2024-05-07 13:59:51
የመንግስት ሰራተኞች እንዳይደራጁ መከልከሉ ከደመወዝና ግብር ጋር የተያያዙ እንግልቶች እየገጠሟቸው ነው ተባለ
ኢሰማኮ ከአቅሜ በላይ ነው ብሏል
ማክሰኞ ሚያዝያ 29 ቀን 2016 (አዲስ ማለዳ) ኢትዮጵያ የመንግስት ሰራተኞች እንዳይደራጁ በአዋጅ መከልከሏ ሰራተኞችን ለከፍተኛ ችግር እየዳረገ መሆኑ ተገለጸ።
የኢትዮጵያ ሰራተኛ ማህበራት ኮንፌዴሬሽን እንዳስታወቀው የመንግስት ሰራተኞች እንዳይደራጁ የሚከለክለው የኢትዮጵያ የአሰሪና ሰራተኛ ሕግ እንዲሻሻል በተደጋጋሚ ለመንግስት ጥሪ ቢያቀርብም ምላሽ ባለማግኘቱ ጉዳዩ ከተቋሙ አቅም በላይ ሆኗል።
ይህ ክልከላ የመንግስት ሰራተኞች ለወራት ደመወዝ ባለማግኘት እና ከከፍተኛ ግብር እንዲሁም መሰል ችግሮች እየተንገላቱ ተደራጅተው መብታቸውን እንዳያስከብሩ አድርጓል መባሉን አዲስ ማለዳ ከኮንፌዴሬሽኑ ያገኘችው መረጃ ያመለክታል።
የኢትዮጵያ መንግስት ይህን ሕጉን እንዲያሻሽል በአሁኑ ሰዓት በዓለም ስራ ድርጅት በኩል ጥሪ እየቀረበ እንደሆነ አዲስ ማለዳ ሰምታለች። ኮንፌዴሬሽኑም ይህ ሕግ እስከሚሻሻል ድረስ ጥያቄያችንን እናቀርባለን ሲል አስታውቋል።
አዲስ ማለዳ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ እና በደቡብ ኢትዮጵያ ክልሎች አንዳንድ ዞኖች ላይ የመንግስት ሰራተኞች በደመወዝ መቆራረጥ እና ሙሉ ለሙሉ መቋረጥ መቸገራቸውን መዘገቧ አይዘነጋም። በዚህ ሳቢይ የተዘጉ ትምህትርት ቤት መኖራቸውም ተሰምቷል።
ኢትዮጵያ የአገሪቱ እንደ አውሮፓዉያን አቆጣጠር በ1963 የፈረመችው የዓለም ስራ ድርጅት ስምምነት የመንግስት ሰራተኞች መደራጀትን ቢደነግግም የኢትዮጵያ አሰሪ እና ሰራተኛ ሕግ ይህንን ይከለክላል።
አዲስ ማለዳ ከኮንፌዴሬሽኑ ባገኘችው መረጃ የአገሪቱ ሕግ አካል ሆኖ ተፈጻሚ መሆን የሚገባው ጉዳይ ከመሆኑ ባለፈ ሰራተኞችን ለችግር እያጋለጠ ነው።
———
ፈጣንና ወቅታዊ መረጃ ለማግኘት እንዲሁም ሃሳብ፣ አስተያየት እና የሚዲያ ሽፋን ጥቆማ ለማድረስ
የአዲስ ማለዳ ትክክለኛ የማህበራዊ ሚዲያ ገጾችን ይቀላቀሉ፤ ለሌሎችም ያጋሩ!
Telegram | Facebook | YouTube | X | www.addismaleda.com | 0961414141
7.5K views10:59