2022-06-30 16:59:35
የዓለምን ታሪክ ከቀየርክ በኋላ ተራ ሆነህ መታየት አትችልም
Daniel Kibret
ኢትዮጵያ ዓባይን ስትገድብ የዓለም ታሪክ እየተቀየረ ነበር፡፡ ዓባይ ከኢትዮጵያ ይመነጫል፣ ወደ ሱዳንና ወደ ግብጽ ይፈስሳል የሚለው ትርክት ከሰው ልጅ መፈጠር ጋር አብሮ የኖረ ትርክት ነው፡፡ በመካከለኛው ምሥራቅና በአውሮፓ እንደ ዓባይ ያለ ረዥም ወንዝ ባለመኖሩ ስለ ዓባይ የማያወራ ጥንታዊ ሕዝብ አልነበረም፡፡ ግብጽ የአፍሪካ፣ የአውሮፓና የእስያ መገናኛ ናት፡፡ ለግብጽ ሕይወት የሚሰጠው ደግሞ ዓባይ ነው፡፡ በዚህም ምክንያት የእስያ፣ የአውሮፓና የአፍሪካ ሰዎች ስለ ዓባይ የሚተርኳቸው ጥንታውያን አፈታሪኮች አሏቸው፡፡
የዓባይ መነሻው የት ነው? ይሄን ጥያቄ የጥንት ሥልጣኔ የነበራቸው ሕዝቦችና መሪዎች ሁሉ ጠይቀዋል፡፡ የግሪክና የሮም አማልክት ጠይቀዋል፡፡ መነሻውንም ለማየት ወደ ኢትዮጵያ መጥተዋል፡፡ የባቢሎንና የአሦር ነገሥታት ወደ ግብጽ ከመጡ በኋላ ወደ ደቡብ ለመውረድ ባይሳካላቸውም እስከ ታኅታይ ግብጽ ድረስ ፍለጋ ወርደዋል፡፡ የግሪኩ ንጉሥ እስክንድር ወደ ኢትዮጵያ ሰሜናዊ ክፍል መጥቶ ነበር፤ የሮም ነገሥታትም እስከ ሜርዌ ድረስ መጥተዋል፡፡
ከሮም ሥልጣኔ በኋላ ኃያላን የነበሩት ስፔንና ፖርቹጋል የመጀመሪያ አሠሳቸውን ወደ ኢትዮጵያ እንዲያደርጉ ከገፋፏቸው ነገሮች አንዱ የዓባይን ምንጭ ለመፈለግ ነው፡፡ በመካከለኛው ዘመን ሕንድ፣ ከዚያም ደቡብ ዓረቢያ፣ በመጨረሻም ደቡብና ሰሜን አሜሪካ በአውሮፓውያን እንዲታወቁ ያደረጋቸው ኢትዮጵያን ፍለጋ የተደረገው ጉዞ ነው፡፡
ከዛግዌ ነገሥታት ጀምሮ ዓባይን ለመገደብ ያልሞከረ ንጉሥ ኢትዮጵያ ውስጥ የለም፡፡ ንጉሥ ሰይፈ አርዕድ ዓባይን ለመገደብ በነበረው ፖሊሲ የረር ላይ በነበረው ቤተ መንግሥት ከአውሮፓ ከመጡ ባለሞያዎች ጋር መክሮ ነበር፡፡ ዐፄ ዳዊትና ዐፄ ይስሐቅ ከፖርቹጋል የውኃ ባለሞያዎችን አስመጥተው ነበር፡፡ እስከ ንጉሥ ኃይለ ሥላሴ የነበሩ ነገሥታት ሁሉ ዓባይ ለኢትዮጵያ ጥቅም ሳይሰጥ መቅረቱ ይቆጫቸው ነበር፡፡
እስከ ቅኝ ግዛት ዘመን ድረስ የዓባይ ጉዳይ በአብዛኛው የኢትዮጵያና የግብጽ ጉዳይ ነበር፡፡ ግብጻውያን ኢትዮጵያ ዐቅም ያገኘች ቀን ዓባይን ትገድበዋለች ብለው እንደሠጉ ነው የኖሩት፡፡ በዐፄ ይስሐቅ ዘመን ዓባይን የሚገድቡ ባለሞያዎችን ፍለጋ ወደ አሪጎን(ምዕራብ አውሮፓ) ተጉዞ የነበረው የንጉሡ መልእክተኛ ጣብሪዚ፣ 13 የጥበበ ዕድ ባለሞያዎችን ይዞ ወደ ኢትዮጵያ ሲመጣ ግብጾች የካቲት 20 ቀን 