2022-04-22 09:50:34
የኢትዮጵያ ስቅለት
(ዳንኤል ገብረማርያም)
¤¤¤¤¤¤¤¤
በኢትዮጵያ አገራችን
ለረጂም ዓመታት ቀኑ ረቡዕ ነበረ
እውነትን ለመክሰስ እውነትን ለመስቀል
ብዙ ተነገረ ብዙ ተመከረ!
ጊዜ ጊዜን ወልዶ
ኀሙስ ሲተካ የምክር ቀን ሄዶ
በዕለተ ኀሙስም
በመልካሙ ምድር በአትክልቱ ሥፍራ
እውነትን ለመያዝ
የተላከው መንጋ የሐሰት ጭፍራ
በይሁዳ መሪነት
ችቦ እያበራ በድፍረት ቀረበ
ጊዜው ደርሷልና እውነት ተከበበ ፍትሕ ተከበበ!
በኀሙሱ ምሽት
የሚበራውን ችቦ ከርቀት ያየ ሰው
መሪውን ይሁዳ
የብርሃን መገኛ ብሎ አሞገሰው
የሮምንም ጭፍራ
የነጻነት ታጋይ ሲል አቆለጳጰሰው!
ሕዝብ ግን የዋህ ነው
የሮምን ሠራዊት ፊት ሆኖ ሲመራ
ለቅጽበት አየና
ፈርዖኑ ይሁዳን ሙሴ ብሎ ጠራ!
ይሁዳ ከሃዲ ነው
ጌታውን ለመሸጥ ለአይሁድ ቃል የሰጠ
በማስመሰል ስሞ
በሚጠፋ ዲናር አምላኩን የሸጠ
የነበረውን ክብር በብር የለወጠ!
የኢትዮጵያ ይሁዳም ለጠላት የዋለ
በማስመሰል ከንፈር ሕዝብ እያታለለ
በሐሰት ስሞ
አገሬን ሽጧታል ለአረመኔ ጭፍራ
እያደረሱባት ግፍና መከራ
እየወሰዷት ነው ወደ ቀራኒዮ ወደ ራስ ቅል ሥፍራ!
እንደቀያፋ ደጅ በኢትዮጵያ ምድር
ፍትሕ እንዲገደል እውነት እንዲቀበር
ውሳኔ ተሰጥቷል
ኀሙስ የቀን ቅዱስ የሚባለው ቀርቷል።
የሞት ጽዋ ትለፍ የተባለው ጸሎት
ከአገሬ አፍ ወጥቶ ቢደርስም ጸባዖት
የዓርቡን መከራ ስቃይ አላስቀረም
የከሳሾቿን ምክር እንዳይኾን አልሻረም።
ኀሙስ እንዲህ ቢያልፍም
በኢትዮጵያ ሰማይ ይኸው ለአራት ዓመት ዓርብ ሆኖ ቀርቷል
ክርስቶስ ተሰቅሎ በመስቀል ላይ ሞቷል
በመከራው ጽናት ደም ግባቱ ጠፍቷል።
ክርስቶስ እውነት ነው እውነት ነው ክርስቶስ
ክርስቶስ ፍትሕ ነው ፍትሕ ነው ክርስቶስ
ክርስቶስ ሕዝብ ነው ሕዝብ ነው ክርስቶስ
ታዲያ ምን ያደርጋል
በሮሞቹ ግዛት
በጸሐፍት ረበናት
በአይሁድ ጽኑ መሻት
በፈቃድ ተይዞ በመስቀል ይሞታል
ልብሱ ይቀደዳል በጥፊ ይመታል
ይላገጥበታል ይዘበትበታል።
እጹብ ነው ድንቅ ነው
የአገሬ ክርስቶስ ትናንት ይሰቀላል ዛሬም ይሰቀላል
በግፈኞች ሴራ በከሳሾቹ ፍርድ መስቀል ላይ ይውላል
አንተ ከኾንህ እውነት
እስኪ ራስህን አድን ኃይልህን ግለጥ ይባላል!
