Get Mystery Box with random crypto!

✝የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ⛪️ቤተ ክርስቲያን 📖ሥርዓት እና 📜አስተምህሮ (Ethiopian Orthodox Tewahdo church Ethics & Teaching ☑️

የቴሌግራም ቻናል አርማ abweldmenfeskidus1amlak — ✝የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ⛪️ቤተ ክርስቲያን 📖ሥርዓት እና 📜አስተምህሮ (Ethiopian Orthodox Tewahdo church Ethics & Teaching ☑️
የቴሌግራም ቻናል አርማ abweldmenfeskidus1amlak — ✝የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ⛪️ቤተ ክርስቲያን 📖ሥርዓት እና 📜አስተምህሮ (Ethiopian Orthodox Tewahdo church Ethics & Teaching ☑️
የሰርጥ አድራሻ: @abweldmenfeskidus1amlak
ምድቦች: ያልተመደበ
ቋንቋ: አማርኛ
ተመዝጋቢዎች: 192
የሰርጥ መግለጫ

ይህ ድህረ መዋያ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓትና አስተምህሮ የሚተላለፍበት፤ ቅዱሳን ሰማዕታት የሚታወሱበት (የሚዘከሩበት)፤ የተዋሕዶ ልጆች የምንማማርበት ይሆን ዘንድ የእግዚአብሔር መልካም ፍቃዱ ሆኖ÷ እነሆ በእናታችን በቅድስተ ቅዱሳን በንፅህተ ንፁሃን በቅድስት ድንግል ማርያም ዕለት በ ፳፩/፲፩/፳፻፲፪ ተከፈተ::
የጻድቃን ሰማዕታት : የቅዱሳን በረከት ይደርብን፤ አሜን!

Ratings & Reviews

3.00

3 reviews

Reviews can be left only by registered users. All reviews are moderated by admins.

5 stars

0

4 stars

2

3 stars

0

2 stars

0

1 stars

1


የቅርብ ጊዜ መልዕክቶች 2

2022-07-07 22:03:23 በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ:: አሜን!

ወርኃ ሐምሌ
ቀን ፩ (1)

እንኳን ለተባረከ ወር ሐምሌ እና ለቅዱሳኑ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፣ አደረሰን።

እግዚአብሔርን ቸር የምንለው በባሕርዩ ፍጹም ቸር በመሆኑ ነው:: ይሕንን ደግሞ ለማረጋገጥ መቅመስ ይቻላል:: ይገባልም:: (መዝ. 33:7) ይሔው ደግሞ ያን ሁሉ ኃጢአታችንን ታግሶ ከወርኀ ሐምሌ አደረሰን:: ለዚሕ ቸርነቱ አምልኮ : ውዳሴና ስግደት ይገባዋል::
ለወርኀ ነሐሴ ደግሞ እንዲያደርሰን ልንማጸነው ይገባል::


" ቅዱስ አግናጥዮስ ሐዋርያዊ ሊቅ "

ሐዋርያዊ ጳጳስና ሰማዕት ቅዱስ አግናጥዮስ ገና በልጅነቱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ያየ : ራሱ ጌታችን ትንቢት የተናገረለት (ማቴ.18:1) እና ከጌታ ዕርገት በኋላ ሐዋርያትን የተከተለ አባት ነው:: ጌታ ሲያርግ የአምስት ዓመት ሕፃን ሲሆን ከሰላሳ ስድስት ዓመታት በላይ ሐዋርያትንና ቤተ ክርስቲያንን አገልግሏል::

ዕድሜው ወደ አርባዎቹ ሲደርስ (ኢየሩሳሌም በጠፋችበት ዓመት - በ70 ዓ/ም) እርሱ የአንጾኪያ ሊቀ ጳጳሳት ሆኖ ተሹሟል:: አስቀድሞ ከወንጌላዊ ቅዱስ ዮሐንስ እግር ምሥጢርና ፍቅርን ጠጥቷልና የተለየ ሰው ነበር:: ቅዱስ አግናጥዮስ ከአንጾኪያ እየተነሳ ምድረ እስያንም በወንጌል ዕርፈ መስቀል አርሷል::

በአካል ያልደረሰባቸውን በጦማር (በክታብ) አስተምሯል:: በአካሉ እንኳ ምንም በጾም በጸሎትና በብዙ ድካም የተቀጠቀጠ ቢሆን ግርማው የሚያስፈራ ነበር:: ከነገር ሁሉ በኋላ የወቅቱ ቄሣር ጠራብሎስ ይዞ አሰቃይቶ ለአንበሳ አስበልቶታል:: በዚህ ምክንያት "ምጥው ለአንበሳ-ለአንበሳ የተሰጠ" እየተባለ ይጠራል::

" አባ ብዮክ እና አባ ብንያሚን "

እነዚህ ቅዱሳን የሥጋ ወንድማማቾች ናቸው:: ካህን አባታቸው በሚገባ ቢያሳድጋቸው እነሱም ገና በወጣትነት የሚደነቅ የክህነት አገልግሎትን ሰጥተዋል:: ሙሉ ሌሊት ለጸሎት : ሲነጋ ለኪዳን : በሠርክ ደግሞ ለቅዳሴ ይፋጠኑ ነበር:: ሁሌም በየቤቱ እየዞሩ የደከመውን ሲያበረቱ : የታመመውን ሲፈውሱ : ያዘነውን ሲያጽናኑ ውለው ትንሽ ቂጣ ለራት ይመገባሉ::

ሰውነታቸው በፍቅር ሽቱ የታሸ ነበርና ብዙዎችን መለወጥ ቻሉ:: አንዴ ቅዳሴ ሊገቡ ሲሉ "አባታችሁ ሊሞት ነው" ቢሏቸው "ሰማያዊው አባት ይቀድማል" ብለው ቀድሰዋል:: አባታቸውንም ቀብረውታል:: በመጨረሻ ግን አንድ ቀን ለመስዋዕት ብለው ያዘጋጁትን የበረከት ሕብስት እባብ በልቶባቸው አገኙ:: እንደ ምንም ፈልገው እባቡን ገደሉት::

ነገር ግን ያ የተባረከ ሕብስት በሆዱ ውስጥ ነበርና ምን ያድርጉት? ጌታን ስለ ማክበር ሊበሉት ፈልገው ጌታን ቢጠይቁት መልአኩ መጥቶ "ሰማዕትነት ሆኖ ይቆጠርላቹሃል" አላቸው:: ሁለቱ ወንድማማቾች ብዮክና ብንያሚን ፈጣሪያቸውን አመስግነው በሉት:: ምዕመናን ወደ ቤተ ክርስቲያን ሲገቡ ሁለቱንም እንደተቃቀፉ ዐርፈው አገኟቸው:: መልካም እረኞቻቸው ናቸውና ከታላቅ ለቅሶ ጋር ቀብረዋቸዋል::


" ቅድስት ቅፍሮንያ ሰማዕት ወጻድቅት "

ይህቺ ቅድስት እናታችን ደግሞ ገና በአሥራ ሁለት ዓመቷ ታላቅ እህቷን ተከትላ ገዳም ትገባለች:: በሚገርም ተጋድሎ በጥቂት ጊዜ አጋንንትን አሳፍራ መነኮሳይያትንም አስገርማቸዋለች:: ትጋቷ ግሩም ነበርና ስትታዘዝ : ስትጸልይና ስትሰግድ ያለ እንቅልፍና ምግብ ቀናት ያልፉ ነበር:: በዚህ የተቆጣ ሰይጣን አረማዊ መኮንንን ይዞባት መጣ::

ሌሎች ደናግል ሲያመልጡ እርሷ ለመከራ ተዘጋጅታ ጠበቀችው:: አዕምሮ የጎደለው መኮንኑም ክርስቶስን ካልካድሽ ብሎ ጽኑዕ ጽኑዕ መከራን አመጣባት:: በተጋድሎ ባለቀ አካሏ ሁሉንም ቻለች:: በዚህች ቀን ግን አንገቷን በሰይፍ አስቆርጧታል::

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የወዳጆቹን ትዕግስትና ጽናት ለእኛም ያድለን:: ከበረከታቸውም ይክፈለን::


" ቅዱስ ቶማስ "

ዳግመኛ በዚህ ቀን ሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ ይታሰባል::
ይኸውም ከሕንድ አውራጃዎች በአንዱ ወንጌልን ሰብኮ እኩሎቹ ሲያምኑ እኩሎቹ እንቢ አሉ:: ቅዱስ ቶማስም ያመኑትን "ከጣዖት አምልኮና ከዝሙት ሽሹ" ብሎ መከራቸው::

ምክሩን ከሰሙት አንዱ በዚያው ምሽት ሊጠጣ ወደ መሸታ ቤት ይገባል:: ሰው ሁሉ ከወጣ በኋላ ባለ መሸተኛዋ ሴት እንደለመደችው አብረው እንዲተኙ ስትጠይቀው "እንዴት ሐዋርያው ከዝሙት ሽሹ እያለ እንዲህ ትይኛለሽ?" በሚል ሰይፍ አውጥቶ አንገቷን ቆረጣት::

እርሱ መልካም ያደረገ መስሎታል:: የሠራው ሥራ (መግደሉ) ግን አሕዛባዊ ግብር ነው:: በማግስቱ ቅዱስ ቶማስ ነገሩን ሰምቶ ሰዎችን ሰበሰበና "ይህንን የአውሬ ድርጊት የፈጸመ ማነው?" ሲል ጠየቀ:: ፈጻሚው ግን አልታወቅም በሚል ዝም አለ:: ወዲያው ቅዱሱ ሐዋርያ ዳቦ አንስቶ ቆረሰና "ለበረከት እያነሳችሁ ውሰዱ" አለ:: ሰውየው ተራውን ጠብቆ ሊያነሳ ሲል እጁ ሰለለች::

ሐዋርያው "ምነው ልጄ! ምን ሆንክ?" አለው:: እሱም እንዳላመለጠ ሲያውቅ እውነቱን ተናዘዘ:: ቅዱስ ቶማስ ግን ሕዝቡ ሁሉ እንደተሰበሰበ ያን ወጣት ገስጾ "አስከሬኑን አምጡልኝ" አለ::

የወጣቱን እጅ ፈውሶ "በል የገደልኩሽ እኔ:: የሚያስነሳሽ ግን ጌታየ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው:: ብለህ አንገቷን ቀጥለው" አለው:: እንዳለው ቢያደርግ የሞተችው አፈፍ ብላ ተነሳች:: ይህንን ተአምር ያዩ አሕዛብ አምነው ተጠምቀዋል::

=> ከሐዋርያው በረከት ይክፈለን:: አሜን!


