Get Mystery Box with random crypto!

በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ የአንድ መጋዘን ግንብ ተደርምሶ በሰው ህይወትና አካል እንዲሁም በንብረ | Fana Tv/Fbc ™

በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ የአንድ መጋዘን ግንብ ተደርምሶ በሰው ህይወትና አካል እንዲሁም በንብረት ላይ ጉዳት መድረሱን የአዲስ አበባ ፖሊስ አስታወቀ።


አደጋው የደረሰው ሐምሌ 24 ቀን 2014 ዓ.ም በግምት ከቀኑ 9:30 ሰዓት ሲሆን በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ወረዳ 3 ክልል ልዩ ቦታው አማኑኤል ሆስፒታል አካባቢ ነው።

በመጋዘን ቤት ውስጥ ውሃ በመሙላቱ ግንቡ ተደርምሶ ከስር በሚገኙ መኖሪያ ቤቶች ውስጥ በነበሩ 3 ግለሰቦች ላይ ጉዳት በማድረስ የ1 ሰው ህይወት ሆስፒታል ከደረሰ በኋላ ሲያልፍ ፤ 2 ግለሰቦች ላይ ደግሞ ከባድ የአካል ጉዳት እንደደረሰባቸው የመሳለሚያ አካባቢ ፖሊስ ጣቢያ የዕለቱ ተረኛ መኮንን ምክትል ኮማንደር መዓዛ ገብረማርያም ገልፀዋል።

ኮማንደሯ አክለው እንዳስታወቁት በአፋጣኝ አደጋው በደረሰበት ቦታ በመሄድ ከሌሎች የፀጥታ አካላትና ከአካባቢው ነዋሪዎች ጋር በመሆን ጉዳት የደረሰባቸውን ሰዎች የማውጣትና ወደ ህክምና እንዲሄዱ የማድረግ እንዲሁም ተጨማሪ አደጋ እንዳይከሰት ሰዎችን ከአደጋው ቦታ የማሸሽ ስራዎች መሰራታቸውን ምክትል ኮማንደር መዓዛ አስረድተዋል።

ኃላፊዋ አያይዘው እንደተናገሩት ከክረምቱ ወቅት ጋር ተያይዞ ለአደጋ ስጋት የሆኑ ቦታዎችን በመለየት የሚመለከታቸው አካላት ጉዳት ከመድረሱ በፊት ትኩረት በመስጠት የመፍትሔ እርምጃዎችን መወሰድ እንዳለባቸው ተናግረዋል።

የአካባቢው ነዋሪዎች በሰጡት አስተያየት የመጋዘኑ ግንብ ተደርምሶ በሰው ህይወትና በአካል ላይ ጉዳት በመድረሱ የተሰማቸውን ሃዘን ገልፀው ተጨማሪ አደጋ እንዳይከሰት ፖሊስ በፍጥነት ቦታው ላይ ደርሶ ከሌሎች የፀጥታ አካላት ጋር በመቀናጀት የሰራውን ስራ አድንቀው ቀጣይም መጋዘኑ መፍትሔ ካልተበጀለት ስጋት እንደሆነባቸው ተናግረዋል።