2022-05-03 17:12:36
የሸዋል ጾም
=======
ከአቡ አዩብ አል‐አንሷሪይ [ረዐ] እንደተዘገበው የአላህ መልክተኛ [ﷺ] እንዲህ ብለዋል: ‐ «ረመዳንን ጾሞ ከዚያም ከሸዋል ስድስት ቀናትን ያስከተለ ሰው ይህ ዓመቱን እንደጾመ ይቆጠርለታል።» ሙስሊምና ሌሎችም ዘግበውታል።
ከጃቢር [ረዐ] እንደተዘገበው የአላህ መልክተኛ [ﷺ] እንዲህ ብለዋል: ‐ «ረመዳንን የጾመ ከዚያም ከፊጥር በኋላ ስድስት ቀናትን ያስከተለ ሰው አመቱን በሙሉ እንደጾመ ይቆጠራል። አንድን መልካም ስራ የሰራ ሰው በዐስር አምሳያዎቹ ይባዛለታል።» ኢብኑ ማጀህ ዘግበውታል።
:
የመልካም ስራ ምንዳው በዐስር ይባዛል። ስለዚህ የረመዳን ጾም በዐስር ሲባዛ ዐስር ወራት ይሞላል። የሸዋል ስድስት ቀናት በዐስር ሲባዙ ስድሳ ቀናት ይሆናሉ። ሁለት ወር ማለት ነው። ስለዚህ ሰውየው ሙሉ አመቱን እንደጾመ ይቆጠርለታል።
:
የዒድ ማግስትን ማስከተል
=================
በሁለቱ ሐዲሶች መሰረት ስድስቱን ቀን ከዒዱ ቀን ማግስት ጀምሮ በመሀል ምንም ክፍተት ሳይኖር መጾም እንደሚወደድ ያመለክታሉ። ሻፊዒዮቹ ይህንን ሃሳብ ይመርጣሉ። ምክንያቱም በዚህ መንገድ መልካም ስራን በማከታተሉ ጾሙን እንዳይተወው ያግዘዋል። በሰፊው የሀገራችን ክፍል ከአባቶቻችን ጀምሮ የለመድነው አካሄድም ይህንን መሰረት ያደረገ ነው።
:
በእርግጥ ሐዲሶቹ ቀናቶቹን አከታትሎ መደርደር መልካም መሆኑን በይበልጥ የሚያመለክት ስሜት ቢኖራቸውም ቀናቶቹን አለያይቶ እያረፉ መጾም ችግር እንደሌለውም ይጠቁማሉ።
ስለዚህ ከዒዱ ዋዜማ አንስቶ እስከ ሰባተኛው ቀን ድረስ የጾመ ሰውም ሆነ አዘግይቶ ሰብስቦ በማከታተል ወይም እያረፈ ነጣጥሎ የጾመ ሰው ሱናውን አግኝቷል። ይህ ሻፊዒዮቹ፣ አሕመድ እና አብዝሀኞቹ ዑለሞች ዘንድ የተረጋገጠ ሃሳብ ነው።
:
ሐነፊዮቹ ተመራጭ ያደረጉት ሃሳብ ስድስቱን የሸዋል ቀናት መጾም ችግር የለውም [ይወደዳል ሳይሆን] የሚለውን ሃሳብ ነው። በእርግጥ ከሐነፊዮች ከፊሎቹ አከታትሎ መጾም ይጠላል ያሉበት ሁኔታም ነበር። ለዚህ ድምዳሜ ምክንያት ያደረጉት ከሸዋል ስድስት ቀን መጾም ከረመዳን ጋር እንዳይመሳሰል ወይም ተጨማሪ ግዳጅ እና ድንጋጌ እንዳይመስል መስጋታቸውን ብቻ ነው። ከኢማም ማሊክም ተመሳሳይ ሃሳብ ተሰንዝሯል። ነገርግን የዒድን ቀንን በማፍጠር ከረመዳን ጋር የመመሳሰል ስሜቱ ስለሚጠፋ ሸዋልን መጾሙ ችግር የለውም የሚለውን ሀሳብ ብዙዎቹ ሐነፊዎች መርጠውታል። "አልሂዳያ" "አልጋያ" የተሰኙ መፅሀፍቶቻቸው ይህንን አብራርተዋል።
:
በርግጥም ከላይ የጠቀስናቸው ሐዲሶች የስድስቱ የሸዋል ቀናት ጾም ተወዳጅ መሆኑን ያረጋግጣሉ። ሐዲሶቹ መከራከሪያ ለመሆን ብቁ የሆኑ ግልፅ መረጃዎች ናቸው። ስለዚህ ሳንጠራጠር በዚሁ መንገድ መጓዝ እንችላለን።
:
ከሌላ ኒያ ጋር ማቆራኘት
===============
