሕልምሽ ትርጉም እንዲህ ነው፦ ነጭ ርግብ የመንፈስ ቅዱስ (የሃይማኖት) ምሳሌ ናት። የወይራ ዝንጣፊው ደግሞ ማኅተመ ጥምቀት (ሜሮን) ነው። ቁራ የክፉ ነገሥታት ምሳሌ ሲሆን እባብ የመከራ ምሳሌ ነው።
ንስር ድል የመንሳት ምልክት ሲሆን አክሊል ደግሞ የመንግሥተ ሰማያት ምሳሌ ነው። ልጄ! ክርስቲያን ሆነሽ የሚደርስብሽን ሁሉ ጌታ አሳይቶሻል።" ብሎ ተርጉሞላት ተሰናበታት።
እርሷም ወደ ምሥራቅ ዙራ ጸለየች፦ "የማላውቅህ አምላክ ሆይ! ወደ እውነትህ ምራኝ።" ስትል ለመነች። በዚያች ሰዓት የእግዚአብሔር መልአክ መጥቶ አጽናናት። የሚያጠምቃትም እንደሚልክላት ነገራት።
በዚያን ጊዜ አባቷ ገብቶ "ልጄ! ከመሣፍንቱ ላንዱ ልድርሽ ስለሆነ ምን ትያለሽ?" አላት። "ሦስት ቀን ስጠኝ?" አለችውና ሰጣት። ወደ ጣዖቶቹ ዕለቱኑ ወርዳ "ላግባ ወይስ ይቅርብኝ?" አለቻቸው። ከቀድሞም በወርቅ የተለበጡ ድንጋዮች ናቸውና ዝም አሉ። በሙሉ ቀጥቅጣ ሰባብራቸው ተመለሰች።
በዘመኑ ቅዱሳን ሐዋርያት (በተለይ እነ ቅዱስ ጳውሎስ) በሕይወተ ሥጋ ነበሩና ከቅዱስ ጳውሎስ ደቀ መዛሙርት አንዱ ቤቷ እንደ ተዘጋ ገባ። ክርስትናን ከጥንቱ እስከ ተፍጻሜቱ አስተምሮ አጠመቃት።
በሦስተኛው ቀን አባቷ "ምን መከርሽ?" ቢላት "የእኔ ምክር መርዓተ ክርስቶስ (ሰማያዊ ሙሽራ) መሆን ነው።" አለችው። አባቷ ደነገጠ። እጅግ ስለ ተናደደ ወደ አደባባይ አውጥቶ አስሮ መሬት ላይ ጣላትና በመቶ የሚቆጠሩ ፈረሶች እንዲረግጧት አደረገ።
በወቅቱ ሰው የሚጠብቀው የአካሏን ቁርጥራጭ ነበር። ነገር ግን ጌታ ከእርሷ ጋር ነበርና ልብሷ እንኳ ጭቃ አልነካም። አባቷ ንጉሥ ሉክያኖስና ሠራዊቱ ያዩትን ማመን አልቻሉም። ሁሉም ድምጻቸውን ከፍ አድርገው "ከክርስቶስ በቀር ሌላ አምላክ የለም።" አሉ። ቅድስት ኄራኒ ምንም ሳትናገር ይህንን ሁሉ ሰው ማረከች።
ወዲያውም ንጉሡ መልእክተኛ ልኮ የቅዱስ ጳውሎስ ደቀ መዝሙርን አስጠርቶ ከነ ቤተሰቦቹ ተጠመቀ። የዚህን ዓለም ክብር ንቆም ንግሥናውን ተወ። የጸሎት ሰውም ሆነ። የቅድስት ኄራኒ ተጋድሎ ግን ቀጠለ።
በአካባቢው የነበረ ንጉሥ መጥቶ የአባቷን መንግሥት ቀማ። እርሷንም እጅግ አሰቃያት። እርሱ አልፎ አርማንዮስ የሚባል ንጉሥ እንዲሁ አሰቃያት። እርሱም አለፈ። ከእርሱ ቀጥሎ የመጣው ንጉሥ ብዙ መከራዎችን በእርሷ ላይ አደረሰ። በጦርም ጐኗን ወግቶ ገደላት።
