የጠቅላዩ አጭር መግለጫ ፥ በወንጀሉ ላይ ምርመራ እንዳይደረግ የተሰጠ ትእዛዝ ይመስለኛል! ጠሚው የአቦሰጥ ፍርድና ብይን ከሰጠ በኃላ ፥ " ፖሊስና የፍትህ ተቋማቱ የተፈፀመውን ወንጀል መርምረው ለህዝብ ይፋ ያድርጉ!" ማለት የዋህነት ካልሆነ ምንም ሊሆን አይችልም፡፡ ጠ/ሚኒስቴር አብይ አህመድን የመሠለ መስሚያው ጥጥ የሆነ ፍጡርኮ በአለም ላይ መኖሩን ሁሉ መጠራጠር ጀምሬአለሁ፡፡ እንደውም ቲክቶክ ላይ " እዋዋን ማንንም አልሰማም!" የሚለው ልጅ የሱን ገፀ-ባህሪ የተጫወው ይመስለኛል፡፡ ሀገሪቱ ላይ ስርአት አልበኝነትና የተቋማት ልፍስፍስነት ተባብሶ የቀጠለው በዋናነት በጠቅላይ ሚኒስቴሩ ማንአለብኝነትና እብሪት ነው፡፡ የሀገሪቱን ሁሉንም ተቋማት ተጠሪነታቸውን ለራሱ አድርጎ ፥ የሚመሩበትን ስርአትና የተሰጣቸውን ተልእኮ ሁሉ እውቀቱ ፣ ሙያው ፣ መብቱ ፣ ስርአታዊ ሀላፊነቱ ሳይኖረው እንዳሻው የሚረጋግጣቸው ራሱ ነው፡፡ አንድ ወንጀል ሲፈፀም መመርመር ፣ ማጣራትና ለህዝብ ይፋ ማድረግ የማን ሀላፊነት ነው ? የሀገሪቱ ፖሊስና የፍትሕ አካላት ጠቅላይ ሚኒስቴሩ የተፈፀመው ወንጀል ያስከተለው ጉዳትና ሟቾች እንኳ በቅጡ ባልተለዩበት ሁኔታ ፥ በብርሃን ፍጥነት ሟችንም ፣ ገዳይንም ፥ የግድያ ምክንያትን ሳይቀር በይፋ በገለፁበት ሁኔታ ፥ ከነአካቴው በጉዳዩ ላይ ምርመራስ ያደርጋሉ ወይ ? ከጠቅላይ ሚኒስቴሩ የተለየስ የምርመራ ግኝት አገኘን እንዲሉ የሚጠብቅ የዋህ አለ ወይ ? "ሙስና አትበሉ ፥ ሌብነት ነው!" እያለ አፉን ቀባብቶ ሲሰብክህ ይቆይና በፓርላማ ፊት ፥ " ...እኔ በግሌ ከወዳጆቼ ለምኜ የማመጣው ገንዘብ ነው!" ሲል ትንሽ እንኳ ፥ ተጠሪነቱ ለራሱ የሆነው "ፀረ-ሙስና" የሚባልን ተቋም ፥ እርባናቢስ እያደረገው እንደሆነ የማይረዳ "መስሚያው ጥጥ" የሆነ ጉደኛ ሰው ነው! በሁሉም ዘርፍ ብትሄዱ የሀገሪቱን ተቋማት ግንባር ቀደም ሆኖ ህግጋትና ስርአታቸውን የሚጥሰው ፥ በህግ የተሰጠ ሀላፊነታቸውን የሚነጥቀው ይኸው " ስዩመ-እግዚያብሄር ነኝ!" የሚል ሠውዬ ነው! አቶ ግርማን ጨምሮ በአሳዛኙ ጥቃት ህይወታቸውን ያጡ ወገኖቻችንን ነፍስ ይማር! ለወዳጅ ዘመዶቻቸው መፅናናትን እመኛለሁ! 7.6K views20:14