የስድስቱ ቀን ጾም ላይ ቀዳእን ጨምሮ በመነየት መጾም ይፈቀዳል። ሰውየው የሁለቱንም ምንዳ ያገኛል። ኢማም ሲዩጢይ [ረዐ] 'አል‐አሽባህ ወን‐ነዟኢር' በተሰኘው መፅሐፋቸው ላይ እንዲህ ይላሉ: ‐ "ለምሳሌ በዐረፋ ቀን ከዐረፋ ጾም ጋር ቀዷእን፣ የስለት ጾምን፣ ከፋራን… በአንድ ላይ ነይቶ መጾም አስመልክቶ እንደሚፈቀድና ምንዳውም እንደሚገኝ አል‐ባሪዚይ ፈትዋ ሰጥተዋል። እንደውም እለቶቹን ልቅ በሆነ የጾም ኒያ ቢያሳልፈውም የስድስቱን የሸዋል ጾም ምንዳ ያገኛል ብለዋል። እርሳቸው የሸዋልን ጾም በተሒይ‐የቱል‐መስጂድ ሶላት መስለውታል።"
ማንኛውም ሰው መስጂድ ገብቶ ከመቀመጡ በፊት ሁለት ረከዐና ከዚያ በላይ የሆነ ማንኛውም ሶላት ቢሰግድ ተሒያን ቢነይትም ባይነይትም የተሒያውን ምንዳ እንደማያጣው፣ ፈርድ ወይም ሱና ሲሰግድ አብሮ ተሒያን መነየት እንደሚፈቀድለት ሁሉ የሸዋል ጾምም በዚሁ አኳያ መታየት አለበት እያሉ ነው።
ምክንያቱም ተሒይ‐የቱል መስጂድ ያስፈለገው ሰውየው መስጂድ ሲገባ ከመቀመጡ በፊት ሶላት እንዲሰግድ ማድረግ ብቻ ነው። ስለዚህ በማንኛውም ሶላት ይህንን ማሳካት ስለሚችል ተሒያውን ያገኘዋል።
የተሒይ‐የቱል መስጂድ ድንጋጌን አስመልክቶ የአላህ መልክተኛ [ﷺ] እንዲህ ብለዋል: ‐ "እያንዳንዳችሁ መስጂድ ስትገቡ ሁለት ረከዐ ሳትሰግዱ አትቀመጡ።"
በሸዋል ወር ያሉት የስድስት ቀናት ጾምንም አል‐ባሪዚይ እና በርካታ መሰሎቻቸው እንደዚሁ ተመልክተውታል።
በዚህ መሰረት ሱና ጾም በፈርድ ውስጥ መካተት እንደሚችል ዐሊሞች [በተለይ ሻፊዒዮች] ጠቁመዋል። ነገርግን ፈርድ ጾም በሱና ጾም ኒያ ውስጥ መካተት አይችልም።
:
ስለዚህ ሴቶች በረመዳን በወር አበባ ምክንያት ያመለጣቸውን ከሸዋል ጾም ጋር በአንድ ላይ በመነየት ቀዳቸውን መክፈል ይችላሉ ማለት ነው።
ነገርግን በቅድሚያ ቀዷቸውን ቢከፍሉ ከዚያም ሸዋል ሳይወጣባቸው የሸዋልን ጾም ቢጾሙ፤ ወይም በተቃራኒው መጀመሪያ የሸዋል ስድስቱን ጾም አስቀድመው ቢጾሙ ከዚያም ቀዳቸውን አስከትለው ቢከፍሉ የተሻለ ነው። ምክንያቱም ደርቦ በመጾም ምንዳ ያገኛል ማለት ነጣጥሎ በመጾም የሚገኘውን የተሟላ ምንዳ ያገኛል ማለት አይደለም። ነጣጥሎ በተለያዩ ጊዜያት ኒያውን ሳያደራርብ የጾመ ሰው ኒያዎችን አደራርቦ ከጾመ ሰው የበለጠ ምንዳ አለው።
:
ኢማም ረምሊይ [ረዐ] እንዲህ ይላሉ: — "በሸዋል ወር ቀዳእን፣ ስለትን እና ሌሎች ጾሞችን የጾመ ሰው የሸዋል ሱና ጾምን ምንዳ ያገኛል። ይህ አባቴ [ረሒ] አል‐ባሪዚን፣ አል‐አስፈዊን፣ አን‐ናሺሪን፣ አል‐ፈቂህ ቢን ሷሊሕ አል‐ሐድረሚን እና ሌሎችንም ዋቢ በማድረግ የሰጡት ፈትዋ ነው። ነገርግን ረመዳንን በስድስት የሸዋል ቀናት ጾም አስከትሉት የተባለበትን የተሟላ ምንዳ አያገኝም።"
:
የስድስቱ ቀናት የሸዋል ጾም በፈርዱ ላይ የተከሰተን ጉድለት ይሞላል። የረመዳን ጾም ተቀባይነት ማግኘቱን ይጠቁማል። ምክንያቱም መልካም ስራ ተቀባይነት ማግኘቱን ከሚጠቁሙ ምልክቶች መሀል አንዱ ወዲያው መልካም ስራን ማስከተል ነው። ሰውየው አላህን ማምለክ እንደማይሰላች ማረጋገጫም ይሆናል።
የሸዋል ጾምም ሆነ የማንኛውም ሱና ጾምን ኒያ በሌሊት ብቻም ሳይሆን እስከ ዙህር ባለው ሰዓት ማስገኘት ይቻላል።
:
በመልካም ነገር ላይ እንተጋገዝ። እንዘያየር። በሸዋል ጾም አደራ እንባባል።
መልካም ዒድ!
http://t.me/fiqshafiyamh
114 viewsBin Baba Ali, 14:12