2022-01-18 11:33:07
[እንኳን ለብርሃነ ጥምቀቱ በሰላም አደረሳችሁ]
ከመጋቤ ሐዲስ ዶክተር ሮዳስ ታደሰ
ጥምቀት ማለት ቃሉ የግእዝ ቃል ሲሆን ትርጉሙም “መነከር፣ መዘፈቅ፣ ውሃ ውስጥ ገብቶ መውጣት” ማለት ነው፡፡
ምስጢረ ጥምቀትን የመሰረተልን ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሲሆን ሲመሠርትም በማዘዝ ብቻ ሳይሆን በሥራ በማሳየት ጭምር ነው (ማቴ 3፡17፤ ማር 1፡9፤ ሉቃ 3፡21፤ ዮሐ 1፡31)፡፡
ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ እከብር አይል ክቡር የባሕርይ አምላክ ሆኖ ሳለ በዮርዳኖስ ወንዝ በአገልጋዩ (በፍጡሩ) በዮሐንስ የተጠመቀበት ምክንያት፦
1) አንድነቱን ሦስትነቱን ለመግለጽ
2) የዕዳ ደብዳቤያችንን ለመደምሰስ (ቆላ 2:14)
3) በእርሱ ጥምቀት የእኛን ጥምቀት ለመቀደስ
4)ለጥምቀታችን ኀይልን ለመስጠት
5) ለአብነት ርሱ ተጠምቆ እናንተም ተጠመቁ ብሎ አርአያና ምሳሌ ለመሆን ከቅድስት ድንግል ማርያም በተወለደ በ30 ዘመኑ ጥር 11 ከሌሊቱ በ10ኛው ሰዓት፤ ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ መጣ፡፡
ጌታችን በዮርዳኖስ እንደሚጠመቅና የዮርዳኖስ ወንዝ ጌታን ስታይ እንደምትሸሽ ነቢዩ ዳዊት በመዝ 113፡3-5፦ “ባሕር አየች ሸሸችም፥ ዮርዳኖስም ወደ ኋላው ተመለሰ፤ ተራሮች እንደ ኮርማዎች፥ ኮረብቶችም እንደ ጠቦቶች ዘለሉ፤ አንቺ ባሕር የሸሸሽ፥ አንቺም ዮርዳኖስ ወደ ኋላሽ የተመለስሽ ምን ሆናችኋል?” በማለት ከ1000 ዓመት አስቀድሞ ትንቢት የተናገረ ሲሆን፤ ብዙ ምሳሌም አለውና ከትርጓሜ ወንጌል ይመልከቱ፨
ዮሐንስ ወደ ጌታችን መምጣት ሲገባው ጌታችን ወደ ዮሐንስ የሄደበት ምክንያት የመጀመሪያው ትሕትናን ለማስተማር ነው።
ሁለተኛው ለአብነት ለምሳሌ ነው፤ ይኸውም ዮሐንስ ሄዶ አጥምቆት ቢሆን ዛሬ ባለሥልጣናቱ ካህናትን ቤታችን ድረስ መጥታችሁ አጥምቁን ይሏቸው ነበርና ሰማያዊ ንጉሥ እኔ ከሄድኩ እናንተም ሄዳችሁ ቤተ ክርስቲያን ተጠመቁ ለማለት ሄዷል።
ዮሐንስ ግን ወደርሱ በትሕትና የመጣው አምላኩ ክርስቶስ መሆኑን ተረድቶ “እኔ በአንተ ልጠመቅ ያስፈልገኛል አንተም ወደ እኔ ትመጣለህን?” ሲል ጌታችንም “ጽድቅን ልንፈጽም” ይገባናል ብሎ ትንቢተ ነቢያትን ሊፈጽም እንደመጣ ሲነግረው ዮሐንስ እሺ አለ።
ከዚያም ተያይዘው ወደ ዮርዳኖስ ሲወርዱ የቤተ ክርስቲያን መጻሕፍት እንደሚያስተምሩት የዮርዳኖስ ወንዝ ወደ ኋላዋ ሸሽታለች በዚህም ዳዊት በመዝ 77፡16 ላይ፦