አገሬ ኢትዮጵያ ኾና ቀራንዮ ኾና ጎልጎታ
ሰርክ ይታይባታል
በግፈኞች ፍርድ ክርስቶስ ሲሰቃይ ፍትሕ ሲንገላታ።
በዚህ የራስ ቅል ሥፍራ
የሚኾነው ነገር እጅጉን ይደንቃል
አስመሳዩ ኹሉ እንደኢየሩሳሌም ሴት ደረቱን ይደቃል
ወዳጅ የተባለው ሦስት ጊዜ ክዶ ከመስቀል ይርቃል።
በዚህ ቀራንዮ በአገሬ ተራራ
በዚህ ጎልጎታ በራስ ቅል ሥፍራ
የሚሰማውን ድምጽ
የሚያየውን ሁሉ ከቶ ማንስ ያምናል?
ውኃው አፉ ደርቆ
ውኃ አጠጡኝ እስኪ ተጠማሁኝ ይላል
እንጀራው ርቦት
ወዮ የምግብ ያለህ ብሎ ይማለላል!
በሀገሬ ምድር
ዛሬም ቀኑ ዓርብ ነው ስቅላቱ አልቆመም
ያለአንዳች በደሉ
በግፍ በመከራ ሕዝብ ነው ሚገረፍ ሕዝብ ነው የሚታመም።
በዚህ የስቅለት ሥፍራ
ወዳጅ የተባለው በፍርሃት ቢርቅም
የሮሞች ጭካኔ እጅግ ቢያስጨንቅም
ከመስቀሉ ግርጌ በጽናት ቆማ
ስለተሰቀለው ደም የምታነባ
የክርስቶስ እናት ያቺው የተባለች
የሰቃልያኑ መሳቂያ የኾነች
የተሰቀለውን ወልዳ ያሳደገች
በተፈጸመው ግፍ ልቧ የቀለጠ አንዲት ምስኪን አለች!
መከራውም ይብቃ ግፉም ከቶ ይብቃ ብላ ትጸልያለች!።
በሕይወት ታሪኩ
በማንነት ልኩ
ክርስቶስ የኾነ የአገሬን ደግ ሰው
ሰቅሎ ለመግደል ነው
ይኸ ኹሉ መንጋ እንዲህ የሚጮኸው እንዲህ የሚታመሰው።
ምስኪኑ የአገሬ ሕዝብ ክርስቶስ አምሳሉ
ተፈጽሞበትም የዓለም ግፍ በሙሉ
ደጉ የኢትዮጵያ ሕዝብ በራስ ቅል ሥፍራ
መስቀል ላይም ኾኖ ጸንቶበት መከራ
የሚያዝንለት የለም ለእርሱ የሚራራ
እወደድ ባዩ ሰው አድር ባዩ መጥቶ
የተሰቀለውን የሕዝቤን ጎን ወግቶ
ደም ውኃ ያፈስሳል
ሕዝቤ ግን የዋህ ነው
በርኅራኄው ብዛት ወጊው ለንጊዮስን ዐይኑን ይፈውሳል።
ግን እንዲህ አይቀርም
ዛሬ ዐርብ ኾኖ ፀሐይ ቢጨልምም
ከዋክብት ቢረግፉ ጨረቃ ብትቀልምም
ተስፋ አለኝ አሁንም
ሕልም አለኝ አሁንም
የዐርብ ፀሐይ መሽቶ ቅዳሜ ይመጣል
በግዞት ያለው ሕዝብ አርነት ይወጣል!!!
ቅዳሜም ያልፍና እሑድ ንጋቱ ላይ
መቃብር ተከፍቶ
ለኢትዮጵያ ይወጣል የትንሣኤ ብርሃን የትንሣኤ ፀሐይ
እግዚአብሔር ያድርሰን ይን ተአምር እንድናይ!!!!
አሜን።
316 views06:50