ከጥቂት ሰዓታት በኋላ ግን ልክ ከእንቅልፉ እንደሚነቃ ሰው ተነስታ ጠራችው። በጣም ደንግጦ "አምላክሽ አምላኬ ነው።" ሲል አመነ። ከሠላሳ በላይ ሠራዊቱን ይዞም ተጠመቀ።
ቅድስት ኄራኒ በቀረ ሕይወቷ በስብከተ ወንጌል እስያን አድርሳለች። ጌታ አብርቶላት እርሷም አብርታ እልፍ ፍሬን አፍርታ በዚህች ቀን ዐርፋለች። የሐዋርያትንም የሰማዕታትንም አክሊል ተቀዳጅታለች።
<3 ንግሥተ ሳባ <3
ይህቺ ኢትዮጵያዊት ከሦስት ሺህ ዘመናት በፊት የነበረች ደግ እናት ናት። በሥጋዊ ደረጃ ከታንዛንያ እስከ የመን ያስተዳደረች ስመ ጥር ንግሥት ስትሆን በመንፈሳዊው ደረጃ ደግሞ እግዚአብሔር የቀባውን ሰው ፍለጋ ወደ ኢየሩሳሌም ተጉዛለች።
ከዚያውም አምልኮተ እግዚአብሔርን ከሥርዓተ ኦሪት ጋር አምጥታለች። ድንግልናዋን ለታላቁ ንጉሥ ሰሎሞን ሰጥታ ምኒልክን ወልዳለች። ይህቺ ንግሥት በጌታችን (በፈጣሪ) አንደበትም ተመስግናለች።
(ማቴ. ፲፪፥፵፪)
በስምም "ሳባ፣ አዜብና ማክዳ ተብላ ትታወቃለች። ዛሬ ዕለተ ልደቷ ነው።
<3 ቅድስት ዕሌኒ ንግሥት <3
ይህቺ ቅድስት የቅዱስ ቆስጠንጢኖስ እናቱ፣ የመስቀሉ ወዳጅ፣ የቤተ ክርስቲያን ባለውለታ የሆነች ክብርት እናት ናት። ይህቺም ቅድስት የተወለደችው በዚሁ ዕለት ነው።
የቅዱሳት እናቶቻችን አምላክ እኅት እናቶቻችንን ከክፋትም፣ ከጥፋትም፣ ይሠውርልን። ለሃገርም፣ ለሃይማኖትም የሚጠቅሙ ሴቶችንም ጌታ አይንሳን። በረከታቸውም ይደርብን።
ነሐሴ ፳፩ ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
፩.ተዝካረ ፍልሠታ ለማርያም ድንግል (ስድስተኛ ቀን)
፪.ቅድስት ኄራኒ ሐዋርያዊት (ሰማዕት)
፫.ቡርክት ንግሥተ ሳባ (ልደቷ)
፬.ቅድስት ዕሌኒ ንግሥት (ልደቷ)
ወርኀዊ በዓላት
፩.ቅድስት ድንግል እግዝእትነ ማርያም ወላዲተ አምላክ
፪.አበው ጎርጎርዮሳት
፫.አቡነ ምዕመነ ድንግል
፬.አቡነ አምደ ሥላሴ
፭.አባ አሮን ሶርያዊ
፮.አባ መርትያኖስ ጻድቅ
"ንግሥተ አዜብ በፍርድ ቀን ከዚህ ትውልድ ጋር ተነስታ ትፈርድበታለች። የሰሎሞንን ጥበብ ለመስማት ከምድር ዳር መጥታለችና። እነሆም ከሰሎሞን የሚበልጥ ከዚህ አለ።"
(ማቴ ፲፪፥፵፪)
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
531 views15:17