ሐምሌ 1 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት

1.ቅዱስ አግናጥዮስ ሐዋርያዊ ሰማዕት
2.አበው ቅዱሳን ብዮክና ብንያሚን
3.ቅድስት ቅፍሮንያ (ሰማዕት ወጻድቅት)
4.ቅዱስ ቶማስ ሐዋርያ
5.አቡነ ገብረ መድኅን ጻድቅ
6.አባ ክልዮስ ዘሮሜ

ወርኀዊ በዓላት

1.ልደታ ለማርያም ድንግል እግዝእትነ
2.ቅዱሳን ኢያቄም ወሐና
3.ቅዱስ ራጉኤል ሊቀ መላእክት
4.ቅዱስ በርተሎሜዎስ ሐዋርያ
5.ቅዱስ ሚልኪ ትሩፈ ምግባር

ንባብ

"በዚያች ሰዓት ደቀ መዛሙርቱ ወደ ጌታ ኢየሱስ ቀርበው "በመንግስተ ሰማያት ከሁሉ የሚበልጥ ማን ይሆን?" አሉት::
ሕፃንም ጠርቶ በመካከላቸው አቆመ:: እንዲህም አለ:- "እውነት እላቹሃለሁ:: ካልተመለሳችሁ እንደ ሕፃናትም ካልሆናችሁ ወደ መንግስተ ሰማያት ከቶ አትገቡም::
እንግዲህ እንደዚህ ሕፃን ራሱን የሚያዋርድ ሁሉ በመንግስተ ሰማያት የሚበልጥ እርሱ ነው:: "
(ማቴ. ፲፰፥፩)

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ዝክረ ቅዱሳን
23 views19:03
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-07 06:42:14 ††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †††

ወርኃ ሰኔ
ቀን ፴ (30)

እንኳን ለመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ዓመታዊ የልደት በዓል በሰላም አደረሳችሁ::

" ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ"

ቅዱስ ወንጌል ላይ ከእመቤታችን ቀጥሎ የነዘካርያስን ቤተሰብ ያህል ክብሩ የተገለጠለት ፍጡር ይኖራል ብሎ መናገሩ ይከብዳል:: ቅዱስ ሉቃስ ወንጌሉን የጀመረው በዚህ ቅዱስ ቤተሰብ ነውና መንፈስ ቅዱስ እንዲህ ሲል አጽፎታል:: "ዘካርያስ ካህኑና ቅድስት ኤልሳቤጥ በሰውና በእግዚአብሔር ፊት ያለ ነቀፋ የሚኖሩ ጻድቃን ነበሩ" ይላቸዋል:: (ሉቃ. 1:6)

+የሰውን እንተወውና በእግዚአብሔር ፊት ያለ ነቀፋ መኖር ምን ይረቅ? ለዚህ አንክሮ (አድናቆት) ይገባል!
እሊህ ቅዱሳን ባልና ሚስት ግን መካኖች በመሆናቸው ልጅ ሳይወልዱ ዘመናቸው አልፎ ነበር:: እንደ ቤተ ክርስቲያን ትውፊት ዕድሜአቸው የኤልሳቤጥ 90 የዘካርያስ 100 ደግሞ ደርሶ ነበር:: ፍጹም መታገሳቸውን የተመለከተ ጌታ ግን በስተ እርጅናቸው ከሰው ሁሉ በላይ የሆነ: ትንቢት ለብቻው የተነገረለት (ኢሳ. 40:3, ሚል. 3:1) ታላቅ ነቢይን ይሰጣቸው ዘንድ መልአከ ብሥራት ቅዱስ ገብርኤልን ላከላቸው::

+ቅዱስ ዘካርያስ ሰው ነውና ከደስታ ብዛት በመከራከሩ ድዳ ሆነ:: ቅድስቲቷ ግን መስከረም 26 ቀን ታላቁን ሰው ጸንሳ ለ6 ወራት ራሷን ሠወረች:: በ6ኛው ወር የፍጥረት ሁሉ ጌታ በተጸነሰ ጊዜ የአርያም ንግሥት ድንግል እመቤታችን ደጋ ደጋውን ወደ ኤልሳቤጥ መጣች:: ሁለቱ ቅዱሳት የእህትማማች ልጆች ናቸው::

+የአምላክ እናቱ ስትደርስና "ሰላም" ስትላቸው መንፈስ ቅዱስ በእናትና ልጅ ወርዶ ኤልሳቤጥ በምስጋና: ዮሐንስ ደግሞ ገና በማሕጸን ሳለ በደስታ ዘለለ (ሰገደ):: ከዚህ በሁዋላ በዚህች ቀን (ሰኔ 30) ተወልዶ: አባቱ ዘካርያስ "ዮሐንስ" ሲለው አንደበቱ ተፈትቶለታል::

=>መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ
+የቅዱሳኑ ዘካርያስና ኤልሳቤጥ ልጅ
+በማሕጸን ሳለ መንፈስ ቅዱስ የሞላበት
+በበርኀ ያደገና በገዳማዊ ቅድስና ያጌጠ
+እሥራኤልን ለንስሃ ያጠመቀ
+የጌታችንን መንገድ የጠረገ
+ጌታውን ያጠመቀና
+ስለ እውነት አንገቱን የተቆረጠ ታላቅ ሰው ነው::

+ስለዚሕም ቤተ ክርስቲያን ነቢይ: ሐዋርያ: ሰማዕት: ጻድቅ: ገዳማዊ: መጥምቀ መለኮት: ጸያሔ ፍኖት: ቃለ ዐዋዲ ብላ ታከብረዋለች::


" አባ ጌራን ሕንዳዊ "

ዳግመኛ በዚህች ቀን ሕንድ ካፈራቻቸው ታላላቅ ቅዱሳን አንዱ የሆኑት ጻድቁ አባ ጌራን ይታሰባሉ:: የእኒህ ቅዱስ ታሪክ አሳዛኝ ነው:: ቅዱሱ በሕንድ ተወልደው: በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን አድገው: ገና በወጣትነታቸው መንነው: ደሴት ውስጥ ወደሚገኝ አንድ በርሃ ገብተዋል:: ከገድላቸው ጽናት: ከቅድስናቸውም ብዛት የተነሳ በሃገረ ሕንድ ሰይጣን እንዳይገባ: ጠብ ክርክር እንዲጠፋ: ሰው ሁሉ በፍቅርና በሰላም እንዲኖር ማድረግ ችለው በጣም ተወዳጅ ነበሩ::

+በዚህ የተበሳጨ ሰይጣን ግን ባልጠረጠሩት መንገድ መጣባቸው:: አንዲት ሴት ወደ እርሳቸው መጥታ (የንጉሡ ልጅ ነኝ በሚል) አስጠግተዋት ነበር:: አንድ ሌሊት ላይ ግን አውሬ ያባረራት በመምሰል ሩጣ ወደ ቤታቸው ገብታ አቀፈቻቸው:: በዚያ ቅጽበት ፍጡር ደካማ ነውና ታላቁ አባ ጌራን ተሰነካከሉ:: ከአፍታ በሁዋላ የሆነውን ሲያውቁ ደም አለቀሱ::

+ልብሳቸውን ቀደው: እንባቸው እንደ ዥረት እየፈሰሰ አለቀሱ:: ራሳቸውን በትልቅ ድንጋይ እየቀጠቀጡት የጭንቅላታቸውና የደረታቸው አጥንቶች ተሰባበሩ:: እርሱ እግዚአብሔር መሐሪ ነውና ይቅር ብሎ: የቅድስና ስም ሰጥቶ በዚሕች ቀን ወደ ገነት አሳርጉዋቸዋል:: ለዚህ ነው መጽሐፉ "ጻድቅ 7 ጊዜ ይወድቃልና: ይነሣማል" ያለው:: (ምሳ. 24:16)

=>አምላካችን ከቅዱሱ ቤተሰብና ከጻድቁ አባ ጌራን በረከት ይክፈለን:: አሜን!


ሰኔ 30 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት

1.ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቀ መለኮት (ልደቱ)
2.ቅዱሳን ዘካርያስና ኤልሳቤጥ (ወላጆቹ)
3.አባ ጌራን መስተጋድል (ሕንዳዊ)
4.ቅዱሳት ደናግል ማርያና ማርታ (ከ36ቱ ቅዱሳት አንስት-የአልዓዛር እህቶች)

ወርኀዊ በዓላት

1.ቅዱስ ማርቆስ ዘአንበሳ (ሐዋርያ)
2.አባ ሣሉሲ ክቡር
3.ቅዱስ ጐርጐርዮስ ነባቤ መለኮት
4.ቅድስት ሶፍያ ሰማዕት

ንባብ

" ደግሞም አንተ ሕጻን ሆይ የልዑል ነቢይ ትባላለህ:: መንገዱን ልትጠርግ በጌታ ፊት ትሔዳለህና:: እንደዚህም የኃጢአታቸው ስርየት የሆነውን የመዳን እውቀት ለሕዝቡ ትሰጣለህ:: ይሕም ከላይ የመጣ ብርሃን በጐበኘበት በአምላካችን ምሕረትና ርኅራኄ ምክንያት ነው:: "
(ሉቃ. 1:76)

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ዝክረ ቅዱሳን
29 views03:42
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-05 20:27:03 በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ:: አሜን!

