Get Mystery Box with random crypto!

“ቤተሰቦቻችን አልቀው እኛ አለን” “እኔስ አንድ ወንድምና የወንድም እህት አጣሁ። ሙሉ ቤተሰቡን | (ABC) Amhara Broadcasting Corporation

“ቤተሰቦቻችን አልቀው እኛ አለን”

“እኔስ አንድ ወንድምና የወንድም እህት አጣሁ። ሙሉ ቤተሰቡን ያጣ ዘመዴ አለ። 21 ቤተሰብ የሞተበትም ሰው አለ እኮ። ልጆቹን፣ የልጅ ልጆቹን ያጣም አለ” ብሏል ከማል።

እሱ የሚኖርበት አካባቢ አቅራቢያ ባሉ ሦስት ጎጦች “250 ሰው እንደተቀበረ” እና ገና አስክሬናቸው ተፈልጎ የሚቀበሩ ሰዎች ስላሉ፣ የሟቾችን አጠቃላይ ቁጥር አሁን ላይ ለመናገር እንደሚከብድ ገልጿል።

“ቤተሰቦቻችን አልቀው እኛ አለን፣ ግማሹ ትላንት ተቀበረ። ግማሹ ዛሬ ይሰበሰባል። ትላንት ‘ይህን ሁሉ ሰው መቅበር አንችልም’ ብለው የተመለሱ አሉ” ሲል ከማል አክሏል።

ዛሬ ተጨማሪ የሰው ኃይል ለቀብር እንደሄደ ጠቅሶ “ምን ያህል ሰው እንደሞተ በዚህ መረዳት ይቻላል” ብሏል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ጥቃቱን በተመለከተ በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ላይ ዝርዝር ነገር ባያሰፍሩም፣ በተለያዩ ክልሎች ውስጥ የሚፈጸሙ እንዲህ ያሉ ጥቃቶችን መንግሥታቸው እንደማይታገስ ገልጸዋል።

መንግሥት ሸኔ ብሎ የሚጠራው እና እራሱን የኦሮሞ ነፃነት ሠራዊት የሚለው ቡድን ታጣቂዎች በርካታ ሰላማዊ ሰዎች መግደላቸውን የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) እና የኦሮሚያ ክልል አመልክተዋል።

ከማል ጥቃቱ በሚፈጸምበት ወቅት ወደ እርሻ ሄዶ እንደነበርና ጥቃቱ መፈጸሙን እንደሰሙ ወደ መንደራቸው ሲመለሱ ሴቶችና ሕጻናት በብዛት ተገድለው እንደደረሱ ተናግሯል።

“ወረዳውን ‘ኧረ እባካችሁ እርዱን፣ ኧረ የመንግሥት ያለህ’ ብለን ስንደውልለት የሚረዳን ጠፋ። ኋላ ላይ በ11 ሰዓት ለይምሰል የሚረዳን መጣ። የተጠቃው አማራ ብቻ ነው። ብሔር ለይተው ‘እዚህ ምን ተደርጋላችሁ? በቃ ውጡ!’ ነው ያሉን። እዚህ ካደራችሁ መልሰን መጥተን እንጨፈጭፋችኋላን ብለውናል። የሦስት ቀን ሕጻን ሳይቀር ተጨፍጭፎብናል።”

ጥቃቱ እሱ የሚኖርበት መንደር ጋር ሲጀመር፣ ቤቶች ሲቃጠሉ ከሩቁ ተመልክቶ ወደ ቤቱ አቅራቢያ እንደሄደም እንዲህ ተናግሯል።

“እየገሰገስን ስንመጣ መንደሩ ተከቧል። እኛንም በጥይት አባረሩን። ቤት ውስጥ የነበሩ ሴቶችና ሕጻናት አለቁ። አርሶ አደሩን እያባረሩ በጥይት ገደሉ። ሸንኮራ ማሳ ውስጥ ተደብቀው ሲያለቅሱ የነበሩ ሕጻናት ሳይቀሩ ተገድለዋል።”

የነዋሪዎች ንብረት እንደተዘረፈና ከእንግዲህ በኋላም ለደኅንነታቸው እንደሚሰጉም ከማል ተናግሯል።

“የቁም ከብት ቀርቶ ዶሮ የቀረው የለም። ተዘርፏል። የሞተው ሞቷል ለእኛ ለቀረው መፍትሄ እንዲሰጠን ነው የምንፈልገው። መንግሥት ካለ፣ ሕግ ካለ ከዚህ ያስወጣንና ወደ አገራችን ይመልሰን። እስካሁን ያዘነልን፣ ስህተት ነው ያለንም የመንግሥት አካል የለም” ብሏል።

ምዕራብ ኦሮሚያን ጨምሮ በተለያዩ አካባቢዎች ውስጥ እንደሚንቀሳቀስ የሚነገርለት ታጣቂ ቡድኑ ቶሌ ቀበሌ ውስጥ በሚገኙ መንደሮች “ሲቪል ሰዎች ላይ በተፈጸመ ጥቃት በሰው ሕይወት፣ በአካል እና በንብረት ላይ ከፍተኛ ጉዳት” ደርሷል ሲል ኢሰመኮ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል።

የኦሮሚያ ክልል መንግሥትም በምዕራብ ወለጋ ዞን፣ ጊምቢ ወረዳ፣ ቶሌ ቀበሌ ውስጥ በአሸባሪነት የተፈረጀው ታጣቂ ቡድኑ ጥቃት መፈጸሙን አረጋግጦ፣ በዚህም ጥቃት በንጹሃን ሰዎች እና በንብረት ላይ ጉዳት መድረሱን ባወጣው መግለጫ ላይ አመልክቷል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ፣ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ "በንጹሃን ዜጎች ላይ በሕገ ወጥ እና በኢ-መደበኛ ኃይሎች የሚደርስ ጥቃት እና መተዳደሪያን ማውደም ተቀባይነት የለውም” በማለት፣ “በቤኒንሻንጉል እና በኦሮሚያ ክልሎች፣ ዋና ዓላማቸው ኅብረተሰቡን ማሸበር በሆነ አካላት የተፈጸመው የሰው ልጆችን ሕይወት የሚቀጥፍ ዘግናኝ ድርጊት የምንታገሰው አይደለም” ብለዋል።

በጊምቢ ለሰዓታት ከተፈጸመው ጥቃት የተረፉ የዐይን እማኞች ምስክርነት

መረጃው የbbc ነው
https://t.me/JournalistNetsanetGetachew