1421 ዓም ያዙት፡፡ ጣብሪዚ ተሰቃይቶ እንዲሞት ነው የተደረገው፡፡ የግብጹ ንጉሥ ጣብሪዚን ከገደለ በኋላ ‹ بينما تصعد إثيوبيا ستسقط مصر› ብሎ መናገሩ ይተረካል፡፡ ‹ኢትዮጵያ ከፍ ከፍ ካለች ግብጽ ትወድቃለች› ማለቱ ነው፡፡ በዚህም የተነሣ በሃይማኖትም፣ በንግድም የሚመጡ ሰዎቻቸው ነገሩን ሲከታተሉ ኖረዋል፡፡ ግብጽ በ18ኛውና 19ኛው መክዘ ራሷ ጦር ሰብቃ ዘምታ ኢትዮጵያን ለማዳከም ሞክራለች፡፡ አልተሳካላትም እንጂ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ የኢትዮጵያን ጠላቶች በማገዝ ኢትዮጵያ ፊቷን ወደ ዕድገቷ እንዳትመልስ ስታደርግ ከርማለች፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ከተፈለፈሉ ‹ነጻ አውጪ› ድርጅቶች ውስጥ የግብጽን ርዳታ የማያገኝ ድርጅት አልነበረም፡፡ ሕወሐት ደርግን ባሸነፈ ጊዜ መጀመሪያ ከጥቅም ውጭ የሆኑት በዓባይ ተፋሰስ ላይ የተሠሩ ሥራዎች ናቸው፡፡ የፓዌ ፕሮጀክትና የጣና በለስ ፕሮጀክት ለዚህ ዓይነተኛ ማሳያ ናቸው፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ በተደረጉ የእርስ በርስ ጦርነቶች ውስጥ ግብጽ አንደኛውን ወገን በመደገፍ ሀገሪቱን ለማዳከም ተጠቅማበታለች፡፡ በዓለም አቀፍ ድርጅቶች ውስጥ ያሏትን ዜጎችና ደጋፊዎች በመጠቀም ኢትዮጵያ የተሻለ ድጋፍ እንዳታገኝ ስታደርግ ኖራለች፡፡ ግብጽ ኢትዮጵያን በተመለከተ ሁለት ፖሊሲዎችን ስትከተል ነው የኖረችው፡፡ ከተቻለ ኢትዮጵያን ወደ ብዙ ትንንሾች መከፋፈል፤ ካልተቻለ ተጽዕኖ እንዳትፈጥር አድርጎ ማዳከም፡፡
አውሮፓውያን አፍሪካን በቅኝ ግዛት መያዝ ሲጀምሩ የዓባይ ጉዳይ የኢትዮጵያና የግብጽ ጉዳይ ብቻ መሆኑ ቀርቶ - የኢትዮጵያ፣ የግብጽና የአውሮፓ ጉዳይ ሆነ፡፡ አውሮፓውያን ወደ ዓባይ ጉዳይ የገቡት በሁለት ምክንያት ነው፡፡ የመጀመሪያው በኢትዮጵያ አካባቢ የሚገኙ የታችኛውና የላይኛው ተፋሰስ ሀገሮችን በቅኝ ግዛት ስለያዙ የዓባይ ተፋሰስ ጉዳይ ባለቤቶች ነን አሉ፡፡ ኢትዮጵያ የሌለችበትን ስምምነት እያዘጋጁ በቅኝ በያዟቸው ሀገሮች ስም መፈራረም ጀመሩ፡፡ አፍሪካ ከቅኝ ግዛት ከተላቀቀች በኋላም የቀድሞ ቅኝ ተገዥዎቻችን ጉዳይ ያገባናል ማለት ቀጠሉ፡፡