ወርኃ ሰኔ
ቀን ፳፱ (29)

እንኩዋን ለቅዱሳን ነገሥታት "ማርቆስ እና ቴዎድሮስ" ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ::

=>ማንኛውም ሰው
¤ቢጾም ቢጸልይ
¤መልካም ቢሠራ
¤ለእግዚአብሔር ቢገዛ
¤አልፎም ቢመንን ይደነቃል:: ይሕንን ሥራ ንጉሥ ሆነው ስለ ሠሩትስ ምን እንላለን? ማድነቅ የሚለው ቃል የሚገልጸው አይመስለኝም::

¤ወርቅና ብር በእግር እየተረገጠ
¤የሚበላውና የሚጠጣው ተትረፍርፎ ሳለ
¤አገር ምድሩ እየሰገደላቸው
¤ሁሉ በእጃቸው
¤ሁሉም በደጃቸው ሳለ...
ይህንን ሁሉ ስለ #ክርስቶስ ፍቅር የተውትን ጻድቃን ነገሥታት የክብር ክብር ይገባቸዋል:: ከእነዚህ መካከል ዛሬ የሚከበሩትን 2ቱን እናዘክር::

" ቅዱስ ማርቆስ ንጉሠ ሮም "

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ይህንን ቅዱስ ጻድቅ: የዋህ: ንጹሕና ገዳማዊ ብላ ትጠራዋለች:: ሮም እንደ ዛሬ ጠባብ ከተማ ሳትሆን ዓለምን በክንዷ ሥር ቀጥቅጣ የምትገዛ ኃያል ሃገር ነበረች:: ቅዱስ ማርቆስ የልዑላኑ ቤተሰብ ነውና በሮም ተወልዶ በእመቤታችን ቤተ መቅደስ ውስጥ አድጉዋል::

+የየዕለት ሙያው ጾምና ጸሎት: መጻሕፍትንም መመልከት ነበር:: ነባሩ ንጉሥ ሲሞት መሣፍንቱ ቅዱስ ማርቆስን በድንግልናው ገና ወጣት ሳለ በዚያች ታላቅ ሃገር ላይ አነገሡት:: ንጉሥ ቢሆንም ሙሉውን ሌሊት በእመቤታችን ፊት ሲጸልይና ሲያለቅስ ያነጋ ነበር::

+ስለ ፍቅርም ድንግል ማርያም ተገልጻ "ምን ላደርግልህ ትወዳለህ?" አለችው:: ቅዱስ ማርቆስም "ለሕዝቡ ፍቅር አንድነትን ሰላምን ስጪልኝ:: እኔ በማስተዳድርበት ቦታ ሁሉ ጠብ ክርክር ይጥፋልኝ:: ፍቅር ይንገስልኝ" ሲል መለሰላት:: ድንግል እመቤታችንም "እንደ ቃልህ ይሁን" ብላ አጋንንት ወደ ሃገሩ እንዳይገቡ ከለከለችለት:: በዚህም ቅዱስ ማርቆስ ከነገሠ ጀምሮ ለ5 ዓመታት ጠብ ክርክር: ክፋትና ችግር አልነበረም:: ሁሉም ተፋቅሮን ያጸና ነበር እንጂ::

+ከ5 ዓመታት በሁዋላ ግን ሕዝቡና ሹማምንቱ ተሠብስበው አንድ ነገርን መከሩ:: #ቅዱስ_ማርቆስን አጋብተው ለብዙ ጊዜ እንዲመራቸው ማለት ነው:: ምክንያቱም አኗኗሩ እንደ መነኮሳት ነውና ጠፍቶ እንዳይሔድ በመስጋታቸው ነው:: ከዚያም የሕዝቡ አለቆች ተመርጠው ሃሳባቸውን አቀረቡለት:: እርሱ ግን ጭንቅ ሆነበት:: ጭራሹኑ እንዲህ ዓይነት ሃሳብ መጥቶበት አያውቅም::

+"እስኪ በጸሎት ላስብበት" ብሎ መለሳቸው:: እነርሱ ግን ወደውታልና ድጋሚ ተሰብስበው ሌላ ነገርን መከሩ:: እርሱ ሳያውቅ መልካም ሴት መርጠው: ሥርዓተ ተክሊል አዘጋጅተው: ድግሱንም አዘጋጅተው በግድም ቢሆን ሊያጋቡት ቆረጡ:: ቅዱስ ማርቆስ የተደረገውን ሁሉ ፈጣሪ ገልጦለት በጣም ደነገጠ::

+ፈጥኖ ወደ #እመ_ብርሃን ስዕል ቀርቦ አለቀሰ:: "#እመቤቴ! እኔ ካንቺ ጋር እንጂ ከዚህ ዓለም ጋር መኖር አልችልም" አላት:: እመ ብርሃን ከሰማይ ወደ እርሱ ወርዳ "የምነግርህን ስማኝ:: በሌሊት ተነስተህ ወደ ማሳይህ በርሃ ሒድ" ብላው ተሠወረች:: ቅዱስ ማርቆስ ደስ እያለው የንግሥና ልብሱን ጥሎ: ቆሻሻ ጨርቅ ለብሶ በሌሊት ከቤተ መንግስቱ ወጣ::

+ወደ ሁዋላ አልተመለከተም:: እመቤታችን እየመራችው #ደብረ_ቶርማቅ የሚባል በርሃ ውስጥ ባሕር ተከፍሎለት ገባ:: ሕዝቡ መልካም እረኛ መሪን አጥቷልና በሮም ከተማ ታላቅ ለቅሶና ሐዘን ተደረገ:: ቅዱስ ማርቆስ ግን በደብረ ቶርማቅ በጾም: በጸሎትና በተጋድሎ ማንንም ሳያይ ለ60 ዓመታት ኖረ::

+በዚህች ቀንም ዐርፎ ወደ ወደደው ክርስቶስ ሒዷል:: ሥጋውን የሚቀብር አልነበረምና ከሰማይ 12ቱ ሊቃነ መላእክትና 12ቱ ሐዋርያት ወረዱ:: በዝማሬ ሲገንዙትም በድኑ ከመሬት 5 ክንድ ከፍ ብሎ ተንሳፈፈ::
መላእክቱና ሐዋርያቱም በማሕሌት እዚያው ደብረ ቶርማቅ ውስጥ ቀብረውታል::

"ቅዱስ_ቴዎድሮስ ንጉሠ ኢትዮዽያ "

በሃገራችን ታሪክ በጣም ተወዳጅ ከነበሩ ነገሥታት #ጻድቁ_ቴዎድሮስ ቅድሚያውን ይወስዳል:: በርግጥ በርካቶቻችን የምናውቀው ስለ ሃገሩ ፍቅር ራሱን የሰዋውን ዳግማዊ ዐፄ ቴዎድሮስን (1845-1860) ነው:: በበጎ ሥራውና በቅድስና ሕይወቱ የተመሠከረለት ግን ዛሬ የምናስበው ቀዳማዊው ነው::

+ቀዳማዊ ዐፄ ቴዎድሮስ የደጉ #ዐፄ_ዳዊት (#ግማደ_መስቀሉን ያመጡት) እና የተባረከችው ሚስታቸው #ፅዮን_ሞገሳ ልጅና የጻድቁ ዐፄ #ዘርዐ_ያዕቆብ ታላቅ ወንድም ነው::

+በኢትዮዽያ ለ3 ዓመታት (ከ1396-1399) ብቻ ነግሦ እያለ እንደ ንጉሥ ሳይሆን
¤ከጠዋት እስከ ማታ ድሃ እንዳይበደል: ፍርድ እንዳይጉዋደል ይታትር የነበር:
¤ጾምና ጸሎትን የሚያዘወትር:
¤ወገቡን ታጥቆ ነዳያንን የሚያበላ:
¤ለአብያተ ክርስቲያናትም የሚጨነቅ ደግ ሰው ነበር::

+ስለዚህም በሕዝቡ እጅግ ተወዳጅ ነበር:: በነገሠ በ3 ዓመቱ ዐርፎ በዝማሬና በለቅሦ ሥጋውን ተሸክመው ሲሔዱ ወንዝ ተከፍሎላቸዋል:: ከመቃብሩም ላይ ጸበል ፈልቁዋል::

=>ቸር አምላክ መልካም መሪ ለሃገራችን: በጐ እረኛንም ለነፍሳችን ያድለን:: ከቅዱሳን ነገሥታቱም ጸጋ በረከትን ይክፈለን:: አሜን!


ሰኔ 29 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት

1.ቅዱስ ማርቆስ ንጉሠ ሮም (ጻድቅ: ንጹሕና ገዳማዊ)
2.ቅዱስ ቴዎድሮስ ጻድቅ (ንጉሠ ኢትዮዽያ)
3.ቅዱስ ዓምደ ሚካኤል ኢትዮዽያዊ (ፍልሠቱ)
4."7ቱ" ቅዱሳን መስተጋድላን (አባ አብሲዳ: አባ ኮቶሎስ: አባ አርድማ: አባ ኒኮላስ: አባ ሙሴ: አባ እሴይ: አባ ብሶይ)
5.ቅዱሳን አባ ሖር: አባ ብሶይ: አባ ሖርሳና እናታቸው ቅድስት ይድራ (ሰማዕታት)

ወርኀዊ በዓላት

1.የፈጣሪያችንና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ልደት
2.ቅድስት አርሴማ ድንግል
3.ቅዱስ ዼጥሮስ ተፍጻሜተ ሰማዕት
4.ቅዱስ ማርቆስ ዘቶርማቅ
5.ቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስ ኢትዮዽያዊት
6.ቅዱስ ዘርዐ ክርስቶስ (ጻድቅና ሰማዕት)

ንባብ

" አቤቱ በኃይልህ ንጉሥ ደስ ይለዋል::
በማዳንህ እጅግ ሐሴትን ያደርጋል::
የልቡን ፈቃድ ሰጠኸው::
የከንፈሩንም ልመና አልከለከልኸውም::
በበጐ በረከት ደርሰህለታልና::
ከከበረ ዕንቁ የሆነ ዘውድን በራሱ ላይ አኖርህ::
ሕይወትን ለመነህ ሰጠኸውም::
ለረጅም ዘመን ለዘለዓለሙ::
በማዳንህ ክብሩ ታላቅ ነው:: " (መዝ. 20:1-5)

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ዝክረ ቅዱሳን
33 views17:27
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-04 22:35:30 ††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ:: አሜን! †††

ወርኃ ሰኔ
ቀን ፳፰ (28)

እንኩዋን ለስደተኛው ሊቀ ዻዻሳት "አባ ቴዎዶስዮስ" ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ::

" አባ ቴዎዶስዮስ "

ጻድቁ ሊቀ ዻዻሳት ተወልዶ ያደገው በምድረ ግብጽ በ6ኛው መቶ ክ/ዘመን ነው:: ከልጅነቱ መጻሕፍትን ተምሮ በመንኖ ጥሪት የሚኖር ደግ ሰው ነበር:: ያ ዘመን መለካውያንና ልዮናውያን (ክርስቶስን 2 ባሕርይ የሚሉ) የሰለጠኑበት ዘመን ነበር:: በአንጻሩ ደግሞ ተዋሕዶን የሚያምኑ ሊቃውንትና ምዕመናን ቁጥራቸው የተመናመነ ነበር::

+ችግሩ ግን ይህ ብቻ አልነበረም:: በጊዜው ተዋሕዶን አምኖ መገኘት እስከ ሞት የሚደርስ ዋጋንም ያስከፍል ነበር:: ለዚሕም ነው ሮማውያን ሃይማኖትን በግድ ለማስለወጥ ከነገሥታቱ ጋር የተቆራኙት:: #ቅዱስ_ዲዮስቆሮስ ጋግራ ደሴት ውስጥ ከተገደለ በሁዋላ በግብፅ የተሾሙ ሊቃነ ዻዻሳት አብዛኞቹ መከራና ስደትን ቀምሰዋል:: ትልቁን ቦታ ግን #አባ_ቴዎዶስዮስ ይወስዳል::

