2022-01-07 19:48:36
ሙክቱ ዶሮ
~~~~~~~~~~~~~~~~~~
የበዓል ዋዜማ ላይ ከቀን ወደ ስምንት ሰዓት ገደማ አንዳንድ ነገር ለመግዛት እናቴ ጋር ገበያ ወጣን ። እና በመጀመሪያ የዶሮ ተራን ለማየት ወስነን ትንሽ ገባ እንዳልን አንድ ፊቱ ደረቅ ያለ ወጣት የአንበሳ ደቦል የሚመስሉ ዶሮዎች ይዞ አየን። እኔም ጠጋ ብዬ አዘቅዝቄ ወደ አንዱ ዶሮ እያየሁ 'ስንት ነው አልኩት ? ' ። ሰውየው ወደ ዶሮው ትንሽ እያየ ቆየና ። 'ቆንጆ ዶሮ ነው ላት እራሱ ሊኖረው ይችላል የሚል ጥርጣሬ አለኝ ' አለኝ። አረ ዋጋውን ነው የጠየቅኩህ ስለው ። ሰምቻለሁ እንደ መግቢያ ይሆንህ ዘንድ ብዬ ነው ። ደግሞም ዋጋውን ከማወቅህ በፊት ስለ ዶሮው ትንሽ ነገር ብታውቅ ይጠቅምሃል እንደ ጠቅላላ እውቀት(general knowledge) ውሰደው ። ዶሮው ቆፍጠን ያለ ጀግና ዶሮ ነው የሰፈር ዶሮዎች ቀና ብለው አየዩትም 'አለኝ ። እና እንዴት ብለው ነው ሚያዩት ልለው ፈልጌ እድሉን አላገኘሁም ። ' እንደ ሌሎቹ ዶሮዎች ሶስቴ ብቻ አይደለም ሌሊት ዘጠኝ ሰዓት የሚጮሀው ።' አለ። ይሄ ነገር መድፍ ነፍስ ዘርቶ ነው እንዴ የገጠመኝ?' አልኩ በሆዴ አሁንም እድሉን ስላልሰጠኝ ።
'የሚውልበትን የሚያውቅ ደፋር እና ብልህ ዶሮ ነው' ብሎ ሊቀጥል ሲል አቋረጥኩትና ። 'በል ዋጋውን ነገረኝ ' አልኩት። እሱም ' ያው ዋጋው መጨረሻ የሌለው ዘጠኝ መቶ ብር ነው ' አለኝ። በቁሜ ክው ነው ያልኩት። በዝግመተ ለውጥ ወደ በግ የሚቀየር ነው የመሰለኝ ። ለዚህማ መግቢያ ብቻ አይደለም ሀተታም ያስፈልገዋል ብዬ ዘወር ስል እናቴ የለችም በድንጋጤ ይመስለኛል ካጠገቤ ተሰውራለች ። በዘጠኝ መቶ ብር ሽንኩርት ከነጅራቱ ፣ ዘይት የባለ ሃይላንዱን እና በግ ከነማረጃው የሚገዛበትን ዘመን ላሳለፈ ሰው እውነትም መሰወር ሲያንስ ነው ብዬ ወደ ሻጩ ዘወር ስል ዶሮው በቆረጣ አየኝ ። እኔ ምልህ' ጀግናው የሰሜኑ ጦርነት ላይ ተሳትፏል እንዴ ቆረጣ ነው አስተያየቱ እራሱ' አልኩት። 'አዎ እሱ የመራው ግንባር ላይ ምንም ሽንፈት አልተስተናገደም ' አለኝ ። ጎበዝ ነጋዴ ነህ ስለምትሸጠው ነገር መረጃ ታሰባስባለህ ብዬ በል ቀንስ እና ሽጥልኝ አልኩት። 'ልጄ ተወው ' አለችኝ የተሰወረችው እናቴ ከየት እንደተከሰተች በማላውቀው ሁኔታ ካጠገቤ ቆማ። እኔም ነገሩን ተረድቼ ቆይ ትንሽ ልከራከር ይቀንሳል አልኳትና 'አትቀንስም? ' አልኩት በድጋሚ ሻጩን እየተማፀንኩ። 'በቃ ስምንት መቶ ሃምሳ ውሰድ ከዚያ በታች አይሆንም' አለኝ ። እናቴ ወገቤን ጉስም አድርጋ አረ ተወው የያዝኩት ብር አይበቃም ገና ሽንኩርት አልገዛሁም አለችኝ ። ግዛልኝ ከማለት የሚሻል አጠያየቅ ነው ። 'ግድ የለም እኔ ይዤአለሁ ' አልኳት ።
ሻጩ ከምክክራችን በጉጉት መልስ ሲጠብቅ የነበር ይመስላል ዘወር ስል 'እንዳያመልጥህ ውሰደው' አለኝ ።
