2022-12-24 15:17:37
✞ እንኩዋን ለኃያል "መሥፍነ እሥራኤል ቅዱስ ጌዴዎን" እና "ማርያም እህተ ሙሴ" ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ ✞
+*" ኃያል ጌዴዎን "*+
=>እግዚአብሔር ሰማይንና ምድርን: 22ቱን ሥነ ፍጥረትን ፈጥሮ አዳምን ገዢ አደረገው:: አክሎም በነፍስ ሕያው አድርጐ: በመንፈስ ቅዱስ አክብሮ: ነቢይና ካህን አድርጐ: ካንዲት ዕፀ በለስ በቀር በፍጥረት ሁሉ ላይ አሰለጠነው::
+አባታችን አዳም ግን ስሕተት አግኝቶት ከገነት ወጣ:: መከራና ፍዳም አገኘው:: በሁዋላም ለ100 ዓመት አልቅሶ ንስሃ ገባ:: ጌታም ንስሃውን ተቀብሎ "ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ" የሚል ተስፋ ድህነትን ሰጠው::
+ስለዚህም ምክንያት ለ5,500 ዓመታት ትንቢት ሲነገር: ሱባኤ ወደ ታች ሲቆጠር: ምሳሌም ሲመሰል ኖረ:: ከደግ ፍጥረት አዳም እስከ ኖኅ ድረስ: የሴት ልጆች እግዚአብሔርን በንጽሕና ሁነው በደብር ቅዱስ አመለኩ::
+ትንሽ ቆይተው ግን ስለተቀላቀሉ ከቃየን ልጆች ጋር በማየ ድምሳሴ ጠፉ:: በጻድቅ ሰው ኖኅ የተጀመረው ትውልድም እግዚአብሔርን ለመዘንጋት ጊዜ አልፈጀበትም:: ነገር ግን ከሴም ዘር ቅንና ጻድቅ ሰው አብርሃም ተገኘ::
+ከእርሱም ይስሐቅ: ከዚያም ያዕቆብ (ደጋጉ) ተገኙ:: ያዕቆብም "እሥራኤል" ተብሎ: በልጆቹ "ሕዝበ እግዚአብሔር" የተባለ ነገድ ተመሠረተ:: በተስፋይቱ ምድር በከነዓን እንዳይኖሩም ረሃብ ምድረ ግብጽ አወረዳቸው::
+በዚያም ለ215 ዓመታት በጭንቅ የባርነትን ሕይወትን አሳለፉ:: እግዚአብሔርም ስለ ወዳጁ አብርሃም ሲል እሥራኤልን አሰባቸው:: የዋሕና ጻድቅ ሰው ሙሴን አስነስቶ እሥራኤልን ከግብጽ ባርነት አዳናቸው::
+ይኸውም በጸናች እጅ: በበረታችም ክንድ: በ9 መቅሰፍት: በ10ኛ ሞተ በኩር: በ11ኛ ስጥመት ግብጻውያንን አጥፍቶ ነው:: በየመንገዱም ጠላቶቻቸውን እየተበቀለላቸው ነው:: ከዚህ ዘመን ጀምሮም እሥራኤል በመሳፍንትና በካህናት የሚተዳደሩ ሆኑ::
+አስቀድሞ ሙሴ በምስፍና: አሮን በክህነት መሯቸው:: ቀጥሎም በቅዱስ ሙሴ ኢያሱ: በአሮን አልዓዛር ተተኩ:: እንዲህ እንዲህ እያለም ከኃያል ሰው ጌዴዎን ደረሱ:: ይኸውም ከዓለም ፍጥረት 4,151 ዓመታት በሁዋላ መሆኑ ነው::
+በጊዜው እሥራኤል ጣዖትን እያመለኩ እግዚአብሕርን ስላሳዘኑት ለጠላቶቻቸው አሳልፎ ይሰጣቸው ነበር:: የአካባቢው መንግስታት እነ አሞን: አማሌቅ: ኢሎፍሊ ስንኩዋ ያኔ ዛሬም ቢሆን እንደምትመለከቱት ዶሮና ጥሬ ናቸው::