+አባ ቴዎዶስዮስ ለእስክንድርያ (ግብፅ) 33ኛ ፓትርያርክ ነው:: እረኝነት (ዽዽስና) እንዳሁኑ ዘመን ሠርግና ምላሽ አይደለምና ገና እንደ ተሾመ የቀረበለት ጥያቄ አንድ ነበር:: "ተዋሕዶን ትተህ መለካዊ ትሆናለህ ወይስ የሚከተልብህን ፍርድ ትቀበላለህ?" አሉት:: ይህንን ያሉት ከንጉሡ ዮስጢያኖስ የመጡ መልእክተኞች ነበሩ:: መልሱ ፈጣን ሆነባቸው:: "እኔንም ሆነ ሕዝቤን ከቀናችው እምነታችን በምንም ልትለዩን አትችሉም" አላቸው::

+በዚህ ምክንያት በቀጥታ ግዞት (ስደት) ተፈረደበት:: ወደ በርሃ ሲያግዙት ካህናት : መምሕራንንና ምዕመናንን አደራ ብሏቸው ነው የሔደው:: መናፍቃኑ እሱን ካሰደዱ በሁዋላ ሕዝቡን ለመቀየር ብዙ ደክመዋል:: ግን ሊሳካላቸው አልቻለም:: ምክንያቱም አደርነትን የማይረሱ ደጋግ መምሕራን ነበሩና ነው::

+በዚያ ላይ አባ ቴዎዶስዮስ #ጦማር (መልእክት) በየጊዜው ይጽፍላቸው ነበር:: እጅግ ብዙ ከሆኑት መልእክቶቹ የተወሰኑት ዛሬም ድረስ #ሃይማኖተ_አበው መጽሐፍ ውስጥ ይገኛሉ::

+በዚሕ አስቸጋሪ ዘመን መልካም ነገሮችም ነበሩ:: ቀዳሚው #ማሕቶተ_ተዋሕዶ #ቅዱስ_ያዕቆብ_ዘእልበረዳይ ሲሆን 2ኛው ደግሞ የንጉሡ ሚስት የተባረከችው #ታኦድራ ናት::

+አባ ቴዎዶስዮስ በግዞትና በስደት ሳለ ንግሥቲቱ ትራዳው : ምዕመናንንም ትንከባከብ ነበር:: ቅዱስ ያዕቆብ ከሊቀ ዻዻሱ ዘንድ ክህነትን ተቀብሎ ከሶርያ እስከ ምድረ ግብጽ ስለ #ተዋሕዶ ሕልውና ተጋድሏል:: ምናልባትም ከሐዋርያው #ቅዱስ_ዻውሎስ በሁዋላ በፈሊጥ ክርስትናን በማስፋፋት ቀዳሚ አባት ነው:: (በነገራችን ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ ማዕተብ ማሰርን ያስተማረ አባትም ነው)

+2ቱ (አባ ቴዎዶስዮስና ቅዱስ ያዕቆብ) ስለ ቀናች ሃይማኖት ብዙ ስለ ደከሙ የዘመኑ ምዕመናን በስማቸው "#ያዕቆባውያን እና #ቴዎዶስዮሳውያን" ተብለው ተጠርተዋል:: አባ ቴዎዶስዮስ ግን ሲታሠር ሲፈታ : ሲሰደድ ሲመለስ ብዙ ተሰቃየ::

+ሕዝቡን ግን በመልካም እረኝነት ጠብቆ : ከተኩላ አፍ ታደገ:: በዚህች ቀንም ዐርፎ ተቀብሯል:: በፓትርያርክነት ያገለገለባቸው ዘመናት 32 ዓመታት ሲሆኑ ከእነዚህ ዓመታት 28ቱ ያለቁት በስደትና በመከራ ነው::

=>እግዚአብሔር የአባቶቻችን ስደት አስቦ ከነፍስ ስደት ይሰውረን:: ከበረከታቸውም ያድለን::


ሰኔ 28 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት

1.አባ ቴዎዶስዮስ ሊቀ ዻዻሳት
2.ቅዱስ ያዕቆብ ዘእልበረዳይ
3.ቅዱስ ባስልዮስ
4.ቅዱስ ባሊዲስ

ወርኀዊ በዓላት

1.አማኑኤል ቸር አምላካችን
2.ቅዱሳን አበው (አብርሃም: ይስሐቅና ያዕቆብ)
3.ቅዱስ እንድራኒቆስና ሚስቱ ቅድስት አትናስያ
4.ቅድስት ዓመተ ክክርስቶስ
5.ቅዱስ ቴዎድሮስ ሮማዊ (ሰማዕት)

ንባብ

" ስለ ጽድቅ የሚሰደዱ ብጹዓን ናቸው:: መንግስተ ሰማያት የእነርሱ ናትና:: ሲነቅፉአችሁና ሲያሳድዷችሁ በእኔም ምክንያት ክፉውን ሁሉ በውሸት ሲናገሩባችሁ ብጹዓን ናችሁ:: ዋጋችሁ በሰማያት ታላቅ ነውና ደስ ይበላችሁ:: ሐሴትም አድርጉ:: ከእናንተ በፊት የነበሩትን ነቢያትን እንዲሁ አሳደዋቸዋልና:: " (ማቴ. 5:10)

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ዝክረ ቅዱሳን
24 views19:35
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-03 18:40:27 ††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ:: አሜን! †††

ወርኃ ሰኔ
ቀን ፳፯ (27)

እንኳን ለሐዋርያው ቅዱስ ሐናንያ እና ለሰማዕቱ ቅዱስ ቶማስ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፣ አደረሰን።

" ቅዱስ ሐናንያ ሐዋርያ "

ሐናንያ ቁጥሩ ከ72ቱ አርድእት ሲሆን መጽሐፍ ቅዱስ ላይ ስማቸው ተመዝግቦ ከተቀመጠልን ከጥቂቶቹ ዋነኛው ነው:: ከነገደ እሥራኤል ተወልዶ : በሕገ ኦሪት አድጐ : ከወጣትነት ዕድሜው ትንሽ እልፍ ሲል ጌታችን ወንጌልን ማስተማር ጀምሯልና ጠራው:: እርሱም በበጐ ፈቃድ ተከትሎታልና ከ72ቱ አርድእት ደመረው::

ለ3 ዓመታት ከጌታ እግር ተምሮ : ከዕለተ ስቅለት በፊት ሀብተ ፈውስም ተሰጥቶት ነበር:: ምክንያቱም ቅዱስ ሉቃስ እንደ ጻፈልን ሰብዐው አርድእት "ጌታ ሆይ! አጋንንት በስምህ ተገዙልን" ማለታቸውን አስቀምጦልናል:: (ሉቃ. 10:17) ቅዱስ ሐናንያ በበዓለ ዕርገት ተባርኮ በ50ኛው ቀንም መንፈስ ቅዱስን ተቀብሎ ለስብከተ ወንጌል ወጥቷል::

በሚያስተምር ጊዜ የሶርያዋን ደማስቆን ማዕከል አድርጐ ነበር:: በሁዋላም አበው ሐዋርያት የዚህች ከተማ የመጀመሪያው ዻዻስ አድርገው ሹመውታል:: ጌታ ባረገ በ8ኛው ዓመት ክርስቲያኖችን ያሰቃይ የነበረው ሳውል (የሁዋላው ቅዱስ ዻውሎስ) ወደ ደማስቆ የተጉዋዘው ክርስቲያኖችን በተለይም ቅዱስ ሐናንያን ለማሠር ነበር::

ለእግዚአብሔር ምርጥ ዕቃ ይሆን ዘንድ መብረቅ ዐይኑን አጠፋው:: ወዲያውም ጌታችን ሳውልን ወደ ሐናንያ እንዲሔድ ነገረው:: ከ3 ቀናት በሁዋላ ጌታችን ለሐናንያ ተገልጦ አነጋግሮታል::

ሳውል (ዻውሎስ) ወደ ሐናንያ የደረሰው በመሪ ነበር:: 2ቱ እንደተገናኙ ቅዱስ ሐናንያ ሳውልን አስተማረው : ፈወሰው : አጠመቀው : በጐ መንገድንም መራው:: በዚህ ምክንያት ቅዱሱ ሐዋርያ የቅዱስ ዻውሎስ የንስሃ አባቱ ይሰኛል:: (ሐዋ. 9:1-19)

ከዚህ በሁዋላ ቅዱስ ሐናንያ ለብዙ ዓመታት በተለያዩ የዓለም ክፍሎች ወንጌልን አስተማረ:: መከራንም ተቀበለ:: በመጨረሻም በዚህ ቀን ክፉዎች ከብዙ ስቃይ በሁዋላ በድንጋይ ወግረው ገድለውታል::


" ቅዱስ ቶማስ ዘሰንደላት "

በ3ኛው መቶ ክ/ዘመን ከነበሩ ሰማዕታት አንዱ የሆነው ቅዱስ ቶማስ ወደ ሰማዕትነት ሕይወት የገባው በ11 ዓመቱ በመላእክት መሪነት ነው:: ገና ወደ ምስክርነት አደባባይ እንደ ቀረበ መኮንኑ "ክርስቶስን ካድና ልሹምህ" ቢለው ሕጻኑ ቅዱስ ቶማስ ተቆጥቶ : "አንተ ሰነፍ መኮንን" ብሎ ገስጾ : በጐችን ይመልስባት በነበረችው ጅራፍ ገርፎታል:: ይሔም በዘመኑ የመጨረሻው የድፍረት ደረጃ ነበር::

††† በዚህም ምክንያት በሕጻን ገላው ላይ የተቀበለው መከራ ሊናገሩት ይከብዳል::
¤ግርፋት:
¤እሳት:
¤አራዊት በእርሱ ላይ አልፈዋል::

አካሉ ተቆራርጧል:: አንድ ጊዜም "ለጣዖታችሁ እንድሰግድ አምጡት" ብሏቸው ልክ ከፊቱ ሲደርሱ ወደ ጌታ ቢጸልይ መሬት ተከፍታ ውጣቸዋለች::

እሱን ያሰቃየው የነበረውን መኮንንም ከደዌው አድኖ ከነ ሠራዊቱ አሳምኖታል:: ሕጻኑን ቅዱስ ቶማስን ግን ያላመኑ አረማውያን በዚህች ቀን አንገቱን ሰይፈውት በሰማዕትነት ወደ ወደደው ክርስቶስ ሔዷል::

††† አምላከ ቅዱሳን ከሐዋርያው በረከት : ከሰማዕቱም ምልጃ አይለየን:: አሜን!

