☞ ዝክረ ኸሚስ ( 85 ) . « ጉረስ ያለውማ ማድ የዘረጋለት ፣ በእህል ውሃ ዲስቱ ኒካውን ጣደለት ። » ( አገሬው ) - አውገረዴ ሆዴ ... አብሮ ዘማች ጓዴ ፣ ኸሚስ አመሻሹ - - ኸሚስ ወደ ማታ ፣ ያርገበግበኛል የክድሚያሽ ወጋገን ክንፉን እያማታ። . ይሄው ... . ወቅቱ ላይ ደግ ሀጃ ፣ ሃጃው ላይ ውብ ሓድራ ፣ ሓድራው ላይ ጠይም ሌት ፣ አንቺን የተኳለ በቀለሜ አውሃል የሚያክለፈልፈኝ፣ ለሰንበራም ግጥም ፣ የነፍሴን ዳርቻ በኣጀቡ ለበቅ በጉድ የሚገርፈኝ ። .. ( መቼስ ... .. እድል ባያነቅፈኝ እጣዬ ጠርጎልኝ ፣ መንገዴ ቢያሰልጠኝ ‘ርምጃ ሰልቶለልኝ ፣ ብቻየን አይሆንም ... ውሃ ልኬ አንቺ ነሽ ፣ የመሄዴ ሚዛን ከነግ ተስፋ ፈጅር ተዋዶ ይተጋል፣ በ‘ያንዳንዱ ዳና የመድረሴ ጀንበር በሺህ ዲጂት ያድጋል። .. ኸሚስ አመሻሹ ... ኸሚስ ወደ ማታ ፣ ሃጃው ገድምዳሜ ፣ ሓድራው አባ ሞገድ ፣ የቀኑ ምስለኔ የለይሉ ባለሟል ጠይሞ አንቺን ሲሆን ፣ በኸሚሱ ሞደብ የቱን ቀለም ይዤ የቱን እጥል ይሆን ?! . ( እንዲያ ሆነ እንግዲህ ... ! ) . እድያ ነውና ... እምቢ የማይሉት ፣ ሀቅ ያጉረበረበው ምናብ ሲጠዘጥዝ እከኩ ይነሳል፣ ጠይም ሌሊት መሀል ፣ ቀልብ የሚያለመልም ሀረግ ያፈረጠው ቅኔ ደም ይፈሳል . አዎ ! ( አውቅሻለሁ ሌቱን ... ! ) . በሀጃው ኸለዋ ፣ ከግርዶሹ ወዲያ አወል ቡናው ደርሶ ቀሃ ጀባ ‘ስኪባል፣ ከመከኬው ክንፈር ፣ ከፍንጭትሽ ግርጌ ፈገግታሽ ያደባል። ሊናደፍ ...! . መገን ።! . ፈሽረክ ትይዋለሽ ... . መሳቅሽ አቅል ነው ! ፈገግታሽ ቀለብ ነው ! . የመሀባ ሸውቁ ፣ የሓድራውን ዋርካ ፣ በፈገግታሽ ጠለሽ ሌቱ ላይ ያዘማል፣ ሳቅሽን አሳቦ .... ነፍስ የሸነቆረው የሀሴት ጉድ ቀለም ፈሶብኝ ይተማል። .. አውገረዴ ሆዴ ፣ ኸሚስ ሃላል ሳቄ ፣ ጠይም ሌት ቀለሜ ፣ ገራም ማልዶ ቢብት ፣ ለይሉ ቢገማሸር ታለ ሰው ብቻውን በዱንያ ሞደቡ፣ ቀለሙ ጥሞናን በሶብሩ ቢያረብብ ምን ቢቸር አደቡ፣ . ቀኑ መች ሲቀናው ፣ ሌቱ መች ሲገራው ፣ ሊገጥመው ሰው ገጥሞት ፣ ከኸልቄው እዬዬ እምባ እየጨለፈ ፣ ዝጎ ላይዶለዱም ለብዕሩ ስለት ሳቅ ካላጠቀሰ ፣ ገጣሚ ፉዞ ነው ... ! ለምናቡ ንቃት ሰውነት ኮልኩሎት ካልተቀሰቀሰ ። ገጣሚ ‘ራስ የለው ... ! ለምናብ ጎፈሬው ባብሮነቱ ሚዶ በሰው ካልነቀሰ፣ . ኸሚስ አመሻሹ - - ኸሚስ ወደ ማታ ፣ ያርገበግበኛል የክድሚያሽ ወጋገን ክንፉን እያማታ። .. እንግዲህ ... እሱ ይደግሰው ፣ አይሆንም ታለ ሰው ፣! እንኳን ሳቁ ቀርቶ ይግጠመኝ አህህ ይብለገኝ እዬዬው፣ በግጥም ላባብል በምናቤ አንቀልባ ስለ ሰው አዝዬው። . « አዳኝ ቁንጥር ፈርቶ -- ጭቃ ተጠይፎ ፣ አይወረወርም -- ቀስቱ ደጋን አልፎ ። » . እያለኝ በቅኔው አያ ሙሌ ጓዴ ፣ እንደት ሀቅ ልዘጋ ይቻለኛል እንዴ ?! . እሱ ይዘንልኝ ፣ ሙሾ ተቧልት ጋር ፣ እንደህል ዋጀራ በማይለይበት ፣ ዘለላ ቃል ሳልፅፍ አዝሞ እንዳይነጋ ባክኜ ‘ ንዳይፈጅር ፣ መሷረፊያ ቀለም አንዳቹን ዛር ልኮ ለፍርጃው ይጀርጅር ። .. ታልቸረማ ምኑን ... ከምኑ ተጋጥሞ ፣ ሌሊቱ እንደት ጥሞ ፣ ሰው ታላስባለማ በምን ወዝ ሊከተብ ሀቅ እንዳይቀበር ፣ ቅብጅር ነው ‘ንጂ ፣ ሌት ሌላ መልክ የለው ካልጠየመ በቀር ። --- semir ami @semiraklu 520 viewsSemir ايمي, 15:07