ሁለተኛው ምክንያታቸው የኢትዮጵያ በቅኝ ግዛት ካለመገዛት ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ኢትዮጵያ በአውሮፓ ያልተገዛች ብቸኛ የአፍሪካ ሀገር ሆና መውጣቷ ለአውሮፓውያን መልካም ምሳሌ አልሆነላቸውም፡፡ አፍሪካውያን፣ ላቲን አሜሪካውያን፣ እስያውያን፣ ከቅኝ ግዛት ለመላቀቅ እንዲችሉ ኢትዮጵያ የሞራል፣ የዲፕሎማሲ፣ የቁስና የሥልጠና ድጋፍ አድርጋላቸዋለች፡፡ በዚህ የተነሣ አንዲት በቅኝ ግዛት ያልተያዘች ሀገር ራሷን ችላ ስታድግና የሞራል ልዕልናዋን ስትጠብቅ መመልከት ለምዕራቡ ዓለም ሐፍረት ሆነበት፡፡ በዚህ የተነሣ ኢትዮጵያ ታሪክ የሚለውጥ ሥራ እንዳትሠራ ሲያደናቅፉ ኖረዋል፡፡ የዓባይ ግድብ ከእነዚህ አንዱ ነው፡፡
የምዕራቡ ዓለም በሁለት መንገድ የኢትዮጵያን የዓባይ ፕሮጀክቶች ሲያደናቅፍ ኖሯል፡፡ በአንድ በኩል በዓባይ ላይ የሚሠራ ፕሮጀክት በቂ የገንዘብ ድጋፍ እንዳያገኝ በማድረግ፤ ሁለተኛ ደግሞ ኢትዮጵያን በአሣሪ ስምምነቶች ለመጥለፍ በመሞከር፡፡
ኢትዮጵያ ይሄን ፈተና ለመወጣት በራሷ ገንዘብ ዓባይን ለመገደብ ተነሣች፡፡ በዚህ ጊዜ የምዕራቡ ዓለምና ግብጽ የግድቡን ፕሮጀክት ለማጓተትና ለማስቀረት ሦስት መንገዶችን ተከተሉ፡፡ አሣሪ ስምምነቶችን ማምጣት፣ የፕሮጀክቱን ጥራት መቀነስ እና የፕሮጀክቱን ሥራ ማጓተት፡፡ የመጀመሪያው ስትራቴጂ የፕሮጀክቱን ጥራት መቀነስ ነው፡፡ ለዚህ ዓላማ መሳካት ሜቴክ የሠራውን አሳፋሪ ሥራ ማስታወስ በቂ ነው፡፡ የግድቡ ብረቶች አዲስ አበባ ውስጥ እየተቸበቸቡ ግድቡ በማይሆኑ ብረቶች እንዲሠራ የተደረገው ባለማወቅ አልነበረም፡፡ ፕሮጀክቱ ከመጠናቀቂያ ጊዜው በዘገየ ቁጥር የዋጋ መናር ይከሠታል፡፡ ከዚያም አልፎ ሥራቸውን ያጠናቀቁ ኮንትራክተሮች ወደ ሌላው ተግባር ባለመሸጋገራቸው የሚጠይቁት ከፍተኛ ክፍያ ይኖራል፡፡ ይሄም እስከ ዓለም አቀፍ ፍርድ ቤቶች የሚደርስ ነው፡፡ ከሦስት ዓመታት በፊት መንግሥት በብልሐት የፈታቸው ሁለቱን ፈተናዎች ነበር፡፡
እነዚህ ሁለቱ ካልተሳኩ ኢትዮጵያን በዲፕሎማሲ ጫና ሥር አስገብቶ አሣሪ ስምምነት እንድትፈርም ማድረግ የመጨረሻው አማራጭ ነበር፡፡ ባለፉት ዓመታት በአሜሪካ መንግሥት፣ በአውሮፓ ኅብረት፣ በጸጥታው ምክር ቤት፣ ኢትዮጵያ በዓባይ ምክንያት የተጠራውን ስሟን ማስታወስ ብቻ ለዚህ በቂ ማሳያ ነው፡፡
ኢትዮጵያ ዓባይን ለመገደብ የተከተለችው ስትራቴጂ ለግብጽ ምቹ አልሆነም፡፡ ‹እየተዋጋን እናመርታለን› ዓይነት ሆነባት፡፡ የግድቡ ሥራ አይቆምም፤ ውይይትምም ድርድም፣ ምክክርም ካለ ጎን ለጎን እናስኬደዋለን፡፡ ገንዘብም ከራሳችን እንመድባለን፡፡ እንደምንም ብለን እንጨርሰዋለን፡፡ የሚለው አካሄድ ኢትዮጵያን ጫና ውስጥ ለመክተት የማይመች ሆነ፡፡
335 views13:59