" ቅዱስ_ያዕቆብ_ዘሥሩግ "

በቤተ_ክርስቲያን_ታሪክ በደራሲነታቸው: በወንጌል አገልግሎታቸውና በቅድስናቸው ከተመሠከረላቸው ዐበይት ሊቃውንት አንዱ ቅዱስ ያዕቆብ ዘሥሩግ ነው::

+ሊቁ የተወለደው መጋቢት 27 ቀን በ433 ዓ/ም ሲሆን ሃገሩ ሶርያ ነው:: ወላጆቹ ክርስቲያኖች ለዚያውም አባቱ ሊቀ ካህናት ነበር:: ቅዱስ ያዕቆብ ገና በልጅነቱ ጀምሮ ጸጋ እግዚአብሔር የጠራው ነውና በብዙ ነገሩ የተለየ ነበር::

+አንድ ቀን በዕለተ ሰንበት ገና በ3 ዓመቱ እናቱ አቅፋ ወደ #ቤተ_መቅደስ ወሰደችው:: ምዕመናን #ቅዱስ_ሥጋውንና #ክቡር_ደሙን ሲቀበሉ ሕጻኑ ያዕቆብም ይቆርብ ዘንድ ቀረበ:: ሊቀ ዻዻሱ ደሙን በዕርፈ መስቀል ሊያቀብለው ሲል መልአኩ መጥቶ "በጽዋው ጋተው" አለው:: የጌታን ደም በጽዋ ቢጠጣ ምስጢር ተገለጸለትና "#አንሰ_እፈርሕ_ሠለስተ_ግብራተ-እኔስ 3 ነገሮች ያስፈሩኛል" ሲል አሰምቶ ተናገረ::

+ዻዻሱና ሕዝቡ ወደ ሕጻኑ ያዕቆብ ቀርበው "ምን ምን?" አሉት:: እርሱም:-
1.ነፍሴ ከሥጋየ ስትለይ
2.ቅድመ እግዚአብሔር ለፍርድ ስቀርብ
3.ከፈጣሪየ የፍርድ ቃል ሲወጣ" አላቸው::
ያን ጊዜ ሕዝቡና ሊቀ ዻዻሳቱ "#እግዚአብሔር_በዚሕ_ሕጻን_አድሮ_ዘለፈን" እያሉ ለንስሃ በቅተዋል::

+ቅዱስ ያዕቆብ 7 ዓመት ሲሞላው ይማር ብለው ወደ ጉባዔ አስገቡት:: በ5 ዓመታት ብሉይ ከሐዲስ ጠንቅቆ በ12 ዓመቱ ሊቅ ሆኗል:: በዚህ ወቅት የነበሩ ታላላቅ ሊቃነ ዻዻሳት ወደ እርሱ ተሰበብስበው "እንግዳ ድርሰት ድረስልን: አዲስ ምሥጢር ንገረን" አሉት:: እርሱ ግን ሲቻለው ስለ ትሕትና "አልችልም" አላቸው::

+"እንግዲያውስ #ትንቢተ_ሕዝቅኤልን ተርጉምልን" ቢሉት ባጭር ታጥቆ አመሥጥሮላቸው ተደስተዋል:: ፈጣሪንም አመስግነዋል::

+ቅዱስ ያዕቆብ ከዚህ በሁዋላ ወደ ገዳም ገብቶ ትሕርምተ አበውን: ዕጸበ ገዳምን: ሕይወተ ቅዱሳንን በተግባር ተምሯል:: በድንግልናው ጸንቶ: #ጾምና_ጸሎትን እያዘወተረ ኑሯል:: በፈቃደ እግዚአብሔር የሥሩግ (በኤፍራጥስና ጤግሮስ ወንዞች መካከል የምትገኝ የሶርያ ግዛት ናት) ኤዺስ ቆዾስ ሆኖ ተሹሟል::

+በዘመኑም:-
1.የ451ን የኬልቄዶን ጉባኤ አውግዟል

2.ብዙ መናፍቃንን ተከራክሮ ምላሽ አሳጥቷል

3.በወንጌል አገልግሎት መልካም እረኝነቱን አሳይቷል

4.ዛሬ የምንገለገልበትን መጽሐፈ ቅዳሴውን ጨምሮ በርካታ መንፈሳዊ ድርሰቶችን ደርሷል::

+በመጨረሻም ከብዙ የተጋድሎና የቅድስና ዓመታት በሁዋላ በተወለደ በ72 ዓመቱ በ505 ዓ/ም በዚሕች ቀን አርፏል:: አንዳንድ ምንጮች ደግሞ ሰኔ 27 ቀን እንዳረፈ ይናገራሉ:: #ቅዱስ_ያዕቆብ_ዘሥሩግ ለቤተ ክርስቲያን የቁርጥ ቀን ተወዳጅ ልጇ ነውና በእጅጉ ታከብረዋለች::

=>#አምላከ_ቅዱሳን ከታላቁ ሊቅ በረከት ይክፈለን:: አሜን!


ሰኔ 27 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት

1.ቅዱስ ሐናንያ ሐዋርያ (ከ72ቱ አርድእት)
2.ቅዱስ ቶማስ ሰማዕት (ዘሰንደላት)
3.ቅዱስ አልዓዛር ነዳይ (በነዌ ደጅ የወደቀ : ቀጥሎ ደግሞ በአብርሃም እቅፍ ውስጥ የተገኘ ጻድቅ - ሉቃ. 16:19)
4.ቅዱስ ማማስ

ወርኀዊ በዓላት

1.የጌታችንና አምላካችን መድኃኔ ዓለም ክርስቶስ በዓለ ስቅለት
2.አቡነ መብዐ ፅዮን ጻድቅ
3.ቅዱስ መቃርስ (የመነኮሳት ሁሉ አለቃ)
4.ቅዱስ ያዕቆብ ዘግሙድ
5.ቅዱስ ገላውዴዎስ ሰማዕት (ንጉሠ ኢትዮዽያ)
6.ቅዱስ ቢፋሞን ጻድቅና ሰማዕት
7.ማር ቅዱስ ፊቅጦር ሰማዕት

ንባብ

"በደማስቆም ሐናንያ የሚሉት አንድ ደቀ መዝሙር ነበረ:: ጌታም በራዕይ:- "ሐናንያ ሆይ!" አለው:: እርሱም "ጌታ ሆይ! እነሆኝ" አለ:: ጌታም:- ተነስተህ ቅን ወደ ሚባለው መንገድ ሒድ:: በይሁዳ ቤትም ሳውል የሚሉትን አንድ የጠርሴስ ሰው ፈልግ:: እነሆ እርሱ ይጸልያልና:: ሐናንያ የሚሉትም ሰው ገብቶ ደግሞ እንዲያይ እጁን ሲጭንበት አይቷል" አለው::" (ሐዋ. 9:10-18)

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ዝክረ ቅዱሳን
30 views15:40
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-02 17:11:50 ††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ:: አሜን! †††

ወርኃ ሰኔ
ቀን ፳፮ (26)

እንኳን ለታላቁ ነቢይ ቅዱስ ኢያሱ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፣ አደረሰን።

" ቅዱስ ኢያሱ ነቢይ ወመስፍን "

ቅዱሱ የተወለደው በምድረ ግብፅ በባርነት ከነበሩ እሥራኤላውያን ሲሆን የቀደመ ስሙ "አውሴ" ይባላል:: ዘመኑ እግዚአብሔር ሕዝቡን ከ215 ዓመታት ባርነት ሊያወጣ የተቃረበበት ነውና ሊቀ ነቢያት ሙሴ ከምድያም ሲመለስ ከመረጣቸው ተከታዮቹ ዋነኛው ኢያሱ ነበር:: እሥራኤል ከባርነት ሲወጡ ሙሴ 80 ዓመቱ : ኢያሱ ደግሞ 40 ዓመቱ ነበር::

ሕዝቡ አንገተ ደንዳና ነበርና ለ40 ቀን የታሠበላቸውን መንገድ 40 ዓመት እንዲሆን አደረጉት:: በዚህ ጊዜ ኢያሱ ከመምሕሩ ከሙሴና ከሕዝቡ አልተለየም::

አውሴን "ኢያሱ" ብሎ ስም የቀየረለት ሙሴ ሲሆን ይሔውም በፈቃደ እግዚአብሔር ነው:: ኢያሱ ማለት "መድኃኒት" ማለት ነው::
ለዚሕም ምክንያቶች አሉት:- ለጊዜው አማሌቃውያንን ድል ነስቶ ሕዝቡን አድኗል:: ምድረ ርስትን አውርሷል::
ለፍጻሜው ግን ለጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ (ጥላ) እንዲሆን ነው::

ቅዱስ ኢያሱ በበርሃ ለ40 ዘመናት እግዚአብሔርን አምልኮታል:: ሊቀ ነቢያትን ታዝዞታል (አገልግሎታል):: እሥራኤልንም የጦር አለቃ ሆኖ ከአሕዛብ እጅ አድኗቸዋል::

በዚህም በእግዚአብሔርና በሕዝቡ ዘንድ ሞገስን አግኝቷል:: ቅዱስ ሙሴ ደብረ ናባው ላይ ባረፈ ጊዜ ሕዝቡን : ካሕናቱንና ታቦተ ጽዮንን ተረከበ:: ይህን ጊዜ ዕድሜው 80 እየሆነ ነበር::

††† እግዚአብሔርም ኢያሱን "ከአንተ ጋር ነኝ" ብሎ በሕዝቡ ላይ ነቢይና መስፍን (አስተዳዳሪ) እንዲሆን ሾመው:: ቅዱሱም ሰላዮችን ልኮ አስገምግሞ:
¤ባሕረ ዮርዳኖስን ከፍሎ
¤ሕዝቡን አሻግሮ
¤የኢያሪኮን ቅጥር 7 ጊዜ ዙሮ
¤በኃይለ እግዚአብሔር አፍርሶ
¤የኢያሪኮን ነገሥታት አጥፍቶ ለሕዝቡ ምድረ ርስትን አወረሰ::

የገባዖን ሰዎች "አድነን" ብለው በላኩበት ጊዜ ነገሥተ አሞሬዎንን ይወጋ ዘንድ ኢያሱ ወጣ:: እነዚያን ግሩማን ነገሥታት በፈጣሪው ኃይል : በጦርና በተአምራት ድል ነስቶ የእግዚአብሔር ስሙ ከፍ ከፍ አለ:: በዚያች ዕለትም ለ12ቱ ነገደ እሥራኤል ርስትን ሲያካፍል ፀሐይን በገባዖን: ጨረቃን ደግሞ በቆላተ ኤሎም (በኤሎም ሸለቆ) አቆመ::

ሰባት አሕጉራተ ምስካይ (የመማጸኛ ከተሞችን) ለየ:: ነቢይና መስፍን ሆኖ ሕዝቡን ለ40 ዓመታት አገለገለ:: በመጨረሻም ለሕዝቡ አላቸው:-
"እኔና ቤቴ እግዚአብሔርን እናመልካለን:: (ኢያ. 24) እናንተስ?" አላቸው:: እነርሱም "እኛም እንዳንተ ነን" አሉት:: ለዚህም ምልክት ይሆን ዘንድ 3 ገጽ ያላት ሐውልትን በመካከላቸው አቆመ::

ይህችውም የቅድስት ድንግል ማርያም ምሳሌ ናት:: ሐውልቷ 3 ገጽ እንዳላት እመቤታችንም በ3 ወገን (በነፍስ: በሥጋ: በልቡና) ድንግል ናት:: አንድም በ3 ወገን (ከኃልዮ: ከነቢብ: ከገቢር ኃጢአት) ንጽሕት ናት:: ለዚህም ነው አባ ሕርያቆስ
"ሐውልተ ስምዕ ዘኢያሱ" (የኢያሱ የምስክር ሐውልት አንቺ ነሽ) ሲል ያመሰገናት::

ታላቁ ነቢይ ኢያሱ ግን ከግብጽ በወጡ በ80 ዓመት: በተወለደ በ120 ዓመቱ (ጥሬው መጽሐፍ ቅዱስ በ110 ዓመቱ ይላል) በወገኖቹ መካከል ዐርፎ በያዕቆብ መቃብር ተቀበረ:: እሥራኤልም ለ30 ቀናት አለቀሱለት::

††† በወዳጁ በኢያሱ እጅ የአሕዛብን ቅጥር ያፈረሰ እግዚአብሔር የእኛንም የኃጢአታችንን ግንብ በወዳጆቹ ምልጃ ያፍርስልን:: ከቅዱሱ ነቢይም በረከትን ያሳትፈን:: አሜን!


