Get Mystery Box with random crypto!

መፍትሔው ግራ አለመጋባትና በአማራነትህ ፀንቶ መቆም ነው! ልጅ እያለሁ ፤ በነጭ ወረቀት ላይ በ | ዘሪሁን ገሠሠ

መፍትሔው ግራ አለመጋባትና በአማራነትህ ፀንቶ መቆም ነው!

ልጅ እያለሁ ፤ በነጭ ወረቀት ላይ በስእል አሽሞንሙነው የገጠሟቸውን አጭሬ ግጥሞች ፥ ገበያ ላይ ወይም ሰው በሚበረክትበት ቦታ ይቀመጡና ፥ እያነበቡ በስሙኒ የሚሸጡ በርካታ ስራ ፈጣሪዎችን አስታውሳለሁ፡፡ ታዲያ ሻጩ በእጁ የያዛቸውን አጭሬ ግጥሞች እያነበበ ሲያስተዋውቅ ፥ ውስጥህ የገባውንና ስሜትህን የኮረኮረውን ግጥም "እሷን አምጣት!" ትልና በስሙኒ ሸምተህ ግድግዳህ ላይ ትለጥፋለህ፡፡

ታዲያ! በዚያ ዘመን ተገዝተው ከኛ ግድግዳ ላይ ከተለጠፉት አጭሬ ግጥሞች መካከል ፦

" ቢወፍሩ ዱባ ፤ ቢቀጥኑ ትንኝ"
"ቢያወሩ አፈኛ ፤ ዝም ቢሉም ሞኝ"
አምላክ ከዚህ ሁሉ አሟልተህ ስጠኝ!"
.
.
የምትልን ግራ የተጋባ ሰው እንደገጠማት የምታሳብቅ ግጥም ፈፅሞ እስካሁን አልረሳትም፡፡

ጓዶች! የአማራ ህዝብም ላለፉት ሰላሳ አመታት በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ፥ የገጠመው እንደዚህ ግራ የተጋባ ነገር ነውኮ!

የጥላቻ ትርክት ጡጦ ጠብተው ያደጉ ፅንፈኛ ብሄርተኞች ፥ በጠላትነት ፈርጀውትና የሀገረ-መንግስቱን ፖለቲካ ተቆጣጥረው ፍዳውን ሲያበሉት ፥ እንደህዝብ ማንነቱን ዋጋ ሰጥቶ ከመደራጀት ይልቅ "ዘር ለገበሬ ነው!" እያለ "ኢትዮጵያ ኢትዮጵያ" በማለቱ " አሀዳዊ ፣ ደፍጣጭ ፥ ነፍጠኛ ፣ ትምክህተኛ ፣ ...ወዘተርፈ " የሚሉ ስሞች እየተሰጠው መከራውን ሲያይ ኖረ፡፡

በታሪክ አጋጣሚ ለ27 አመታት የሀገረ-መንግስቱን ስልጣን ይዘው የኖሩት የትግራይ ፅንፈኛ የብሄር ሀይሎች ፥ በህዝብ ትግል ከማዕከላዊ መንግሥት ስልጣን ተገፍተው ቢሰነብቱም ፥ "ፍጥጥ" ያሉት የከፉ ፅንፈኞች ተተክተው ፥ የፍረጃ ስያሜዎቹንም ለማጥቂያነት እየተጠቀሙ አባብሰው ቀጠሉ እንጂ የተለየ ነገር አልተፈጠረም!

ታዲያ! ከዚህ ሁሉ መከራ በኃላ የአማራ ህዝብ የተጋረጠበትንና ፥ ከጊዜ ወደጊዜ አሳሳቢ እየሆነ የመጣውን የህልውና አደጋ ለመቀልበስ ብሎም ጥቅምና ፍላጎቱን ለማስከበር " እንደህዝብ ተደራጅቼ የሀገረ-መንግስቱን የፖለቲካ አሰላለፍ ልመሳሰል!" በማለት " አማራ ነኝ!" ብሎ ሲነሳ ደግሞ ፤ የራሳቸውን ዘመን ተሻጋሪ የግብር መጠሪያ አውልቀው " የአማራ ፅንፈኞች" የሚል ካባ ደረቡለትና ፥ ይኸው ለጅምላ እልቂትና ሰቆቃ በይፋ መጠቀም ጀምረው አረፉት!

ገጣሚው "ቢወፍሩ ዱባ ፤ ቢቀጥኑ ትንኝ " ያለውም እንዲህ ግራ ቢገባው ነውኮ!

ለዚህ መፍትሔው " ትንኝም ፥ ዱባም ፥ ..!" ለሚሉት መስሚያህን "ጥጥ" አድርገህ ፥ ፍፁም ጠንካራ በሆነ ህዝባዊ አደረጃጀትና ትግል ፥ ለዘመናት የገነቡትን የትርክትና የጥላቻ ግንብ በመናድ ራስህን የአላፊ አግዳሚው መፈንጫ ከመሆን መዳን ብቻ ነው!

ይኸው ነው!