+ከክርስቶስ ልደት 1,349 ዓመታት በፊትም በእሥራኤል ላይ ምድያማውያን (ይህቺ ሃገር የኢትዮዽያ ግዛት ነበረች ይባላል) በጠላትነት ተነስተውባቸው ተጨነቁ::
+አምላካችን እግዚአብሔርም ሊያድናቸው ወዶ መልአኩን ወደ ጌዴዎን ላከው:: ቅዱስ መልአክም ወደ እርሱ ቀርቦ "ኃያል የእግአብሔር ሰው" ሲል ጠራው:: ጌዴዎን ግን "ባሮች ስንሆን ምን ኃይል አለን!" ሲል መለሰለት::
+መልአኩም "እግዚአብሔር ካንተ ጋር ነውና ሒድ! እሥራኤልን ከምድያም እጅ አድናቸው" አለው:: ጌዴዎን ምልልሱን ቀጠለ:: "እግዚአብሔር ከእኔ ጋር መሆኑን በምን አውቃለሁ?" ሲል ጠየቀው::
+ጌዴዎን ይህንን ያለው ፈጣሪውን ተጠራጥሮት አይደለም:: ይልቁኑ ጥበበ እግዚአብሔር ይገለጥ ዘንድና በሁዋለኛው ዘመን የሚፈጸመውን ምሥጢረ ሥጋዌ ሊያስረዳ እንጂ::
+መልአኩም መስፍኑ የሰዋውን መስዋዕት አሳረገለት:: ቀጥሎም ጌዴዎን "ጸምር (ብዝት ጨርቅ) ልዘርጋ:: ጠል (ዝናብ) በጸምሩ ላይ ይውረድ:: ዳር ዳሩ ግን ይቡስ (ደረቅ) ይሁን" አለ:: በጠዋትም እንዳለው ሆኖ አገኘው::
+በጸምሩ ላይ የወረደውን ጠል ጨምቆ በመንቀል ሞልቶ ቢጠጣው ሰማያዊ ኃይል ወረደለት:: ጥያቄውን አሁንም ቀጠለ:: "ጌታ ሆይ! እንደ ገናም ነገሩ ይቀየርልኝ:: ጠል በጸምሩ ላይ አይውረድ:: ዳር ዳሩ ግን ይውረድበት" አለ::
+እንዳለውም ሆነ:: ይህ ሁሉ ምሳሌ ነው:: ለጊዜው ጸምር የእሥራኤል: ጠል የረድኤት: ምድር የአህዛብ ምሳሌ ነው:: ጠል በጸምር እንጂ በምድር ላይ እንዳልወረደ ረድኤተ እግዚአብሔር ለእሥራኤል እንጂ ለአሕዛብ ያለ መደረጉ ምሳሌ ነው::
+አንድም ምሳሌውን ይለውጧል:: ጠል የሚለውን ብቻ እንቀይረውና ጠል የመቅሰፍት ምሳሌ: በ2ኛው ጠል በምድር ላይ እንጂ በጸምር ላይ እንዳልወረደ: መቅሰፍቱም እሥራኤልን ትቶ በአሕዛብ ላይ ወርዷልና:: ( ይህ ጊዜአዊ ምሥጢሩ ነው:: )
+አማናዊ ምሥጢሩ ግን ወደ ሐዲስ ኪዳን ያመጣናል:: ጸምር የእመቤታችን: ጠል የጌታ ምሳሌ:: ጠል በጸምር እንጂ በምድር ላይ አለመውረዱ ጌታ ከድንግል ማርያም ብቻ መወለዱን ያሳያል::
+በ2ኛው ምሳሌ ደግሞ ጠል የፍዳ: የመርገም ምሳሌ ይሆናል:: ጠል በምድር ላይ እንጂ በጸምር ላይ አለመውረዱ ድንግል ማርያም ፍዳ መርገም የሌለባት ንጽሕት መሆኗን ያሳያል::