ሰኔ 26 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት

1.ቅዱስ ኢያሱ ነቢይ ወመስፍን
2.ቅዱስ ገብርኤል ሊቀ መላእክት (ቅዳሴ ቤቱ)

ወርሐዊ በዓላት

1.ቅዱስ ቶማስ ሐዋርያ
2.አቡነ ሐብተ ማርያም ጻድቅ
3.አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ዘሐይቅ
4.ቅዱሳን ሰማዕታተ ናግራን
5.አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን

ንባብ

"አሁንም እግዚአብሔርን ፍሩ:: በእውነተኛም ልብ አምልኩት . . . እግዚአብሔርን ማምለክ ክፉ መስሎ ቢታያችሁ . . . የአሞራውያንን አማልክት ታመልኩ እንደ ሆነ: የምታመልኩትን ዛሬ ምረጡ:: እኔና ቤቴ ግን እግዚአብሔርን እናመልካለን::" (ኢያሱ. 24:14)

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ዝክረ ቅዱሳን
27 views14:11
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-07-01 21:00:59 ✞✞✞ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፡፡ አሜን! ✞✞✞

ወርኃ ሰኔ
ቀን ፳፭ (25)

እንኩዋን ከዘመነ ጸደይ ወደ ዘመነ ክረምት መሸጋገሪያ ለሆነችው ዕለትና ለቅዱሳኑ ዓመታዊ ክብረ በዓል በሰላም አደረሳችሁ::

=>ስንዱ እመቤት ቤተ ክርስቲያን (ሃገራችን) ሁሉ ነገሯ በሥርዓት ነውና ዓመቱን በዘመናት ከፍላ ትጠቀማለች:: እሊሕም ዘመናት መጸው (ጽጌ): ሐጋይ (በጋ): ጸደይ (በልግ)ና ክረምት ናቸው:: ዘመናቱ ወቅቶችን ከመለየትና ማሳወቅ ባሻገር የእኛ ሕይወትም ምሳሌዎች ናቸውና ልብ ልንላቸው ይገባል::

+በተለይ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለስም አጠራሩ ጌትነት ይሁንና "ሽሽታችሁ (ስደታችሁ) በክረምትና በሰንበት እንዳይሆን ጸልዩ" ብሎናልና (ማቴ. 24:20) ልንጸልይ ይገባናል:: በዘመነ ክረምት ቅጠል እንጂ ፍሬ የለበትምና ፍሬ ምግባር ሣናፈራ ሞት እንዳይመጣ: አንድም ክረምት የዝናብና የጭቃ ጊዜ በመሆኑ እንኩዋንስ ለስደት ለኑሮም አይመችምና እንደ ሊቃውንት እንዲህ ብለን እንጸልይ:-

"በዝንቱ ክረምት በመዋዕሊነ:
እንበለ ፍሬ እንዘ በቆጽል ኀሎነ:
ናስተበቁዐከ እግዚኦ ኢይኩን ጉያነ::"
(ክረምት በተባለ በእኛ እድሜ:
ፍሬ ሳናፈራ በቅጠል /ያለ መልካም ሥራ/ ሳለን:
አቤቱ ጌታ ሆይ ስደትን አታምጣብን)

=>ቸሩ አምላካችን ከዘመነ መጸው በሰላም ያድርሰን:: ተረፈ ዘመኑንም የንስሃ: የፍሬና የበረከት ያድርግልን:: አሜን!


በዚሕች ዕለት እነዚህ ቅዱሳን ይከበራሉ:-

" ቅዱስ ይሁዳ ሐዋርያ "

+በዘመነ ሐዋርያት ይሁዳ ተብለው ይጠሩ ከነበሩት አንዱ የሆነው ቅዱሱ የአረጋዊው ቅዱስ ዮሴፍ ልጅ ሲሆን እናቱ ማርያም ትባል ነበር:: እናቱ ስትሞትበት ተጎድቶ የነበረ ቢሆንም ገና በልጅነቱ ድንግል ማርያም አግኝታው በፍጹም ጸጋ አሳድጋዋለች:: አስተዳደጉም ከጌታችን ጋር በአንድ ቤት ነበር::
ጌታችን እርሱንና ወንድሞቹን (ያዕቆብና ስምዖንን) ከ72ቱ አርድእት ቆጥሯቸዋል:: ቅዱስ ይሁዳ ወንጌል ላይ ከጌታችን ጋር መነጋገሩን ዮሐንስ ወንጌላዊ መዝግቧል:: (ዮሐ. 14:22)

+ቅዱስ ይሁዳ ከጌታችን እግር 3 ዓመት ተምሮ: መንፈስ ቅዱስንም ተቀብሎ ብዙ አሕጉራትን ዙሯል:: አይሁድንም አረማውያንንም ወደ ክርስቶስ ይመልስ ዘንድ ብዙ ድካምና ስቃይን በአኮቴት ተቀብሏል:: አንዲት አጭር (ባለ አንድ ምዕራፍ) መልእክትም ጽፏል:: አጭር ትምሰል እንጂ ምሥጢሯ እጅግ የሠፋ ነው:: ቅዱስ ይሁዳን በዚህች ቀን አረማውያን ገድለውት በሐዋርያነቱ ላይ የሰማዕትነትን ካባ ደርቧል::


" ቅዱሳን ዺላጦስና አብሮቅላ "

=>ብዙዎቻችን መስፍኑን ዺላጦስ መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ጌታችን እንዳይሰቀል ከአይሁድ ጋር ሲከራከር እናውቀዋለን:: የጌታችን ሞቱ በፈቃዱ ነበርና አይሁድ እንቢ ሲሉት የክርስቶስን ንጽሕና መስክሮ: እጁንም ታጥቦ ሰጥቷቸዋል:: የዺላጦስ ታሪክ ግን እዚህ ላይ አያበቃም::

+ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን ድል አድርጐ ከተነሳ በሁዋላ ትንሳኤውን በራዕይ ገልጦለት አይሁድን ተከራክሯቸዋል:: ውሸታም ወታደሮችንም ቀጥቷል:: በመጨረሻ ግን በሮም ቄሳር ተጠርቶ ከእሥራኤል እስከ ሮም ድረስ ሰብኮ በሮም አደባባይ አንገቱ ተሠይፏል::

+ቅድስት እናታችን አብሮቅላም የዺላጦስ ሚስት ስትሆን ቁጥሯ ከ36ቱ ቅዱሳት አንስት ነው:: ጌታችንን ተከትላ: ቤቷን ለሐዋርያት አስረክባ: ቤተ ክርስቲያንንም በዘመኗ አገልግላ ዐርፏለች:: ዛሬ ሁለቱም ቅዱሳን ይታሠባሉ::

=>ጌታችን ከሐዋርያው ይሁዳ: ከዺላጦስና አብሮቅላም ጸጋ በረከትን ያድለን:: አሜን!


ሰኔ 25 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት

1.ቅዱስ ይሁዳ ሐዋርያ (ከ72ቱ አርድእት)
2.ሰማዕቱ ዺላጦስ መስፍን
3.ቅድስት አብሮቅላ (ሚስቱ)
4.አባ ዼጥሮስ ሊቀ ዻዻሳት
5.የጸደይ መውጫ / የክረምትመግቢያ

ወርሐዊ በዓላት

1.ቅዱስ መርቆሬዎስ ሰማዕት
2.ቅድስት ቴክላ ሐዋርያዊት
3.ቅዱስ አበከረዙን ሰማዕት
4.ቅዱስ ዱማድዮስ ሶርያዊ
5.አቡነ አቢብ /አባ ቡላ/
6.ቅዱስ አባ አቡፋና ጻድቅ

ንባብ

" የኢየሱስ ክርስቶስ ባሪያ: የያዕቆብም ወንድም የሆነ ይሁዳ በእግዚአብሔር አብ ተወደው: ለኢየሱስ ክርስቶስም ተጠብቀው ለተጠሩ: ምሕረትና ሰላም: ፍቅርም ይብዛላችሁ::
ወዳጆች ሆይ! ስለምንካፈለው ስለ መዳናችን ልጽፍላችሁ እጅግ ተግቼ ሳለሁ ለቅዱሳን አንድ ጊዜ ፈጽሞ ስለ ተሰጠ ሃይማኖት እንድትጋደሉ እየመከርኩዋችሁ እጽፍላችሁ ዘንድ ግድ ሆነብኝ:: " (ይሁዳ. 1:1)

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ዝክረ ቅዱሳን
25 views18:00
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-06-30 20:08:45 ✞✞✞ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፡፡ አሜን! ✞✞✞

❖ እንኳን አደረሳችሁ ❖

ወርኃ ሰኔ
ቀን ፳፬ (24)

በዚች ዕለት የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት

" ቅዱስ_ሙሴ_ጸሊም (ጥቁሩ ሙሴ) "

ግብጻውያን ስማቸውን ጠርተው ከማይጠግቧቸው
ቅዱሳን መካከል አንዱ ኢትዮዽያዊው አባ ሙሴ ጸሊም
ነው:: በእኛ ኢትዮዽያውያን ግን ይቅርና በወርኀዊ በዓሉ (በ24) በዓመታዊ በዓሉ እንኩዋ ሲከበር ብዙም አይታይም::

