Get Mystery Box with random crypto!

የዓለም የጤና ድርጅት ናይሪቢ ኬንያ ላይ ለአስቸኳይ አገልግሎት የሚውል የጤና ማዕከል ከፈተ። እንደ | ዶይቸ ቬለን | DW AMHARIC NEWS🇪🇹

የዓለም የጤና ድርጅት ናይሪቢ ኬንያ ላይ ለአስቸኳይ አገልግሎት የሚውል የጤና ማዕከል ከፈተ። እንደ የድርጅቱ ዳይሬክተር ዶክተር ቴዎድሮስ አድሃኖም ገለጻ ማዕከሉ በጤናው ዘርፍ ያለውን አቅም በማጠናከር በመላው አፍሪቃ አስተማማኝ የመድኃኒት እና የህክምና መሳሪዎች ክምችት እንዲኖር ያስችላል። ቅዳሜ ዕለት በዓለም የጤና ድርጅት እና በኬንያ መንግሥት ትብብር የተከፈተው የጤና ማዕከል በአህጉሩ አፋጣኝ ምላሽ ለመስጠት የሚውል በአፍሪቃ ሃገራት የተዘረጋ የመጀመሪያው የግንኙነት መስመር መሆኑ ተገልጿል። ማዕከሉ በውስጡ ራሱን የቻለ የስልጠና ማዕከል፤ ለደረሰ አስቸኳይ የጤና ችግር በ24 ሰዓታት ውስጥ ምላሽ መስጠት ለሚችሉ ባለሙያዎች መኖሪያ ቤት እንዲሁም የህክምና መሳሪያዎች ማከማቻ ስፍራ ይኖረዋል ተብሏል። የዓለም የጤና ድርጅት እንዲህ ያለውን ፈጣን ምላሽ የሚሰጥ የባለሙያዎች ቡድን በሁሉም የአፍሪቃ ሃገራት ለመፍጠር የመርዳት ፍላጎት እንዳለው አመልክቷል። የድርጅቱ የአፍሪቃ ዳይሬክተር ማቲዲሶ ሞኢቲ ለሮይተር እንደገለጹት «አህጉሩ ለቀጣዩ ወረርሽኝ የተሻለ ዝግጁ ለመሆን ያለውን ተግባራዊ ቁርጠኝነት እየገለጸ ነው፤ ይኽ ደግሞ የበለጠ ዝግጁ ሆነው ማላሽ መስጠት እንዲችሉ አቅማቸውን ለማጎልበት በእኛ በኩል የሚደረግ ድጋፍ ነው» ብለዋል። በዚህ መሠረትም አሁን ኬንያ ለአፍሪቃ የህክምና መሳሪያ ማዕከል መሆኗ አጎራባች ሃገራት መድኃኒቶችን በፍጥነት ለማግኘት እንዲችሉ እንደሚረዳ ተገልጿል።