እኔም ከዶሮው ይልቅ የዶሮው ታሪክ ስለደነቀኝ እሺ ይሁን አልኩት ። ከዚያ ክንፉን ለመያዝ ሲታገል 'ቆይ ቆይ ' ላግዝህ አልኩ እና ወፍራም ገመድ አምጥቼ ' አንገቱ ላይ አጥልቅልኝ እየጎተትኩ ነው የምወስደው 'አልኩት ። ለእናቴ ጅራፍ ገዝቼ ሰጠሗት ። ሻጩ ተገርሞ አየኝ እና 'በግ አረከው እንዴ ' አለኝ ። 'በዚህ ዋጋ ዶሮ ነው የገዛሁት ብዬ ብብቴ ውስጥ ብከተው ማን ያምንኛል 'አልኩት ። በዝግመተ ለውጥ ወደ በግ ቢቀየር እድሌን ልሞክር እንጅ ብዬው ገንዘቡን ቆጥሬ ሰጠሁት እና እናቴን " ጅራፉን እያኖጋሽ ቅረቢልኝ " አልኳት ። እኔ እየጎተትኩ እሷ እየቀረበች እንደምንም ቤት ደረስን ። እውነትም ጀግና ነው ዶሮው ክንፉን እራሱ ሚጠቀመው ላደጋ ጊዜ ብቻ ነው: ማለት እኔን ከምንም አልቆጠረኝም ወይም ወታደራዊ ስልት እያካሄደብኝ ይሆናል ። ብቻ አንድ ትልቅ ችካል ላይ ወስጄ አሰርኩት ። እናቴ ቤት ውስጥ አለ የተባለ ሳፋ (በውሃ ቢለካ አምስት ሊትር በትንሹ የሚችል ) እያዘጋጀች አየሗትና ። 'ምን እያረግሽ ነው ?' አልኳት ። 'እረደው እንጅ በጊዜ እንደሰራው ' አለችኝ ። እኔም ' ብቻዬን ነው ማርደው?' አልኳት ። 'አዎ ' አለችኝ ። ' እኮ የስምንት መቶ ሃምሳ ብር ሙክት ዶሮ ብቻዬን ላርደው??' ስላት። 'ወንድ አይደለህ እንዴ !!!' አለችኝ ። እሱን ተይው ብዬ በሆዴ ' ቆይ ጎረቤት ልጥራ ' አልኩና የሰው ሃይል አሰባሰብኩ ። ሁሉም ከመጡ በኋላ አንዱ አንድ ክንፉን ፣ አንዱ አንድ ክንፉን ፣ አንዱ አንድ እግሩን ፣ አንዱ አንድ እግሩን ፣ አንገቱን እና አፉን ቆልምሞ የሚይዝልኝ ሰው መደብኩ። እናቴ አንዲት ብርቱካን መሰንጠቂያ የምታክል ቢላ ይዛ መጣች። በቃ ምን ልበላት ቆሌዬን ነው የገፈፈችው ። 'አሁን በዚህ ላርደው ነው ወይስ ሙጀሌ ላወጣለት ነው?' አልኳት እና እንዳያመልጣችሁ ብዬ ሰዎቼን አስጠንቅቄ በግራንደር የተሳለ አርባ ገራፊ(ገጀራ) ከጋሻ ጋር ይዤ ስመለስ ሙክቱ ዶሮ ሊያመልጥ እየታገለ ፣ ሰዎቹ ላብ በላብ ሆነዋል ። እንዴ!!! እሄንማ ቶሎ ልጥረበው አልኩ እና ያለ የሌለ አቅሜን አጠራቅሜ ገጀራውን አንገቱ ላይ ባሳርፈው ገጀራው ተጣመመ ። ልደግመው ስል እግሩን አንስቶ ሆዴ ላይ አሳረፈው ። እኔን ለብቻ ፣ ገጀራዬን ለብቻ ፣ ጋሻዬን ለብቻ ፣ ሰዎቼን ለብቻ ለብቻ ገነጣጠለን። ለትንሽ ደቂቃ እራሴን ስቼ ስነሳ ሙክቱ ዶሮ አንድ ኩንታል ጥሬ እናቴን አዞ አስበትኖ ጥሬ እየለቀመ ነው ። እውነትም ኮማንዶ ነው ክንፉን ላደጋ ጊዜ ብቻ የሚጠቀም!!! ። እኔም እናቴን 'የሚያርድ ባለታንክ እና ታንከኛ ሰው ጥሪ ' አልኳት እና በእግራ እግሩ ሳይደግመኝ ቀስ ብዬ ተንፏቅቄ አመለጥኩ ። ማታ ስመለስ እናቴ በርሚል ማን እንዳበደራት አላውቅም ፣ ሙክቱንም ማን እንዳረደው አላውቅም መቀመጫ ቀጣጥላ ቆማ በግምት ሶስት ሜትር ቁመት ያለው ማማሳያ(የወጥ እንጨት) ወገቡን በትከሻዋ ተሸክማ ወጡን እያማሰለች ነበር።
(ሽንኩርቱን በምን ሰዓት ገዝታው ይሆን!!)
~~~~~~~~~~~~~~~~~
ደሱ ተገኝ...
እንኳን ለጌታችን ለመድሃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል በሰላም አደረሳችሁ!!!
@awdetibeb
725 viewsDesu Tegegn, edited 16:48