=>ቅዱሱ ሰው በትውልዱ ኢትዮዽያዊ
ሲሆን ያደገውም እዚሁ ሃገራችን ውስጥ እንደሆነ
ይታመናል:: ገና በወጣትነቱ አገር የሚያሸብር ሽፍታ ነበር::
ሙሴ ጸሊም
ወደ ግብጽ የሔደበት ምክንያት በግልጽ ባይታወቅም
መምለክያነ ጣዖት (ፀሐይን ከሚያመልኩ ሰዎች) ጋር
ይኖር ስለ ነበር:: ምናልባት እነርሱ ወስደውት ሊሆን ይችላል::

+ቅዱስ_ሙሴ በምድረ ግብጽም በኃይለኝነቱ ምክንያት የሚደፍረው
አልነበረም:: ፀሐይን ያመልካል: እንደ ፈለገ ቀምቶ
ይበላል: ያሻውን
ሰው ይደበድባል:: ነገር ግን በኅሊናው ስለ እውነተኛው
አምላክ ይመራመር ነበርና አንድ ቀን ፀሐይን "አምላክ
ከሆንሽ አናግሪኝ?" አላት:: እርሷ ፍጡር ናትና ዝም አለችው::

+ቅዱስ ሙሴ ምንም አስቸጋሪ ሰው ቢሆንም ፈጣሪን
መፈለጉን ግን ቀጥሏልና አንድ ቀን ተሳካለት:: መልካም
ክርስቲያኖችን
አግኝቶ . . . ወደ ገዳመ_አስቄጥስ ቢሔድ በዛ ያሉ መነኮሳት ወደ እውነት እንደሚመሩት ነገሩት:: እርሱም ሰይፉን እንደታጠቀ ወደ ገዳም ገባ::

መነኮሳቱ ፈርተውት ሲሸሹ ታላቁ አባ_ኤስድሮስ ግን ተቀብለው አሳረፉት::

+"ምን ፈለግህ ልጄ?" አሉት:: "እውነተኛውን አምላክ ፊት
ለፊት ማየት እፈልጋለሁ" የሙሴ ጸሊም መልስ ነበር:: አባ
ኤስድሮስም "የማዝህን ሁሉ ካደረግህ ታየዋለህ" ብለው
ወደ መነኮሳት አለቃ ቅዱስ_መቃርስ_ታላቁ ወሰዱት:: መቃሬም ክርስትናን አስተምረው አጠመቁትና
ለአባ ኤስድሮስ መለሱላቸው::

+ከዚህ ሰዓት በሁዋላ ነበር የአባ ሙሴ ጸሊም ሕይወት
ፍጹም የተለወጠው:: በጻድቁ እጅ ምንኩስናን ተቀብሎ
ይጋደል ጀመር:: በጠባቧ በር ይገባ ዘንድ ወዷልና ያ በሽፍትነት የሞላ አካሉን በገድል አረገፈው:: ከቁመቱ በቀር ከአካሉ አልተረፈለትም:: ወገቡን በአጭር ታጥቆ መነኮሳትን አገለገለ:: አጋንንት በቀደመ ሕይወቱ በሕልም: አንዳንዴም በአካል እየመጡ ይፈትኑት ነበር::

+እንዳልቻሉት ሲረዱ ተሰብስበው መጥተው በእሳት
አለንጋ ገርፈው አቆሳስለውት ሔዱ:: እርሱ ግን ታገሰ::
በበርሃ ለሚኖሩ
አበው መነኮሳት ሁሉ ብርሃን በሆነ ሕይወቱ ሞገስ ሆነላቸው:: ለኃጥአን ደግሞ መጽናኛ
ሆነ::

<< በተራራ ላይ ያለች ሃገር ልትሠወር አይቻላትምና ስም
አጠራሩ በመላው ዓለም ተሰማ:: ሁሉም "ሙሴ_ጸሊም ይል ጀመር ፡፡ >>

+በየበርሃው ያሉ አበው ብቻ ሳይሆነ ዓለማውያን
መኩዋንንት ሳይቀሩ ሊያዩት ይመኙ ነበር:: እርሱ ግን
ራሱን "አንተ
ጥቁር ባሪያ ስለ ኃጢአትህ አልቅስ" እያለ ይገስጽ:
ከውዳሴ ከንቱም ይርቅ ነበር:: ከቆይታ በኋላም
በመነኮሳት ላይ
እረኛ (አበ ምኔት) ሆኖ ተሾመ:: እንደሚገባም አገለገለ::
የበርካቶችን ሕይወት ጨው በሆነ ሕይወቱና ምክሩ
አጣፍጦ:
ድርሳናትንም ደርሶ እያረጀ ሔደ::

+ከቁመቱ መርዘም የጽሕሙ ነጭነትና አወራረዱን ያዩ
ሁሉ ሲያዩት ያደንቁት ነበር:: በመጨረሻም በ375 ዓ/ም
በርበረሮች
(አሕዛብ) ገዳመ አስቄጥስን ሲያጠፉ ሌሎች መነኮሳት
ሸሹ:: እርሱ ግን አልሸሽም ብሎ ከ7 ደቀ መዛሙርቱ ጋር
በዚሕች ቀን ተሰይፎ በሰማዕትነት አልፏል::

=>ቅዱስ ሙሴ ጸሊምን ለርስቱ ያበቃ ጌታ ለእኛም ዕድሜ
ለንስሃ: ለዘመን ለፍስሃን አይንሳን:: ከበረከቱም ፈጣሪው
ያድለን:: አሜን!


ሰኔ 24 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት

1.ቅዱስ አባ ሙሴ ጸሊም (ኢትዮዽያዊ)
2."7ቱ" ቅዱሳን መነኮሳት (ደቀ መዛሙርቱ)
3.አባ ኤስድሮስ ታላቁ

ወርኃዊ በዓላት

1፡ ቅዱስ ተክለ ሃይማኖት
2፡ ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ
3፡ ቅዱስ ቶማስ ዘመርዓስ
4፡ ቅዱስ አጋቢጦስ
5፡ ቅዱስ አብላርዮስ
6፡ አቡነ ዘዮሐንስ ዘክብራን
7፡ ፳፬ቱ ካህናተ ሰማይ

ንባብ

" መቶ በግ ያለው ከእነርሱም አንዱ ቢጠፋ ዘጠና
ዘጠኙን በበርሃ ትቶ የጠፋውን እስኪያገኘው ድረስ
ሊፈልገው የማይሔድ ከእናንተ ማን ነው? ባገኘውም ጊዜ ደስ ብሎት በጫንቃው ይሸከመዋል:: ወደ ቤትም በመጣ ጊዜ ወዳጆቹንና ጐረቤቶቹን በአንድነት ጠርቶ "የጠፋውን በጌን አግኝቼዋለሁና ከእኔ ጋር ደስ ይበላችሁ" ይላቸዋል::
እላችሁአለሁ: እንዲሁ ንስሃ ከማያስፈልጋቸው ከዘጠና ዘጠኝ ጻድቃን ይልቅ ንስሃ በሚገባ በአንድ ኃጢአተኛ በሰማይ ደስታ ይሆናል:: " (ሉቃ. 15:3-7)

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ተወሰደ:- ዝክረ ቅዱሳን
28 views17:08
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-06-29 21:58:01 ✞✞✞ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፡፡ አሜን! ✞✞✞

ወርኃ የሰኔ
ቀን ፳፫ (23)

❖ እንኳን አደረሳችሁ ❖

በዚች ዕለት የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት

" ቅዱስ_ሰሎሞን ንጉሠ እሥራኤል "

=>መፍቀሬ ጥበብ:
¤ጠቢበ ጠቢባን:
¤ንጉሠ እሥራኤል:
¤ነቢየ ጽድቅ:
¤መስተሣልም (ሰላማዊ) . . . እየተባለ የሚጠራው
ቅዱስ ሰሎሞን የታላቁ ነቢይና ንጉሥ ልበ
አምላክ ቅዱስ_ዳዊትና የቅድስት ቤርሳቤህ (ቤትስባ) ልጅ ነው:: ከ3ሺ ዓመታት በፊት የተወለደው ቅዱስ
ሰሎሞን እስከ 12 ዓመቱ ድረስ በቤተ መንግሥት ከአባቱ
ጋር አድጉዋል::

+ቅዱስ ዳዊት 70 ዘመን በሞላው ጊዜ የአካሉን
መድከም አይቶ አዶንያስ በጉልበት እነግሣለሁ ቢልም
አልተሳካለትም::
እግዚአብሔር ሰሎሞንን መርጧልና ገና በ12 ዓመቱ
ነገሠ:: ልበ_አምላክ አባቱ ዳዊት ነፍሱ ከሥጋው ከመለየቷ በፊት መከረው::
"ልጄ ሆይ! ልብህን ስጠኝ:: ፈጣሪህንም አምልክ"
አለው::

+ቅዱስ ሰሎሞን እንደ ነገሠ በገባዖን ለእግዚአብሔር
መስዋዕትን አቀረበ:: ጌታም ተገልጾ "ምን ትፈልጋለህ?"
አለው::
ሰሎሞንም ልክ እንደ አባቱ ማስተዋልን: ልቡናን ለመነ::
በዚህም ጌታ ደስ ስለተሰኘ "አልቦ እምቅድሜከ: ወአልቦ
እምድኅሬከ - ከአንተም በፊት: ከአንተም በኋላ እንዳንተ
ያለ ጠቢብና ባለጠጋ ሰው የለም: አይኖርም" ብሎት
ተሠወረ::
ቅዱስ ሰሎሞን ለ40 ዓመታት በእሥራኤል ላይ ነገሠ::

+ግሩም በሆነ ፍትሑ: በልዩ ጥበቡ ዓለም ተገዛለት::
እግዚአብሔር የመረጣት የእኛዋ ንግስተ_ሳባ /አዜብ/ማክዳም ትፈትነው ዘንድ ሒዳ ምኒልክን (እብነ_መለክን) ጸነሰች:: በኋላም ታቦተ_ጽዮንና ሥርዓተ ኦሪት መጣልን:: ነቢየ ጽድቅ ቅዱስ ሰሎሞን ድንግል_ማርያም ከእነሱ ዘር እንደምትወለድ ነግሮት ነበርና ያበጀሁ መስሎት
ሴቶችን አብዝቶ ነበር::

+ነገር ግን:-
¤አንደኛ ሰው (ሥጋ ለባሽ) ነውና:
¤ሁለተኛ ደግሞ ከብዙ ሴቶች መካከል
ከአንዷ እመ_ብርሃን ትገኛለች መስሎት ነበር:: ነገሩ መንገድ ስቶበት ከአሕዛብ
(ከፈርዖን ልጅ) ጋር በመወዳጀቱ ለጣዖት አሰገደችው::
እግዚአብሔር እጅግ አዘነ::

