Get Mystery Box with random crypto!

በመረጋጋት ላይ አደራችሁን!!! -فَعَلَيْكُمْ بِالتُؤَدَةِ ―――――――――――― | 🌹የሱና እህቶች የለውጥ ሚና🌹

በመረጋጋት ላይ አደራችሁን!!!

-فَعَلَيْكُمْ بِالتُؤَدَةِ
―――――――――――――
በዚህ ዘመን እጅግ በከፍተኛ ሁኔታ እውቀት ፈላጊና አስተማሪ ከሆኑ በርካታ ግለሰቦች በስፋት እያነሰ የመጣው በጥልቅ የማስተዋል፣ የመረጋጋትና በዋናነት ደግሞ የስነምግባር ጉዳይ ነው። እርጋታ፣ ብስለትና ስነምግባር የዲኑ አንድ አካል በማይመስል መልኩ ሆደ ሰፊነት በሚያስፈልግባቸው ርዕሶች ላይ በየቦታው በወንድሞቻችን መካከል የሚታዩ ለከት የሌላቸው ነቆራዎች፣ ስድቦችና ያለ አግባብ ስም ማጠልሸቶች ተበራክተዋል። ሰዎችን ወደ ሐቅ ለማድረስ አቋራጭ የሚመስሉንን በሙኻሊፎች አልያም ተሳስተዋል ብለን ባሰብናቸው ወንድሞች ላይ የሚሰነዘሩ መረን የለቀቁ የጥላቻ ሰበካዎች በተዘዋዋሪ ዳዕዋችንን እየጎዳው ነው። ሁሉንም በልክና በብስለት ማስኬድ አፅንዖት የሚሰጠው ጉዳይ መሆን አለበት። እንዲሁም ከፊሉ በአቅሙ ልክ ውስን ዘርፎችን ሲሸፍን ሌላው ክፍተቱን እየሞላ ዳዕዋውን ማራመድ ካልተቻለ ትልቅ ክፍተት መፍጠሩ አይቀርም።
በዳዕዋው ውስጥ የተሳትፏችን ልክ በእውቀታችን መጠን የሚገደብ መሆኑን መዘንጋት የለብንም። አንድ ሰው ስለሁሉም ተናግሮ ማስጠንቀቅና አዳርሶም ማስተማር አይችልም። አንተ የአቅምህን ከተወጣህ ሌላው ወንድምህም ከጎንህ የአቅሙን ካበረከተ ተጋግዘን በአላህ ፈቃድ በአጭር ግዜ ለውጥ ይመጣል። ነገር ግን እኔ የገባሁበት ካልገባህ፣ እኔ የታየኝ ካልታየህ፣ የኔን የዳዕዋ ስልት ካልተገበርክና እኔ ያስጠነቀኩትን ካላስጠነቀክ ብለህ ሽኩቻና ነቆራ በወንድሞችህ ላይ ከከፈትክ በተውሒድ ዳዕዋ ላይ እጅግ ከፍተኛ ችግር ትፈጥራለህ። መንገድህም ይረዝማል። ሸይኽ ኢልያስና መሰል ወንድሞች በዚህ ርዕስ ላይ የሚስተዋልባቸው እርጋታና ብስለት፣ ማስተዋልና ስክነት እንዲሁም መሰረታዉ እውቀት ላይ ትኩረት መስጠት ለብዙ ወጣት ዱዓቶች አስተማሪ ነው።
ሰዎች ዘንድ መታወቂያህ ስህተት መልቀምና ስህተት የመሰለህን በመሰብሰብ "ረድ" ማዘጋጀት ከዚያም በአቋራጭ መድረስ ሳይሆን መሰረታዊ የዐቂዳና ተያያዥ ርዕሶችን በማስተማር መሆን አለበት። በእያንዳንዱ ርዕስና አለመግባባት ላይ መልስ ካልሰጠው በተጨማሪም ተዕሊቅና ተድቂቅ ካላደረኩ ማለት እጅግ አስከፊ ውድቀት ውስጥ ይከተናል።
ከጥንት አበዎች አንስቶ እስከ አሁን ያሉ ሊቃውንቶች በቅድሚያ ህዝቡ ዘንድ የሚታወቁት በጀርሕና ተዕዲል ብቻ ሳይሆን በሚያሰራጩት እውቀት፣ በዒባዳቸው ትጋት፣ በስነምግባራቸው ምጥቀት ነው። እነዚህ ምስጉን ስብዕናዎች በነዚህ መልካም ባህሪያት ከመታነፃቸውም ጋር ከተለያዩ አንጃዎችና ግለሰቦች የሚነሱ ውዥንብሮችንና ማምታቻዎችን የአላህን ፊት ፈልገው፣ እውቀትና ስርኣትን በተላበሰ መልኩ መልስ ይሰጣሉ። ውጤቱም ምስጉን ይሆናል።

ዐብዱረዛቅ አል-ሐበሺይ
https://t.me/abdurezaq27