“አቤቱ፥ ውሆች አዩህ ውሆችም አይተውህ ፈሩ ጥልቆች ተነዋወጡ፥ ውሆችም ጮኹ” ብሎ የተናገረው ትንቢት ተፈጸመ።
ጌታችንም ተጠምቆ ከውሃው ከወጣ በኋላ ሰማይ ተከፈተ ይላል። መተርጉሙ ሲያመሰጥረው፦
1) "ከመ ተጠምቀ ሰማያዊ ናሁ ወረደ እምሰማይ ወሀለዎ ከመ ይዕርግ ውስተ ሰማይ" (ሰማያዊው እንደተጠመቀ ከሰማይ እንደወረደ ወደሰማይ እንደሚያርግ ለማስረዳት)
2) "ወዳግም እስመ አናቅጸ ሰማያት ተዐጽዉ በምክንያተ ዕልወተ አዳም ..." (በአዳምና በሰዎች በደል ምክንያት የሰማያት ደጆች ተዘግተው ነበር። ገነትም ተዘግታ በእሳት ጦር ትጠበቅ ነበር። ጌታችን በተጠመቀ ጊዜ በጥምቀቱ ምክንያት የሰማይ ደጃፎች ተከፈቱ)።
3) "ሣልስ ያጠይቀነ ከመ እለ ይጠመቁ ይትረኃው ሎሙ አናቅጸ ሰማያት ..." (ለሚጠመቁ ሰዎች የሰማያት ደጃፎች እንደሚከፈቱላቸውና ከሞት ከተነሡ በኋላ ወደ ሰማይ እንደሚወጡ ያስረዳል)።
4) ሰማያት ተከፈቱ መባሉ ደጃፍ በተከፈተ ጊዜ በውስጥ ያለው ዐዲስ ነገር እንዲገለጥ በጥምቀትም ዐዲስ ምስጢር ይገለጣልና ነው።
አብ በሰማይ ኹኖ “ዝንቱ ውእቱ ወልድየ ዘአፈቅር ዘቦቱ ሠመርኩ” (በርሱ ደስ የሚለኝ የምወድደው ልጄ ይኽ ነው) ብሎ ሲመሰክር፤ መንፈስ ቅዱስም በርግብ አምሳል ወርዶ በራሱ ላይ ተቀመጠ፤ አካላዊ ቃል ክርስቶስም በጽንፈ ዮርዳኖስ ቁሞ ታየ፡፡
መንፈስ ቅዱስ በርግብ አምሳል ለምን ወረደ? ቢባል
ርግብ ኀዳጊተ በቀል (በቀልን የምትተው) ናት፤ መንፈስ ቅዱስም ኀዳጌ በቀል፤ ቸር ነኝ ሲል፡፡
ርግብ ልጆቿን ተከባክባ እንድታሳድግ፤ መንፈስ ቅዱስም ለምእመናን ልሕቀት መንፈሳዊ እሰጣለኊ ሲል፡፡
የርግብ ዐይኑ ነጩም ጥቁሩም ያያል አይከፈልበትም፤ መንፈስ ቅዱስም ዕውቀት ሥልጣን አይከፈልብኝም ሲል፡፡
ርግብ በኖኅ ጊዜ የጥፋት ውሃ መጒደሉን የወይራ ቅርንጫፍ ይዛ ብሥራተ ፍሥሐ የምሥራችን እንደገለጸች፤ መንፈስ ቅዱስም በርግብ አምሳል በመውረድ ከርሱ ጋር የሥልጣን አንድነት ባለው በወልድ ኢየሱስ ክርስቶስ በመውረድ የፍዳ ዘመን ማክተሙን ተስፋ መስቀልን አብሥሯል፡፡
ርግብ ክንፏን ቢመቷት፤ ዕንቊላሏን ቢሠብሩባትም ቤቷን ካላፈረሱባት በቀር አትኼድም፤ መንፈስ ቅዱስም ምንም ኀጢአትን ቢሠራም፤ ጨርሰው ካልካዱት በስተቀር አይለይምና፡፡
ይኸውም በምስጢረ ሥላሴ ትምህርት እንደምንረዳው ከሰማይ ኾኖ የመሰከረው ክርስቶስ በቃልነት መንፈስ ቅዱስ በእስትንፋስነት ያሉበት (ሕልው የኾኑበት) አብ ነው።
