2022-02-28 20:43:24
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን
እንኳን ጌታችን ለመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዐብይ ጾም (ጾመ ኢየሱስ) በሰላም አደረሰን አደረሳችሁ!!!
ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለምን 40 ቀን እና ሌሊት ጾመ፤ እኛስ ለምን 55 ቀን እንጾማለን?
ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለምን 40 ቀን እና ሌሊት ጾመ
እኛስ ለምን 55 ቀን እንጾማለን
1ኛ. ነቢያት 40 ቀን ጾመዋልና 40 ጾመው ትንቢት የተናገሩለት ስለ እርሱ መሆኑን ለማጠየቅ
2ኛ. ቀድሞ ነቢያት 40 ቀን ጾመዋል፤ ጌታችንም ከ40 ቀን ቢያተርፍ ‹‹አተረፈ›› ቢያጎድል ‹‹አጎደለ›› ብለው ሕገ ወንጌልንም እንዲሁም ጌታን ላለመቀበል ምክንያት እንዳያደርጉ
3ኛ. ነቢዩ ሙሴ 40 መዓልትና ሌሊት ጾሞ ሕገ ኦሪትን ሰርቷል፤ ጌታችንም መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም 40 መዓልትና ሌሊት ጾሞ ሕገ ወንጌልን የሚሰራ ነውና፡፡
4ኛ. አዳም በ40 ቀን ያገኘውን ልጅነት አስወስዶ ነበርና ለእርሱ እንደ ካሣ ለማጠየቅ፤ እንዲሁም በ40 ቀን ተሥእሎተ መልክ ለተፈጸመለት ሰው ሁሉ ለካሣ እንደመጣ ለማጠየቅ፡፡
55 ቀናት መሆኑ
❖ ይህ ጾም አብዛኛውን የየካቲትና የመጋቢት ወራትን የሚይዝ ሲሆን የሚያዝያም ወር የሚጨምርበት ጊዜ አለ፤ እስከ ቀዳም ስዑር ለ55 ቀናት ይጾማል፡፡
❖ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የጾመው ለ40 ቀናት ሲሆን እኛ ለ55 ቀናት የምንጾምበት ምክንያት በ55 ቀን ውስጥ 8 ሳምንታት (8 ቅዳሜና 7 እሑድ) ይገኛሉ፡፡
❖ አንድ ላይ አሥራ አምስት ቀናት ይሆናሉ፤ እነዚህን ሰንበታት ከጥሉላት (ሰውነትን ከሚጠግኑ) እንጂ ከእህልና ከውኃ ስለማይጾም የእሑድና የቅዳሜን ምትክ አስራ አምስት ቀናት ተጨምረው ይጾማሉ፡፡
በተጨማሪ
❖ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክ ተዋህዶ ቤተክርስትያን ይህ መታሰብያ ይዘከራል እስከዛሬ ድረስ ከጾመ 40 በፊት ያለው የ1 ሳምንት ጾም (ዘወረደን) ስንጾም እንኖራለን።
❖ ሕርቃል (አራቅሊዮስ) የበዛንታይን ንጉሥ ነበረ 614 ዓ.ም፤ ይህ ሳምንት በስሙ የተጠራበት ምክንያት በዘመኑ ፋርሶች ኢየሩሳሌምን ወርረው የጌታችን መስቀል ማርከው ወስደው ነበር ሕርቃልም በ628 ዓ.ም ወደ ፋርስ ዘምቶ ኮሰሮየን ድል አድርጎ የጌታችንን መስቀል አግኝቶ ሲመለስ መስቀሉን እርሱ እራሱ ተሸክሞ ከፋርስ እስከ ኢየሩሳሌም ድረስ አለጫማ በእግሩ እየሄደ አምጥቶ ለኢየሩሳሌም ምዕመናን አስረከበ።
