2022-06-16 15:17:12
"አስቀድማችሁ መንግስቱትንና ጽድቁን ፈልጉ "
ማቴ 6÷33
............. ........... ................. ........... ......
" ስለዚህ እላችኋለሁ፥ ስለ ነፍሳችሁ በምትበሉትና በምትጠጡት፥ ወይም ስለ ሰውነታችሁ በምትለብሱት አትጨነቁ፤ ነፍስ ከመብል ሰውነትም ከልብስ አይበልጥምን?" አላቸው
ማቴ 6:25
ጌታችን ይህንን ትምህርት የሰው ልጆች ከሁሉ የቱን ማስቀደም እንዳለባቸው ያስተማረው ትምህርት ነው፡
አንድም ከሁለቱ የቱን ማስቀደም እንዳለባቸው ያስተማረው ነው፡፡
ከሁለቱ የተባለው
1ኛ ከሚያልፈው ዓለምና ከማያልፈው ዓለም
፡-የሚያልፈው ዓለም ይህኛው አሁን የምንኖርበት ዓለም ሲሆን፡፡
፡-የማያልፈው ዓለም ፡- መንግስተ ሰማያት ነው፡፡
2ኛ ከሥጋና ከነፍስ ማለት ነው፡፡
ይህም ስጋ ፡-በሚያልፈው ዓለም ውስጥ ምቾት ተድላ ደስታን ትናፍቃለች ጊዜአዊ ደስታና እርካታ ላይ ታመዝናለች ::
ነፍስ፡- ይህኛው ዓለም ጠፊ ኃላፊ መሆኑን ተገንዝባ የማያልፈውን ያኛውን ዓለም ትናፍቃለች፡፡
ይህንንም ጌታችን በጥልቅ መለኮታዊ ምስጢር ሲያስረዳን፡-
"ለነፍሳችን ምን እንበላለን ምን እንጠጣለን ለሥጋችን ምን እንለብሳለን ብላችሁ አታስቡ " ይለናል::
ምስጢራዊ ትርጉሙ፡- መብል መጠጥን ለነፍስ ሰጥቶ ተናገረ ስለምንድ ነው ብንል የበሉት የጠጡት ደም ይሆናልና ነው በዚህም ምክንያት ነፍስ ከስጋ ጋር ተዋህዳ ትኖራለችና " እስመ ነፍስ ተኃድር በደም " እንዲል፡፡
ልብስን ለስጋ ሰጥቶ ተናገረ ምንም የምታፍር ነፍስ ብትሆን አጊጦ ከብሮ የሚታይ ሥጋ ነውና፡፡
አንድም ካለመኖር ወደመኖር ነፍስን አምጥቼ ሥጋን ከአራቱ ባህርያት አዋሕጄ የፈጠርኳችሁ ለእናንተ ምግብ ልብስ እንዴት እነሳችሗለሁ ሲለን ነው፡፡
አንድም ነፍስን ካለችበት አምጥቼ ሥጋን ካለችበት አስነስቼ ሗላ በመንግስተ ሰማያት መንፈሳዊ ምግብን የምመግባችሁ ዛሬ ለእናንተ ምግብ ልብስ እነሳችሗለሁን ሲለን ነው፡፡
እናንተግን ከሁሉ አስቀድማችሁ መንግስቱንና ጽድቁን ፈልጉ ሊለን ይህን ተናገረን ምክንያቱም የምስጢሩ ፍጻሜ ለነፍሳችሁ ምን እንበላለን ካላችሁ "#ሥጋዬን" ምን እንጠጣለን ካላችሁ ደሜን አንድም ለስጋችሁ ምን እንለብሳለን ካላችሁ #እኔን ሲለን ነው ምክንያቱም የምንራቆተው ከእርሱ ስንለይ መሆኑን ሲነግረን::
ይህንን ሁሉ በምሳሌ ካስረዳን በሗላ እናንተ መጨነቅ ሳይሆን ይህንን ፈልጉ ብሎ ተናገረን እሱም፡- "መንግስቱንና ጽድቁን"
መንግስተ ሰማያት የተባለ ክርስቶስ ፈልጉ ለነፍሳችሁ እረፍት ታገኛላችሁና፡፡
ጸሀየ ጽድቅ ክርስቶስ ፈልጉ ሥጋዊ ፍላጎትን ንቃችሁ ስለ ስሙ ስደትን ትመርጣላችሁና፡፡ " ስለጽድቅ የሚሰደዱ ብፁዓን ናቸው መንግሥተ ሰማያት የእነርሱ ናትና " ማቴ 5÷10 ሲለን ነው፡፡
አንድም አስቀድማችሁ ሃይማኖትን ምግባርን ፈልጉ
አንድም ልጅነትን መንግስተ ሰማያትን ፈልጉ ሲለን ነው፡፡ ይህ ማለት የዚህ ዓለምስ ነገር ሁሉ በእራት ላይ ዳረጎት እንዲጨመር ይጨመርላችሗል፡፡
አንድም ሰለነገ አትጨነቁ ይለናል ይልቁንስ እንዲህ ይለናል "ለነፍሳችሁ በምትበሉት ወይም ለሰውነታችሁ በምትለብሱት አትጨነቁ።"
ሉቃስ 12:22
ከመጨነቅ ይልቅ ይህንን አድርጉ ሲለን ነው ፡-
" በነገር ሁሉ በጸሎትና በምልጃ ከምስጋና ጋር በእግዚአብሔር ዘንድ ልመናችሁን አስታውቁ እንጂ በአንዳች አትጨነቁ።"
ፊል 4:6
ምክንያቱም ይለናል ቅዱስ ጴጥሮስ፡-
" እርሱ ስለ እናንተ ያስባልና የሚያስጨንቃችሁን ሁሉ በእርሱ ላይ ጣሉት።"
1ኛ ጴጥ 5:7
ስለዚህ ክርስቲያን ከምድራዊው ይልቅ ሰማያዊውን ከሚያልፈው ይልቅ የማያልፈውን የሚያስቀድም በምድራዊ ህይወቱ መላካዊ ባህርይን ተለማምዶ በዚች በምታልፈው ዓለም የማያልፈው ዓለም ለማግኘት ከኃላፊው ከጠፊው ቁስ በፊት ጽድቁንና መንግስቱን ሲያስቀድም የሚያስፈልገው ነገር እንደሚሰጠው በማመን ከጭንቀት ተላቆ ተስፋ ክርስቶስ ለብሶ እንዲኖር የተሰጠ ትምህርት ነው፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
@Anketsemedanitsnbttimhirtbet
87 viewsAbay Getaneh, 12:17