+በራዕይ ተገልጦ "ስለ ወዳጄ ስለ ዳዊት ስል በአንተ ላይ ክፉን አላደርግም" አለው:: ታላቁ ነቢይ
ሰሎሞን ይህንን ሲሰማ ወደ ልቡ ተመለሰ:: ማቅ ለብሶ:
አመድ
ነስንሶ በፍጹም ልቡ አለቀሰ:: ንስሃ ገባ:: መፍቀሬ ንስሃ
ጌታችንም ንስሃውን ተቀበለው::

+የይቅርታው መገለጫም ተወዳዳሪ የሌላቸውን 5
መጻሕፍት ገለጠለት:: ተናገራቸው:: ጻፋቸው:: እሊሕም:-
1.መጽሐፈ ጥበብ
2.መጽሐፈ ተግሣጽ
3.መጽሐፈ መክብብ
4.መጽሐፈ ምሳሌ
5.መኃልየ መኃልይ ዘሰሎሞን ናቸው::

+ቅዱስ ሰሎሞን ልዩ የሆነውን ቤተ_መቅደስ በመስራቱም ይደነቃል:: ደጉ ንጉሥ: ጠቢብና ነቢይ ሰሎሞን በዚህች ዕለት በ52 ዓመቱ ዐርፎ ወደ ፈጣሪው ሔዷል::


" አባ_ኖብ "

ዳግመኛ በዚህ ቀን ታላቁ ሰማዕት አባ ኖብ አርፏል::
በዚሕ ስም የሚጠሩ ብዙ ቅዱሳን ቢኖሩም ዋናው ይኼው
ቅዱስ ነው::

+አባ ኖብ እንደ ገዳማውያን በበርሃ የተጋደለ: እንደ
ሊቃውንት መጻሕፍትን ያመሰጠረ: በተለይ ደግሞ በዘመነ
ሰማዕታት ጭንቅ ጭንቅ መከራዎችን የተቀበለ አባት ነው:: ስለ ገድሉ ብዛት "ኃያል ሰማዕት": አንገቱን ስላልተቆረጠም "ሰማዕት ዘእንበለ ደም" ይባላል:: ዘመነ ሰማዕታትን ካለፉ 72ቱ ከዋክብትም አንዱ ነው::

=>ከመፍቀሬ ጥበብ ቅዱስ ሰሎሞን: ከኃያሉ ሰማዕት አባ
ኖብ በረከትን አምላካችን ይክፈለን:: አሜን!


ሰኔ 23 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት

1.ነቢየ ጽድቅ ቅዱስ ሰሎሞን (ንጉሠ እሥራኤል)
2.ቅዱስ አባ ኖብ (ሰማዕት ወጻድቅ)
3.ቅዱሳን መርቆሬዎስ: ፊልዾስና ቶማስ (ሰማዕታት)

ወርኃዊ በዓላት

1፡ ቅዱስ ዳዊት ልበ አምላክ
2፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ ሊቀ ሰማዕታት
3፡ ቅዱስ ጢሞቴዎስ ገዳማዊ
4፡ አባ ሳሙኤል
5፡ አባ ስምዖን
6፡ አባ ገብርኤል
7፡ ቅዱስ ዳንኤል ነቢይ

ንባብ

" የጭንቀት ቀን ሳይመጣ በጉብዝናህ ወራት
ፈጣሪህን አስብ:: ደስ አያሰኙም የምትላቸውም ዓመታት
ሳይደርሱ: ፀሐይ: ጨረቃና ከዋክብትም ሳይጨልሙ . . . አፈርም ወደ ነበረበት ምድር ሳይመለስ: ነፍስም ወደ ሰጠው ወደ እግዚአብሔር ሳይመለስ ፈጣሪህን አስብ::
ሰባኪው:- "ከንቱ: ከንቱ: ሁሉ ከንቱ ነው" ይላል:: "
(መክ. 12:1-9)

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ተወሰደ:- ዝክረ ቅዱሳን
30 views18:58
ክፈት / አስተያየት ይስጡ
2022-06-28 21:03:10 በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ:: አሜን!

ወርኃ ሰኔ
ቀን ፳፪ (22)

እንኳን ለቅዱሱ አባታችን የዋህ ዻውሊ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ ፣ አደረሰን።

" ቅዱስ ዻውሎስ የዋህ "

በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን መጀመሪያ አካባቢ ግብፅ ውስጥ ተወልዶ ያደገው ቅዱሱ ስሙ ዻውሎስ ቢሆንም ብዙ ጊዜ የሚጠራው "የዋህ ዻውሊ" በሚል ነው:: ይሕስ እንደ ምን ነው ቢሉ:-

የዋህ ዻውሊ ከሕጻንነቱ ጀምሮ መጻሕፍትን የተማረ: ግን ደግሞ ትዕቢት: ቁጣና ቂምን የማያውቅ ገራገር ሰው ነው:: እድሜው ለአካለ መጠን ሲደርስ ቤተሰቦቹ ሚስት አግባ አሉት:: እርሱ ባያስብበትም ወገኖቹን ላለማሳዘን አገባ:: እንዳለመታደል ሆኖ ግን ያገባት ሴት በጣም ቆንጆ በዚያም ላይ ክፉ ነበረች:: የዋህ ዻውሊ ክፋቷን ሁሉ ታግሶ ለበርካታ ዓመታት አብሮ ኖረ:: ልጆችንም አፈሩ::

አሁንም ግን እርሷ ከክፋቷ ልትታገስ አልቻለችም:: ይባስ ብሎ ዻውሊ በሌለበት ከሌሎች ወንዶች ጋር ትዘሙት ያዘች:: የዋሁ ሰው ይሕንኑ ያውቃል ግን የእግዚአብሔርን ሥራ ዝም ብሎ በተስፋ ይጠብቅ ነበር:: ለነገሩስ እሱ ያርሳል: ይቆፍራል: ነዳያንን ያበላል: እንግዳ ይቀበላል እንጂ ክፋትን ለማሰብ ጊዜ አልነበረውም::

አንድ ቀን ግን ለሥራ ወደ በርሃ ወጥቶ አንድ ግሩም ዜና ሰማ:: "አባ እንጦንስ ምንኩስና የሚባል ሕይወተ መላእክትን ጀምሯል: ደቀ መዛሙርትንም ይቀበላል" አሉት:: ግን ሚስትና ልጆች አሉትና ምን ያደርጋል?

የዋህ ዻውሊ ሙሉ ቀን ሢሠራ ውሎ ወደ ቤቱ ሲመለስ ግን የጠበቀው ሌላ ነው:: ሚስቱ በራሱ መኝታ ላይ ከአገልጋይ እረኛው ጋር ራቁታቸውን አገኛቸው:: ልብ በሉልኝ በትክሻው ሞፈርና ምሳር: መጥረቢያም ይዟል:: እርሱ ግን ክፉን አላሰበም:: ጥሩ ልብስ አንስቶ ሁለቱንም አለበሳቸው::
እንዲሕም አላቸው:- "ከዚሕ በሁዋላ እኔ አልመለስም:: ሀብት ንብረቴን ውረሱ: በደስታም ኑሩ:: የልጆቼን ነገር ግን አደራ" ብሏቸው ተነሳ::

በእጁ ምንም አልያዘም:: በትከሻው ያለችውን ብጣሽ ጨርቅ ይዞ ወደ በርሀ ተጉዋዘ:: አባ እንጦንስም ተቀብለው አስተምረው አመነኮሱት:: ከዚያች ቀን ጀምሮ ራስን ዝቅ በማድረግ: በመታዘዝ አገለገለ:: ጾም: ጸሎትና ስግደቱንማ ማን ቆጥሮት::

እያለ እያለ ከብቅዐት ማዕርግ ደረሰ:: ምዕመናንም ሆነ መነኮሳት ሊጠይቁት ሲመጡ የእያንዳንዱ ኃጢአት በግንባራቸው ተጽፎ ይመለከት ነበርና ስለነሱ ሲያለቅስ ቅንድቡ ተላጠ:: ሰውነቱም አለቀ:: አንድ ቀን ጋኔን የያዘውን ሰው ፈውስ ብለው አመጡለት:: እርሱ ግን በአጋንንት ላይ ሥልጣን እያለው በትሕትና ተጠግቶ ጋኔኑን "አባ እንጦንስን ከምጠራብህ ቀስ ብለህ ውጣ" አለው:: ጋኔኑ ግን የፈራው መስሎት በትዕቢት "እንጦንስ ማነው?"አለው::

ያን ጊዜ የዋህ ዻውሊ እንደ እሳት ከጋለ ድንጋይ ላይ ቁሞ "ሕያው እግዚአብሔር ምስክሬ ነው:: ይሕ ጋኔን ካልወጣ አልወርድም" አለ:: ወዲያው በዘንዶ አምሳል ከሴትዮዋ ወጥቶ እየጮኸ ወደ ቀይ ባሕር ገባ::ቅዱስ ዻውሊ የዋሕም እንዲሕ በቅድስና ተመላልሶ በዚሕች ቀን በመልካም ሽምግልና ዐርፏል::

" የመንፈስ ፍሬ ግን ፍቅር: ደስታ: ሰላም: ትእግስት: ቸርነት: በጐነት: እምነት: የውሃት: ራስን መግዛት ነው:: እንደዚህ ያሉትን የሚከለክል ሕግ የለም:: የክርስቶስ ኢየሱስም የሆኑቱ ሥጋን ከክፉ መሻቱና ከምኞቱ ጋር ሰቀሉ::" (ገላ. 5:22)


ሰኔ 22 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት

1.ቅዱስ አባ ዻውሊ የዋሕ
2.ቅዱሳን ወክቡራን ቆዝሞስና ድምያኖስ (ሰማዕታት)
3.ቅድስት ቴዎዳዳ ሰማዕት (እናታቸው)
4.አንቲቆስ: ዮንዲኖስና አብራንዮስ (ሰማዕታት)

ወርኀዊ በዓላት

1.ቅዱስ ዑራኤል ሊቀ መላእክት
2.ቅዱስ ሉቃስ ወንጌላዊ
3.ቅዱስ ደቅስዮስ (የእመቤታችን ወዳጅ)
4.አባ እንጦንዮስ (አበ መነኮሳት)
††† አምላካችን ከቅዱስ ዻውሊ የውሃነትን: ትእግስትን: በጐነትን: ጸጋ በረከትን ይክፈለን:: አሜን!!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ተወሰደ:- ዝክረ ቅዱሳን
29 views18:03
ክፈት / አስተያየት ይስጡ