ወርዶ በወልድ ራስ የተቀመጠው አብ በልቡናነት ክርስቶስ በቃልነት ሕልው የኾኑበት መንፈስ ቅዱስ ነው። በጽንፈ ዮርዳኖስ ቆሞ የታየው አብ በልቡናነት መንፈስ ቅዱስ በእስትንፋስነት ሕልው የኾኑበት አካላዊ ቃል ክርስቶስ ነው፤ እንዲኽ አድርገው የአካል ሦስትነታቸውን የፈቃድ አንድነታቸውን ለማስረዳት አብ በደመና ኾኖ መሰከረ፤ መንፈስ ቅዱስ በአምሳለ ርግብ ወርዶ ታየ፤ አካላዊ ቃል ክርስቶስ በጽንፈ ዮርዳኖስ ቆሞ ታየ።
በዚኽም የሥላሴ አንድነትና ሦስትነት በሚገባ ሲታወቅ በተጨማሪም “በርሱ ደስ የሚለኝ የምወድደው ልጄ ይኽ ነው” ብሎ እግዚአብሔር አብ በመመስከሩ ቅድመ ዓለም ከአብ ያለ እናት የተወለደው በኋለኛው ዘመን ከእመቤታችን ያለ አባት በኅቱም ድንግልና የተወለደው እግዚአብሔር ወልድ ተቀዳሚና ተከታይ የሌለው አንድ ብቻ መኾኑ በሚገባ ተረጋግጧል፤ ዕለቱም በጽርዕ ቋንቋ ኤጲፋንያ ሲባል በግእዝ አስተርእዮ በዐማርኛም የመታየት የመገለጥ ጊዜ ተብሏል፡፡
ኢትዮጵያ ሀገራችን ስለ ነገረ ጥምቀት የሰማችው ከሌላው ዓለም አስቀድማ ጌታችን ባረገ በጥቂት ወራት (በ34 ዓ.ም) በኢትዮጵያው ጀንደረባ አማካይነት ነው (የሐዋ 8፥26-39)፤ ይህም በዐል ከዘጠኙ ዐበይት በዐላት አንደኛው ሲሆን ጌታችን ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ ወንዝ ስላመራ ይህንን ለማሰብ ታቦታቱ ወደ ባሕረ ጥምቀቱ ያመራሉ።
በዚህ መልኩ መከበር እንዴት ተጀመረ? የሚለውን ሊቀ ትጉኃን ኃይለ ጊዮርጊስ በጻፉት የነገረ ሃይማኖት መጽሐፍ ላይ የጻፉትን ለአንባብያን ለማካፈል ወደድኩ። ይኸውም ከ515-529 ዓ.ም ለ14 ዓመት ኢትዮጵያን በመሩት በአጼ ገብረ መስቀል ዘመን ሲሆን በጊዜው ቅዱስ ያሬድ የነበረበት ጊዜ በመሆኑ ከዝማሬው በመነሣት ታቦታቱ ጥር 11 ጠዋት ከመንበረ ክብራቸው ተነሥተው ወደ ባሕረ ጥምቀቱ አምርተው አመሻሹ ላይ ይመለሱ ነበር ብለዋል፡፡
ከዚያም ከ1157-1197 ዓ.ም ድረስ ለ40 ዓመት ኢትዮጵያን በመራው በታላቱ ጻድቅ ንጉሥ በላሊበላ ዘመን በአንድ አካባቢ ያሉ አብያተ ክርስትያናት ታቦታቱ ባንድ ላይ እንዲያከብሩ ንጉሥ ላሊበላ ታላቅ መንፈሳዊ ዐዋጅን አሳውጆ በአንድ አካባቢ፣ ወረዳ፣ ያሉ በአንድ ላይ ማክበር ጀመሩ፤ በርሱ ዘመን የነበሩት ታላቁ ጻድቅ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ በአክሱም፣ በጎንደር፣ በሸዋ፣ በአንኮበር፣ በመርጡለ ማርያም እየሄዱ ባሕረ ጥምቀቱን እንደባረኩ ይጽፋሉ፡፡
109 views08:33