+ይህ ሁሉ የተደረገለት ጌዴዎንም በወገኖቹ መካከል አዋጅ አስነግሮ 32ሺ ሠራዊትን ሰበሰበ:: ግን እግዚአብሔር የእሥራኤላውያንን ክፋት (ማለትም በራሳችን ኃይል አሸነፍን) እንደሚሉ ያውቃልና "የፈራ ይመለስ በል" አለው::
+22ሺ ሠራዊት ፈርቶ ተመለሰ:: ምክንያቱም የምድያም ሠራዊት ከ100ሺ በላይ ነበርና:: አሁንም "10ሺው ብዙ ነው:: ወደ ወንዝ አውርደህ ለያቸው" አለው:: ጌዴዎንም ወደ ወንዝ አውርዶ "ውሃ ጠጡ" አላቸው::
+ከ10ሺው 300ው በእጃቸው እየጠለፉ ሲጠጡ 9,700 ያህል ሰራዊት ግን ተጐንብሰው በአፋቸው ጠጡ:: በዚህም "ሌሎቹን (የተጐነበሱትን) አስመልሰህ በ300ው ተዋጋ" ተባለ::
+እርሱም 300ውን ተከታዮቹን ይዞ: መለከትና መብራት በሸክላ ይዞ በምድያም ሠራዊት አካባቢ አደረ:: በዚያች ሌሊትም ጌዴዎንና ሠራዊቱ በምድያም መካከል ገብተው እንስራቸውን ሰበሩ::
+መለከቱንም ነፉ:: እንደ አንበሳም "ኃይል ዘእግዚአብሔር: ኩዊናት ዘጌዴዎን - ኃይልን ከእግዚአብሔር: ጦርን ከጌዴዎን" እያሉ ገጠሙ::
+በድንጋጤ የተመቱት ምድያማውያንም እርስ በርሳቸው ተዋግተው በአንድ ሌሊት ብቻ 102,000 ሠራዊት አለቀባቸው:: ቀሪዎቹም ወገኖቻቸው አፈሩ:: እሥራኤል ግን በፈጣሪያቸው ኃይል ተፈሩ:: ጌዴዎንም ለ40 ዓመታት እሥራኤልን አስተዳድሮ በዚህች ቀን ዐርፏል:: (መሣ. 6:1---8:35)
+"+ ማርያም እህተ ሙሴ +"+
=>ይህች እናት የሊቀ ነቢያት ቅዱስ ሙሴና የሊቀ ካህናቱ ቅዱስ አሮን ትልቅ እህት ስትሆን ወላጆቿ እንበረምና ዮካብድ ይባላሉ:: እሥራኤል ከግብጽ ባርነት እንዲወጡ የእርሷን ያህል አስተዋጽኦ ያደረገች ሴት የለችም::
+ከመነሻውም ቅዱስ ሙሴን የጠበቀች: በሕግ በሥርዓት እንዲያድግ ከእናቱ ጋር ያገናኘች: ወገኖቿ ከግብጽ ሲወጡም ሴቶችን የመራች እናት ናት:: ወንድሞቿን ሙሴንና አሮንንም ታገለገላቸው ነበር:: በተለይ እግዚአብሔር ባሕረ ኤርትራን የብስ ሲያደርጋት ከበሮን አንስታ "ንሴብሖ ለእግዚአብሔር" ብላ ፈጣሪዋን አመስግናለች:: (ዘጸ. 15:20)
+አንድ ጊዜም "ኢትዮዽያዊቷን ሲፓራን ለምን አገባህ" በሚል ስለ ተናገረችው እግዚአብሔር ተቆጥቶ በለምጽ መቷታል:: (ዘኁ. 12:1) ቆይቶም በቅዱሱ ምልጃ ምሯታል:: ማርያም በመንገድ ሳሉ: ወደ ርስት ሳይደርሱ ዐርፋ ተቀብራለች:: (ዘኁ. 20:1)
=>አምላከ ኃያላን መንፈሳዊ ኃይልን ልኮ ጠላትን ያድክምልን:: ከወዳጆቹ በረከትም ይክፈለን::
=>ታሕሳስ 16 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ ጌዴዎን ኃያል
2.ማርያም እህተ ሙሴ
84 views12:17