Get Mystery Box with random crypto!

ትኩረት ልንሰጠው የሚገባ ነጥብ ነው! መቼም ፈቅደንም ሆነ ተገደን 'በአማራ ፖለቲካ ውስጥ አለንበ | ዘሪሁን ገሠሠ

ትኩረት ልንሰጠው የሚገባ ነጥብ ነው!

መቼም ፈቅደንም ሆነ ተገደን "በአማራ ፖለቲካ ውስጥ አለንበት!" እስካልን ድረስ ፤ ቃላቶቻችን ጥይት ሆነው የመግደልም ሆነ መድሀኒት ሆነው የመፈወስ ኃይል እንዳላቸው መገንዘብ በእጅጉ ያስፈልገናል፡፡

ፖለቲካዊ ተግባቦት/Political Communication ከስሜት በዘለለ ፥ ፖለቲካዊ አላማንና ግብን ከማሳካት አኳያ ካልተቀነበበ የሚወልደው አደጋና ኪሳራም የትየለሌ ነው፡፡

በተለይ ደግሞ በሳይበሩና በሚዲያዎች አካባቢ ፖለቲካዊ ሀሳቦቻችንን የምናቀርብና ለተግባቦታዊ ስርአቱ ቅርብ የሆንን ሰዎች  ፥ በዚህ ረገድ የመጣንበትን ገምግመን ራሳችንን ልናርም ፣ ልናበቃና ልንነቃ ይገባል ባይ ነኝ፡፡

አንዳንድ ወገኖቻችን በማወቅም ሆነ ባለማወቅ ፥  ሁኔታና ጊዜው ስለፈቀደላቸው ብቻ  ፥ በተለያዩ የማህበራዊ መገናኛ ዘዴዎች በፅሁፍ ፣ በድምፅና  በተንቀሳቃሽ ምስል የሚያሰራጯቸው አደገኛ ንግግሮች ፥  ተፅዕኗቸው እነሱ ጋር ባይደርስ እንኳ ሌላ ቦታ ገጀራ ፥ ጥይት ፣ እሳት ፣ መከራና ግፍ ሆነው ፥ "እንታገልለታለን" በምንለው ህዝብ ላይ እንደበረዶ ይዘንባሉ፡፡

የምንታገላቸው ፅንፈኛ የፖለቲካ ሀይሎች (ቡድኖች) እነዚያን ሀላፊነት የጎደላቸውና የአማራ ህዝብ መሠረታዊ የትግል ግብና አላማ ያልሆኑ የግለሰቦች  ሀሳብና ንግግሮች እያስተጋቡም " እነሱኮ አላማቸው ይኸ ነው!" ሲሉ እንደህዝብ አቋም ወስደው  ከፍተኛ የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ ያደርጋሉ ፥ ይቀሰቅሳሉ ፥ ለህዝባችን ተጨማሪ ጠላት ለመፍጠር ይተጋሉ፡፡

በተለይ ደግሞ የምንታገለው "የጥላቻ ጡጦ ጠብተው ያደጉና በህዝብ ስልጣን ላይ ያሉ የፖለቲካ ሀይሎችን" እንጂ ህዝብን እንደህዝብ ፈርጀን አለመሆኑን ማጤንና ማስረዳት ያሻል፡፡ ሹምምንቱንና ፖለቲከኛውን እንዳሻን መተቸት ፥ መዝለፍ መቃወም መብታችን ነው፡፡ ሆኖም እነሱ ሴራ ደርተው ለስንፍናቸውና ለወንጀላቸው መደበቂያ የሚያደርጉትን የወጡበት  ፥ ማህበረሰብ ወይም ግለሰባዊ አምልኮዎች (ሀይማኖቶች ) በተመለከተ በጅምላ ለሴራ የሚመነዘር ፖለቲካዊ ንግግር ማድረግ ፥ ፈፅሞ ጎጂና በገዛ ወገኖቻችን ላይ ተጨማሪ መከራ የሚያዘንብ መሆኑን በሚገባ በመረዳት ተጠንቅቀን መጓዝ ይኖርብናል፡፡

ይኸው ነው!