❖ የኢየሩሳለም ምዕመናን፣ ኤጲስ ቆጶሳትና ካህናቱም በጣም ተደስተው ስለነበር ስለ እርሱ ብለው ሰባት ቀን ሙሉ በጾምና በጸሎት የያዙትን ሱባኤ ከጌታችን ጾም ጋር ሆኖ በየአመቱ ሰባት ቀን እንዲጾም አዘዙ።
❖ ስለዚህ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክ ተዋህዶ ቤተክርስትያን ይህ መታሰብያ ይዘከራል እስከዛሬ ድረስ ከጾመ 40 በፊት ያለው የ1 ሳምንት ጾም(ዘወረደን) ስንጾም እንኖራለን።
❖ ሌላው ደግሞ ሰሞነ ሕማማት የመጨረሻው ሳምንት ስሆን ይህን ሐዋርያት የጌታችን ነገረ መስቀል ስቃዩን ግርፋቱን ስቅለቱን ሞቱን እያሰቡ የፆሙት ሳምንት ነው።
❖ ስለዚህም እኛም የሐዋርያትን ፈለግ ተከትለን የጌታችንን መከራውን ስቃዩን መገረፉን መሰቀሉን መሞቱን እያሰብን እንጾማለን፤ እነዚህ ሁለት ሳምንታት (ጾመ ሕርቃል እና ሰሞነ ሕማማት) ስጨመሩ 55 ቀን ይሆናል።
በእነዚህ 55 ቀናት ውስጠ ስምንት ሳምንታት አሉ፤ ስያሜአቸውና ትርጉም በቅደም ተከተል
❖ 55 ቀናት 15 ቀናት- 7 እሁድ እና 8 ቅዳሜ 40 ቀናት
1ኛ ሳምንት
❖ ዘወረደ- የክርስቶስ ከሠማይ መውረድ
2ኛ ሳምንት
❖ ቅድስት- የሰንበት ቅድስና
3ኛ ሳምንት
❖ ምኩራብ- ክርስቶስ በምኩራብ ስለማስተማሩ
4ኛ ሳምንት
❖ መፃጉ- ክርስቶስ በሽተኞችን መፈወሱ
5ኛ ሳምንት
❖ ደብረዘይት- በዚህ ተራራ ስለ ዳግም ምጽአቱ ማስተማሩ
6ኛ ሳምንት
❖ ገብርሔር- ለደግ አገልጋይ ዋጋ ያለው መሆኑ
7ኛ ሳምንት
❖ ኒቆዲሞስ- ጌታ ከኒቆዲሞስ ጋር መነገጋሩ
8ኛ ሳምንት
❖ ሆሳዕና- እየተመሰገነ ወደ ቤተ-መቅደስ መግባቱና ስለ እኛ ህማማትን መቀበሉ ይታሰብበታል
እነዚህ 55 ቀናት ለሦስት ይከፈላሉ
1ኛ. ዘወረደ
2ኛ. የጌታ ጾም (አርባ ቀን) ከቅድስት እስከ ሆሳዕና ያለው
3ኛ. ሰሙነ ሕማማት
እስከ ስንት ሰዓት እንጹም
❖ ቅዱሳን አባቶቻችን ከሌሎቹ አጽዋማት በተለየ ሁኔታ በዓቢይ ጾም እስከ ስንት ሰዓት መጾም እንዳለብን በመጽሐፈ ነገሥት በመጀመርያው አንቀጽ ቁጥር 15ላይ ልዩ ሥርዓት ሠርተውልናል፡፡ ይህም
1ኛ. ዘወረደን ፀሐይ እስክትጠልቅ ድረስ (አሥራ ሁለት ሰዓት)
2ኛ. ከቅድስት እስከ ኒቆዲሞስ እስከ 11(አሥራ አንድ) ሰዓት ድረስ
3ኛ. በሰሙነ ሕማማት ከዋክብት እና ጨረቃ እስኪታዩ ድረስ (ማታ 1፡00)
4ኛ. አክፍሎት
❖ የተቻለው ከጸሎተ ሐሙስ እስከ ትንሳኤ፤ ያልተቻለው ደግሞ ከስቅለት እስከ ትንሳኤ ማክፈል እንደሚገባ ከዚህ ሥርዓት አብልጦ የጾመ ዋጋው እንደሚበዛለት አስፍረውልናል፡፡
ጾሙን መድኃኒተ ሥጋ መድኃኒተ ነፍስ የምናገኝበት ያድርግልን፡፡ አሜን፡፡
1.8K views.........., 17:43